>

ደምቢ ዶሎም አዲስ አበባም አንድ ነው!!! (መአዛ መሀመድ)

ደምቢ ዶሎም አዲስ አበባም አንድ ነው!!!

 

መአዛ መሀመድ
ዛሬ በአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን በታገቱ እህቶቻችን ጉዳይ የታሰሩ የታጋች እህት እና ለሀሰተኛ ዶክመንተሪ በዛቻ ከደቡብ ጎንደር የመጡ እህቶቼን፤ ጉዳያቸውን ለማጣራት እና ለማነጋገር  ፖሊስ ኮሚሽን ተገኝቼ ነበር።
የታጋች እህት ፍቅርተ በትናንትናው እለት የታሰረች ሲሆን እንደነገረችኝ የተከሰሰችበት ክስ “ሀሰተኛ መረጃ በማሰራጨትና አመፅ እንዲነሳ በማድረግ” ነው። የታገተችባት እህቷ አስቻሉ ቸኮል በደንቢ ዶሎ ዩኒቨርስቲ የሶስተኛ አመት ተማሪ ስትሆን፤ ከታገተች በሁዋላ አጋቾቹ የኦሮምኛ ቋንቋ ተናጋሪ በመሆናቸው ፍቅርተ ለተከታታይ ቀናት በአስተርጓሚ ታወራትም ነበር። ይህ ኦሮምኛ ቋንቋን በመተርጎም ሲያግዛት የነበረ አበበ አብርሃም የተባለ ግለሰብ አብሯት እዚሁ ታስሮ ይገኛል።
በተመሳሳይ ባህር ዳር ተገኙ ተብለው በማህበራዊ ሚድያ ፎቷቸው ሲሰራጭ የነበሩትና መንግስት ለድራማ ያዘጋጃቸው ናቸው የተባሉት ሸዋዬ ገነትና ቅድስት ጋሻው የተባሉ ሴቶችን  ከደቡብ ጎንደር ይበልጣል በተባለ ግለሰብ አስፈራርተው ለባህርዳር ደህንነት እንዳስረከቧቸው ነግረውኛል። አዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ከመጡ በሁዋላ ይህንኑ እንደተናገሩ ነግረውኛል። አንተባበርም በማለታቸው “ለመንግስት የተሳሳተ መረጃ በመስጠት” በሚል  ክስ ተከሰው ታስረው ይገኛሉ።
ይህ ጉዳይ ሀገራችን ምን ያህል የሞራል ልዕልና ኃላፊነት በማይሰማቸው እጅ እንደምትገኝ የሚያሳየን ሲሆን፤ ገዥው መንግስትም ምንም ያህል የእህቶቻን ጉዳይ ያላስጨነቀውና ብሎም ወንጀለኞችን ለመደበቅ ብዙ እርቀት እየሄደ እንደሆነ ያሳያል።
ለዜጎቹ የሚቆረቆርና ኃላፊነት የሚሰማው መንግስት የለንም፣ ለተበደሉ እህቶች የሚቆም ጠንካራ  ተቋማት አልገነባንም፣ መንግስት  የታገተ እንዳለም እውቅና መስጠት አልፈለገም።  የተደራጀ ህዝብና ጠንካራ ተቋምም የለንም።
ከዚህ በላይ ምን አለ? በዚህ ሁኔታ ሃገር አለን ማለት እንችላለን ወይ? ነገ የእንዚህ ልጆች እጣ ፈንታ እንደማይገጥመን በምን እርግጠኛ እንሁ?
Filed in: Amharic