>
5:13 pm - Sunday April 18, 0173

ሀሰተኛ የማስተርስና የዶክትሬት ድግሪ ሲያድሉ የኖሩ የሜቴክ ኃላፊዎች ላይ ክስ ተመሠረተ!!!

ሀሰተኛ የማስተርስና የዶክትሬት ድግሪ ሲያድሉ የኖሩ የሜቴክ ኃላፊዎች ላይ ክስ ተመሠረተ!!!
አወድ መሀመድ – ሪፖርተር
በመንግሥት ላይ በአጠቃላይ ከ73.6 ሚሊዮን ብር በላይ ጉዳት መድረሱ ተገልጿል
የመከላከያ ኢንጂነሪንግ ኮሌጅ ላላስተማራቸውና ባልተቀረፀ የትምህርት ካሪኩለም ሐሰተኛ የማስተርስና የዶክትሬት ዲግሪዎች እንዲሰጡ አድርገዋል የተባሉት፣ የቀድሞ የሜቴክ ዋና ዳይሬክተርን ጨምሮ በስምንት ተጠርጣሪዎች ላይ ክስ ተመሠረተ፡፡
በአሜሪካ መንግሥት ከሚታወቀውና በዓለም ላይ አሉ ከሚባሉ የትምህርት ተቋማት ውስጥ ዋነኛ ከሆነው ካሊፎርኒያ ኢንስቲትዩት ኦፍ ቴክኖሎጂ ጋር ተቀራራቢ ስም ያለው ተቋም፣ ነገር ግን በማንም የማይታወቅ በማስተርስና በዶክትሬት ዲግሪዎች ለማስተማር መኮንን ገብረ ሚካኤል (ዶ/ር) በተባለ ተጠርጣሪና ባልተያዘ ግለሰብ መቋቋሙን ክሱ ያስረዳል፡፡
ግለሰቡ ራሱን የሐሰተኛ ተቋም ሥራ አስኪያጅ አድርጎ በማቅረብ፣ ከቀድሞ የሜቴክ ኃላፊዎች ሜጀር ጄኔራል ክንፈ ዳኘው፣ ብርጋዴር ጄኔራል ጥጋቡ ፈትለ፣ ሻለቃ ገብረ ሥላሴ ገብረ ጊዮርጊስ፣ ሻለቃ ፋሲል አበራ፣ መቶ አለቃ ቶማስ ደረሰ፣ ወሰን የለህ ኃይለ ሚካኤልና ሀድአት ወልደ ትንሳይ በተባሉ የሜቴክ የተለያዩ ክፍል ኃላፊዎች ጋር በጥቅም በመመሳጠር፣ ሐሰተኛው ተቋም ከሜቴክ ጋር ከፍተኛ ትምህርት ለማስተማር የውል ስምምነት መፈራረሙንና ዋና ዳይሬክተሩ እንዲፀድቅ ማድረጋቸውን የዓቃቤ ሕግ ክስ ያስረዳል፡፡
ግለሰቡ ድርጊቱ በኢትዮጵያ መንግሥት እንዳይታወቅ የተለያዩ የውጭ አገር ዜጎችን በቱሪስት ቪዛ ወደ አገር ውስጥ እንዲገቡ በማድረግ፣ ክፍያው በውጭ ምንዛሪ እንዲፈጸምላቸው ስምምነት ማድረጉን ክሱ አክሏል፡፡ ግለሰቦቹ ትምህርቱን ሳያስተምሩ ተመራቂዎች ዲግሪ በሕገወጥ መንገድ በመከላከያ ኢንጂነሪንግ ኮሌጅ እንዲሰጥ ማድረጋቸውን ክሱ ያስረዳል፡፡
በሐሰት የተቋቋመው ኮሌጅ በታዳሽ ኃይል፣ በኦፕሬሽን ማኔጅመንትና በኢንዱስትሪያል ኢኮኖሚክስ የማስተርስና የዶክትሬት ዲግሪዎች ለመስጠት አራት ውሎችን በመፈጸም፣ በአጠቃላይ 3,901,140 ዶላር ወይም 75,114,030 ብር ሐሰተኛ ተቋሙ አሜሪካ ውስጥ በከፈታቸው የሒሳብ ቁጥሮች ገቢ ማድረጋቸውንና በእጅ አዙር የጥቅሙ ተካፋይ በመሆናቸው፣ ሥልጣንን ያላግባብ መገልገል የሙስና ወንጀል ክስ ዓቃቤ ሕግ መሥርቶባቸዋል፡፡
በተጨማሪም ሜጀር ጄኔራል ክንፈ ማርዳ መለስ ለተባለች ግለሰብ በሁለት ዙር 56,205 ዶላር ወይም 1,250,886 ብር ክፍያ ከሜቴክ እንዲከፈል በማድረጋቸው፣ ሥልጣናቸውን ያላግባብ መገልገል የሙስና ወንጀል ክስ አቅርቦባቸዋል፡፡ በአጠቃላይ ተከሳሾቹ በመንግሥት ላይ 76,364,916 ብር ጉዳት ማድረሳቸውን የቀረበባቸው ክስ ያሳያል፡፡
Filed in: Amharic