>
5:13 pm - Saturday April 19, 8504

ችግርን በችግር መተካት (ፕሮፈሰር መስፍን ወልደ ማርያም)

ችግርን በችግር መተካት

 

ፕሮፈሰር መስፍን ወልደ ማርያም

 

ኮሮናቫይረስ ኢትዮጵያን ብቻ ሳይሆን ዓለምን በሙሉ፣ ከአውስተራልያ እሰከአሜሪካ ካውሮፓ እስከአፍሪካ ወረርሺኙ ተስፋፍቶ እያዳከመና እየገደለ ነው፤ የእግዚአብሔር አገር የሆነችው ኢትዮጵያ እስካሁን በተሻለ ሁኔታ ላይ ነች፤ በአገዛዙም በኩል እየተደረገ ያለው አብዛኛው የሚደገፍ ነው፡፡

ነገር ግን መፍትሔ ተብሎ በሰዎች ላይ የሚፈጸመው ግፍ ሌላ በሽታን እያስከተለ ነው፤ አንድ ኢትዮጵያዊ በጊዜ አገሬና ወገኔ ዘንድ ልድረስ ብሎ ከውጭ ሲመጣ ተይዞ የደኅንነት ሰዎች ወደሆቴል ይወስዱታል፤ በሽታን ለመቆጣጠር ይህ አስፈላጊ እርምጃ ነው፤ አያከራክርም፤ ለሆቴሉና ለማደሪያ፣ ለምግብ ማን ይከፍላል? አንዴት ይከፍላል? መቼ ይከፍላል? የሚሉት ጥያቄዎች ተገቢ መልስ ካላገኙ በሽታው በበሽታ ይተካል፤ አንድ በሉ!

በሆቴል የተያዘው ሰው የሥራ ድርጅት ያለው ከሆነ ሠራተኞች ይኖሩታል፤ ለብዙ የተለያዩ ጉዳዮች ገንዘብ ያስፈልገዋል፤ እነዚህን ግዴታዎቹን የሚወጣው እንዴት ነው? ሠራተኞቹ ይቸገራሉ፤ በሽታውን በበሽታ መተካት አይሆንም?

እንደሰማሁት አንድ ሰው በግዮን ሆቴል እንዲገቡ ሲገደዱ ለአሥራ አራት ቀኖች አሥራ አምስት ሺህ ብር በቅድሚያ ያስይዛሉ፤ አልጋቸውን የሚያነጥፉት እነሱው ናቸው፤ የሆቴል አገልግሎት ከጣራና ከግርግዳው አያልፍም፤ በሽታን ማሻር ነው? ወይስ በሽታን መተካት?

ለእኔ በሽታው ማኅበረሰባዊ ነው፤ ይህ ማለት ኃላፊነቱና ግዴታው የጋራ ነው፤ የሁላችንም ነው፤ እንደሚነገረው ከሆነ በሽታው ሥነ ሥርዓትን የሚፈራ ነው፤ ሥርዓት-አልባ በመሆን የባሰ እንጠቃለን፤ የአኗኗር ለውጥ ለማምጣት ግንኙነታችንን ሥርዓት ለማስገባት እንገደዳለን፡፡

Filed in: Amharic