>

ከራዳር የወጣች፣ ኮምፓሷም የጠፋባት ሀገር (አምባቸው ደጀኔ (ከወልዲያ)

ከራዳር የወጣች፣ ኮምፓሷም የጠፋባት ሀገር

አምባቸው ደጀኔ (ከወልዲያ)

ኢትዮጵያ የምትመሰልበት ነገር አበዛዙ!

ድመትም ትመስለኛለች፡፡ ድመት የገዛ ሙጫቅሊቶቿን ሳይቀር ቅርጥፍ አድርጋ ትበላለች፡፡ “ስለምትወዳቸው ነው” ይባላል፡፡ እንዲህ አድርጎም መውደድ የለም፡፡ ኢትዮጵያም ከጥንት እስካሁን ልጆቿን የምታነክተው ስለምትወዳቸው ከሆነ ፍቅሯና ውዴታዋ ባፍንጫቸው ይውጣ፡፡ ስንትና ስንት ትውልድን እየጨረሰ “አብዮት ልጆቿን ትበላለች!” ይባልልኛል – ወደድመት የተለወጠች ሀገር ትቅርብኝ፡፡ 

ኢትዮጵያ አቅጣጫ መጠቆሚያ ኮምፓሷ የጠፋባት መርከብ ትመስለኛለች፡፡ እንደኢትዮጵያ ኮምፓሱ ጠፍቶበት አውላላ ውቅያኖስ ላይ የተገተረ መርከብ ይታያችሁ፡፡ ልሂድ ቢል ወደየትም ሊሄድ አይችልም፡፡ ልቁም ቢል ረሀብና ጠኔው በውስጡ ያሉትን ተሣፈሪዎች አያስቆማቸውም፡፡ ሞትን መጠበቅ ብቻ ይሆናል ዕድላቸው፡፡ ልክ እንደ እኛ፡፡

ኢትዮጵያ ከራዳር የወጣ አውሮፕላን ትመስለኛለች፡፡ አውሮፕላን ከራዳር ሲወጣ ከምድርም ሆነ ከሰማይ ምንም ዓይነት ዕርዳታ ሊደረግለት አይችልም፡፡ ከክትትል አድማስም ይሰወራል፡፡ ቢከሰከስ ቢጠለፍ የሚያውቅ የለም፡፡ ኢትዮጵያም ከእግዜርም ከሰውም እጅ ወጥታ እንዲሁ በበረሃ እንደሚቅበዘበዝ እርኩም ሆናለች – “እርኩም” ነው ያልኩት፤ ከፈለግህም “እርጉም” ብለህ ልታሻሽለው ትችላለህ፡፡

ኢትዮጵያ የአእምሮ ህሙማን የታጨቀበት አማኑኤል ሆስፒታልን የመሰለ የህክምና ማዕከል ትመስለኛለች፡፡ የአእምሮ ህሙማን የጭንቅላት ችግር ስላለባቸው በሚያደርጉት ነገር ሁሉ አይፈረድባቸውም፡፡ ይልቁንም በራሳቸውም ሆነ በሌላ ሰው ላይ ጉዳት እንዳያስከትሉ ክትትልና ጥበቃ ይደረግላቸዋል፡፡ የኅሊና ጤንነት ችግር ላይ የወደቁ ሰዎች ግን መቀወሳቸው ስለማይታወቅ የዕብደታቸው ውጤት እንጂ ዕብደቱ ገንኖ አይስተዋልባቸውም፡፡ እናም ኢትዮጵያ አመራሩም ሆነ የአመራሩ ቦታ ሁሉ በንኮችና በለየላቸው ዕብዶች በመያዙ ተቆጣጣሪ የሌላት የወፈፌዎች ሀገር ሆናለች፡፡ በዚህ የዕብዶች ግዛት ውስጥ መኖር ደግሞ ትልቅ እርግማን ነው፡፡

ኢትዮጵያ ካምሱሩ የተነቀለ ቦምብ ትመስለኛለች፡፡ በግዳጅ ላይ ያለ ወታደር በጥይትና በቦምብ ከጠላት ጋር በሚሞሻለቅበት የጦፈ ዐውደ ውጊያ ላይ  ቅርበቱን ጠብቆ ቦምብ ይወረውራል፡፡ ከመወርወሩ በፊት ግን የቦምቡን ካምሱር ( መጠበቂያውን) ይፈታና ያወልቀዋል፡፡ ያኔ ጊዜ ወሳኝ ነው፡፡ በሚፈቀዱ ሴከንዶች ውስጥ ካልወረወረ አደጋ አለው፡፡ ለራሱም ይተርፍና ድራሹ ሊጠፋ ይችላል – ካለሰዓቱ ከወረወረ ጠላት መልሶ ይወረውርበታል – ሰዓቱ ካለፈም እጁ ወይም ጭኑ ላይ ይፈነዳና ራሱ ያልፋል፡፡ ኢትዮጵያም በዚያ ሁኔታ ውስጥ ትገኛለች፡፡ ዕብድ ልጆቿ ቤተ መንግሥቷንና ሁለመናዋን ሰቅዘው ይዘው ካምሱሩ እንደተነቀለ ቦምብና ፈንጂ ስላደረጓት እግዜር በወቅቱ ካልደረሰላት በስተቀር የጊዜ ጉዳይ እንጂ መፈንዳቷ የማይቀር ድማሚት ሆናለች፡፡ “ደስ የሚለው” ግን ስትፈነዳ ከቦምብ ሊተርፍ የሚችል “bomb(TNT)-immune“ የሆነ አንድም ሥጋ ለባሽ ኦሮሞም ይሁን አማራ ማለቴ አንድም በሰው አምሳል የሚንቀሳቀስ ፍጡር አይኖርም፡፡ ጉዳቱ ለእንስሳትና ለዛፍ ቅጠልም አይቀር፡፡ መሬትም ትከስላለች፤ ዓለቶችም ይቀልጣሉ፡፡ “የታደለ” ይህንንም ያያል፡፡ ልባም ቢገኝ ግን ዕብደትን ቆም ብሎ በማስተዋል ወደ ቀናው መንገድ በአፋጣኝ መግባት ትልቅ መፍትሔ በሆነ ነበር፡፡ “በፋሲካ የገባች ገረድ ሁሌ ፋሲካ ይመስላታል” የሚለው ብሂል እያሸተ እንጅ እየጠወለገ አይሄድምና ጥጋበኞች  please በጊዮርጊስ ጥጋባችሁን በረድ አድርጉት ለማለት እወዳለሁ –  በዚህች አጋጣሚ፡፡ ከፈለግህም ቀጥልበት፡፡ ወዳዲሱ ደደቢት ወደ ደምቢዶሎ ሄደህ የመወሸቅ ዕድል እንኳን የምታገኝ አይመስለኝም – ምድረ ጥጋበኛ አባዱላና አባላፋ ሁሉ! እውነቴን ነው ደግሞ፡፡ ሕዝብን ማታለል የሚችል የለም፡፡ ሕዝብ የጠላው እግዜርም የጠላው ነውና ቀን ሰጠኝ ብሎ በሐዝብ ላይ ግፍ መሥራት ትልቅ ዋጋ ያስከፍላል – ወያኔን እዩ!! አሁን የሚሠራህን ያሳጣህ ምድረ ኦህዲድና ቅጥረኛው ብኣዴን እናትህ ማሕፀን ውስጥ ብትገባ ያቺን ቀጭን ዘመን አታልፍም!! “ምናለ አምባቸው” በለኝ! ቱ!

“እንዲህ ጨሶ ጨሶ የነደደ እንደሆን፤

ያመዱ ማፍሰሻ ‹ሥርፋው› ወዴት ይሆን?” ተብሎ የተቀነቀነውን ነባር ሥነ ቃላዊ ብሂል ማስታወስ ይገባል – ብዙም ሳይረፍድ አሁን፡፡

ኢትዮጵያ በባዕዳን ዐረመኔያዊ ቅኝ ግዛት ሥር የወደቀች ትመስለኛለች፡፡ ከሁለት ዓመታት በፊት የነበረችበትን አስቀያሚ የሥቃይ ዘመን በሚያስናፍቅ ሁኔታ በአዲሶቹ ሥልጣንና ሀብት ብርቁ ገዢዎች እጅ ወድቃ ኤሎሄ እያለች ናት፡፡ እነዚህኞቹ ተረኞች ይሉኝታቢስነትንና ሀፍረት የለሽነትን ከአማራ ብድርና ቁጠባ ባገኙት ገንዘብ ከወያኔዎች ገዝተው ገና በሁለት ዓመታቸው ዕጹብ ድንቅ የሚሰኝ አዲስ የአፓርታይድ ሥርዓት በመላ ሀገራችን እየዘረጉ ይገኛሉ፡፡ እንኳንስ እነሱን መሰል ከተማ ቀመስ ሰው ከጫካ የወጣ አዲስ ፍጡርም እንደነሱ ዐውሬና ፍርደ ገምድል ይሆናል ተብሎ አይታሰብም፡፡ “ይች ሰው ቸኮለች ልታድር ነው መሰል” ይባላል እንደነዚህ ያለ ቅሌታም እንግዳ ሲያጋጥም፡፡ አማዞን ውስጥ በቅርቡ ተገኙ የተባሉት የሰው ልጅ ዘሮችም የነዚህ ደነዞችን ያህል ዘረኛ አይሆኑም፡፡ ሰዎች ናቸዋ!

አሁን ላይ ሆነን ስናስበው – በዜጎች በተለይም በአማሮች ላይ ያደረሱትን ዘመን የማይሽረው አካላዊና ኅሊናዊ ጠባሳ ለጊዜውና ለዚህች ቅጽበት ብቻ ወደጎን አስቀምጠን – ወያኔዎች መጠነኛ ይሉኝታ ነበራቸው፡፡ ያን ሁሉ ግፍና በደል የፈጸሙትም በ27 ዓመታት ውስጥ ነው፡፡ እነዚህኞቹ ጉዶች ግን ገና በሁለት ዓመታቸው እንደዮዲት ጉዲትና እንደአህመድ ግራኝ ዘመን ዓይነት ጥፋት እየፈጸሙ ነው፡፡ የሚገርመው ግን እነሱም ብልጥ ሆነው በዳቦና በዛፍ ተከላ እንዲሁም በከተማ ውበትና በመንገድ ጽዳት የጉሽ ጠላ ስካር አዳሜን እያነበረሩ በኅቡዕም በግልጽም ግና ያሻቸውን በማድረግ በተለይ አንዳንድ የሀገር ውስጥ ጅሎችንና ሌላውን ዓለም ማነሁለላቸው ነው፡፡

ያዝልኝ እንግዲህ!

  • ከሞላ ጎደል አዲስ አበባን ለቄሮና ለቄሪት አከፋፍለው ጨርሰዋል፡፡ ዴሞግራፊውን ወደ ኦሮሞነት እንለውጣለን ብለው ከዛቱ ወዲህ ሁሉንም የአዲስ አበባና የፌዴራል ተብዬ ቁልፍ ቁልፍ ሥልጣን ለአክራሪ ኦሮሞ እያደሉ ሌላውን ዜጋ ጨረቃ ላይ እያስቀመጡት ነው፡፡ እንደሰማሁት እንደሚድሮክ ያሉ ግዙፍ የልማት ድርጅቶችንም ኦሮሞ ካላስተዳደራቸውና ኦሮሞን ብቻ ካልቀጠሩ “ወደ ወልዲያ ወስዳችሁ ትከሉ” እስከማለት የደረሰ ዕብሪትም እያሳዩ ነው አሉ – አዎ፣ ጥጋብን እስከጥግ ካልጠገቡ የጥጋብን ዋጋ አያገኙትምና እውነታቸውን ነው በደምብ ይጥገቡ፤ ትምክህታቸውንም በደምብ ያውጡትና እንይላቸው፤ ከዚያም የሰው ልጅ ሲጠግብ እስከምን ሊበሻቀጥ እንደሚችል እኛም እንማር፤ ተምረንም የወደፊታችንን እናስተካክል – እናም ይህም ለበጎ ነው፡፡ በሌላ ወገን ሕዝበ አዳም የተዞረበትን ድግምት ሳያውቅ ፈዝዞና ደንግዞ ተጎልቷል፡፡ የትም ሂድ ያለ ኦሮሞ ሹም ማግኘት ይቸግርሃል – ለይስሙላ የተዘረፈጡትን አትቁጠር፡፡ ይህን መሰሉን የይስሙላ ሹመት ደግሞ ከወያኔ ነው የተስተማሩት፡፡
  • የኮንዶምንየም ነገር አይነሣ፡፡ ለቄሮና ለቄሪት በነፃ ሳይቀር እንደጠበል በከዚህ መልስ እየተረጨ ነው፡፡ ባዶ ቦታ የተባለች በጧፍና በሻማ እየተፈለገች ኦሮሞ እየወረራት ነው፡፡ አዲስ አበባ ከተጋሩ ወደ ኦሮሙማ ተገልብጣ አሣሯን እያየች ነው፡፡ በዚህ ከቀጠልን በአምስት ዓመታት ውስጥ – እዚያም ሳንደርስ እንዲያውም – አዲስ አበባና አካባቢዋ ካለኦሮሞ አንድም ኢትዮጵያዊ አይኖርም – እንዲኖርም አይፈቀድለትም፡፡ ዱሮ በትግርኛ ጩኸት ስትናወጥ የምታመሽና የምታድር ሸገር አሁን ላንቃው እስኪበጠስ የሚጮው ኮበሌ ቄሮ ነው (ቆርቆሮ ስትል ሰማሁህ ልበል? እኔ አልወጣኝም!)፡፡ ግዴላችሁም – ይሄ ዘረኝነት የሚባል ነገር ከእንስሳነትም በወረደ ደረጃ ያበደ ዐውሬ ሳያደርግ አይቀርም፡፡ አንጎል በዘረኝነት በሽታ ሲበከል የሚታይህ ሁሉ ያንተው ይመስልሃል ወይም እንዲሆን ትመኛለህ፤ ያንተ ሆኖ ካላገኘኸው ደግሞ በለው በለው ይልሃል፡፡ ዘመኑ ለዚህ ዓይነቱ ዕብድ ፖለቲካ የሰጠ በመሆኑ አሁን እየሆነ ያለው ይሄው የበለውና በበለውም ያለመከሰስ መብት ነግሦ መታየት ነው፡፡ ፌዴራልና መከላከያ በኦሮሞ የበላይነት በመያዙ አማራና ሌላው እየተለማመጠ እንዲኖር ተፈርዶበታል – (ለጥቂት ጊዜም ቢሆን፡፡)
  • ዘመነ መሣፍንት ከዚህ በላይ የለም፤ ያኔም አልነበረም፡፡ አቢይ ማንን እየገዛ እንደሆነ ራሱም የሚያውቅ አይመስለኝም፡፡ ክልሎችን ቀርቶ ግለሰቦችን መንካት አይፈልግም፤ እንደማይችልም ሳያምን አልቀረም – መሣፍንቱም ይህን ስስ ብልቱን ሳይገነዘቡ አልቀሩም፡፡ አቢይ ማለት ክፍት በነበረ የፈሪዎች ቤት ውስጥ አንዱ እግሩን ጅብ እየቆረጠመው ሌላኛውና ወደጥጋቱ የነበረው ሰው “ምንድን ነው የሚጎረድመው?” ብሎ በጠየቀ ጊዜ “ዝም በል ታስጨርሰናለህ፤ የኔን እግር እየበላ ነው” እንዳለው ሰው ነው፡፡ አስመሳዩና ውሸታሙ አቢይ (ለቃል አጠቃቀሜ ከፍተኛ ይቅርታ!) ዓላማና ፍላጎቱ በጭራሽ አይታወቅም፡፡ የኦሮሞን ጉዳይ እያስፈጸመ ነው ለማለትም፣ የኢትዮጵያን ጉዳይ እያስፈጸመ ነው ለማለትም፣ የሰይጣናውያኑን የነእስራኤል ዳንሳን በሃይማኖት ስም  ሕዝብን የማጭበርበርና እስከመቅኒው የመጋጥ አጋንንታዊ ተልእኮ እያስፈጸመ ነው ለማለትም፣ የግብጽን ዓላማ ለማሳካት የሚጥር ነው ለማለትም፣ አማራን ድራሹን ለማጥፋት ያለመ ሥልታዊ አካሄድን እየተከተለ ነው ለማለትም፣ ኢትዮጵያ በ30 እና በ40 የክልል መንግሥታት እንድትከፋፈል ታጥቆ የነተሳ ነው ለማለትም፣ dysfunctional portfolio or responsibility without authority የሚሉትን ዓይነት ደካማ ሥልጣን መያዙ እየታወቀ ለዚህም ዓይነቱ ባዶ ቦታ ያለውን አራራ ለማስጠበቅ ነው እንዲህ የሚማስነው ለማለትም … በማልችልበት ውልንግዙ የጠፋበት ሁኔታ ውስጥ ሲድሞነሞን አየዋለሁ – አቢይን፡፡ በራሱና በሥልጣን ፍቅር የወደቀው አቢይ ለማንም የማይገባ እስፊንክስ ነገር ሆኖብኛል – እንደኔና እንደአካሄድ፡፡ ቡዳ አይሉት ሰላቢ፣ ጳጳስ አይሉት ፓስተር፣ ሃጅ አይሉት ራባይ … ሁሉንም ለመሆን እየሞከረ የሚገኝ አንዱንም መሆን ግን ያቃተው የታሪክ ዕንቆቅልሽ ነው – ዶ/ር ኮሎኔል ፓስተር ባለኖቤሉ … አቢይ፡፡ ኢዲያሚን ዳዳ ምን ብላችሁ ጥሩኝ ነበር ያለው? ለምን ትዝ እንዳለኝ ግን አላውቅም፡፡ … ለዚህ እኮ ነው ቭላድሚር ኢሊች ኡሊያኖቭ ሌኒን “ሀገር ሲያረጅ ጃርት ያፈራል” ሲል አይረሴ ተረት የተረተው፡፡ ‹የማነሽና ትባረኪያለሽ› አሉ … በአቢይ መንግሥት ሥር ሆኜ ዱሮውስ … ደግሞ ለውሸት፡፡ ለማንኛውም ሌኒን እንዲህ አላለም ወንድማለምዋ …
  • ግለሰቦችና የሃይማኖት በድኖች – ቡድኖች ለማለት ነው – የመንግሥትን ሚና ቀምተው ሲያስተዳድሩ(ን)ም ይስተዋላል፡፡ ድንቁ ደያስ የተባለ ማፈሪያ ማፊያ ምን እንደሠራ እየሰማን ነው፤ እሱን መሰሎችም ሞልተዋል አሉ፡፡ መንግሥት የለም ያስብላል፡፡ ካለም ከዱርዬዎችና ከሌቦች ጋር እየተሻረከ የድርሻውን የሚወስድ ማጅራት መች መሆን አለበት፡፡ አቢይ አሰለጡ ሁሉንም ያውቃል፡፡ ደያስን ያውቃል፤ ዳንሳን ያውቃል፤ እዩ ጩፋን ያውቃል፤ አባ ዮሐንስ ተብዬውን ባህታዊ ያውቃል፤ እህተ ሰይጣንን ያውቃል፤ ገብረ መስቀል የሚባለውን አጭበርባሪ ባህታዊ ነኝ ባይ ያውቃል፣ ስምንተኛውን ንጉሣችንን አቤቶሁን በላቸው አቡዬን ያውቃል፤ … የገደሉንም የባህሩንም … ሁሉንም … ዴራሞ ፀራሞ ጠንቅቆ ያውቃል – ሀገር እሚያምሱትን፤ የዋሃንን የሚያታልሉትንና ውዥንብር የሚፈጥሩትን፡፡ በየቤቱ እስር ቤት ያለውን ምድረ ሀብታምና ምድረ ሰይጣን ጎታች አስጎታች ባለቆሪጥ ያውቃል፡፡ ግን ዝም ነው፡፡ ሀገር የዶግ አመድ እየሆነች፣ ሀገር በሌቦችና በባለጌ ባለሀብቶች እየታመሰች አቢይ ግን አራት ኪሎ አትነካበት እንጂ ጉዳዩ አይደለም፡፡ ውዥንብርና ዕልቂት ምቾት የሚሰጠው ይመስላል፡፡ የሚገርም ሰው ነው አንተ!
  • ፍርድ ቤት ዱሮውንም የለም – አሁን ደግሞ በባሰ ሁኔታ በወረርሽኙ ሳቢያ ጭራሹን የለም፡፡ ሁሉም መለዮ ለባሽ ማለት በሚቻል ሁኔታ አጭበርባሪና ለገንዘብ የሚገዛ ነው – በዚህ በኮሮና ወቅት እንኳን የከበረው የመንግሥት ደምብ አስከባሪ እጅግ ብዙ ነው ( ካንዱ መዝናኛ ትታፈስና ወደማቆያ ልትሄድ ስትል ከወሳጆችህ ጋር ትደራደራለህ … አንድ ሽም … ሁለት ሽም … እንዳቅምህ ቦጨቅ ታደርግና ትቀራለህ … በበሽታም የሚነገድባት … በሞትም ትርፍ የሚግበሰበስባት … ቫይረስ እንድታሰራጭ በጉቦ ከኳራንታይን የምትለቀቅባት ሀገር ብትኖር ኢትዮጵያ ብቻ ናት – ግርምቲ አዲ!)፡፡ ለህገ መንግሥት ተብዬው አድሮ የሽምብራ መግዣ እንኳን የማይሆን ሣንቲም በደሞዝ መልክ ከሚከፈለው ይልቅ የድንቁ ደያስን እስረኛ በመግረፍ፣ የደቻሳን ሠራተኛ በማሰርና በማሰቃየት፣ የእዩ ጩፋ የግል ጠበኛ ላይ ሃያ ዓመት በመፍረድ የሚያገኘው ረብጣ ብር ያሳሳዋልና ዛሬ የመንግሥት ሥራ ለሀብት ክብረት እርካብ እንጂ ለኅሊና እርካታ የሚውል አልሆነም – በአንድ በኩል ለሙስና የሚዳርገንን ክፍተት መጠቆሜ ነው፤ ትልልቆቹ ባለሥልጣናትማ ምን ያድርጉ – ደሞዝ ለነሱ ምናቸውም አይደለም፡፡ ከአንድ የውሸትም ሆነ ከፊል እውነት ፕሮጀክት የሚቦድሱት ገንዘብ ዕድሜ ልካቸውን አንቀባርሮ ያኖራቸዋል፡፡ ወይ ሀገር!  “ምን ልሁን?” አለ ያ ዳዊት ጽጌ የሚሉት ዘፋኝ! እውነቱን ነው፡፡ እኛ ምን ይዋጠን? ወዴት ሄደን እንኑር? ማንስ ይዘንልን? እግዚአብሔር ሆይ ወዴት አለህ!
  • አዎ፣ ሀገር አለን የማንልበት ደረጃ ላይ ደርሰናል፡፡ ህግ ሳይኖር፣ ፍትህ ሳይኖር፣ ፖሊስ ሳይኖር፣ መንግሥት ሳይኖር፣ በቂ ውኃ ሳይኖር፣ በቂ መንገድ ሳይኖር፣ ህክምና ሳይኖር፣ ትምህርት ሳይኖር፣ መብራት ሳይኖር፣ በቂ የቴሌ ግንኙነት ሳይኖር፣ ፍቅር ሳይኖር፣ ሃይማኖት ሳይኖር፣ ከምንም በማይተናነስ ደረጃ አለን በምንለው እንደምንም ሊቆጠር በሚችልም በማይችልም ጥቃቅን ነገር ራሳችንን እያታለልን ለመኖር ያህል ብቻ እንኖራለን – ጥቂት ምርጦችን አንቀባርረን ለማኖር ባለብን ታሪካዊ ኃላፊነት ተገደን፡፡ በዚህ ማኅበራዊና ፖለቲካዊ ማዕቀፍ ውስጥ … ዘረኛውን የመንግሥት ተቋም የተማመነ ሁሉም ጉልበተኛ እንደልቡ እየጨፈረ ባለበት ሁኔታ ድሆች ያለቅሳሉ እንጂ ማንም የሚደርስላቸው የለም – ዕንባ ግን እሳት ነው፡፡ በቃኝ እባክህን … ሆድ ባሰኝ፡፡
Filed in: Amharic