>
5:13 pm - Saturday April 19, 6836

አራተኛው ሰኔ ትንሳያችን ካልሆነ መጥፊያችን ይሆናል! (ያሬድ ሀይለማርያም)

አራተኛው ሰኔ ትንሳያችን ካልሆነ መጥፊያችን ይሆናል!

ያሬድ ሀይለማርያም

የዛሬ ስድስት ወር አገሪቱ ያለችበት ውጥንቅጥ ሁኔታ ቢያሳስበኝ እና እየመጣ ያለው አደጋ በጨረፍታም ቢሆን ሲታየኝ ይችን ምክር አዘል ትዝብት ጽፌ ነበር።
አራተኛው ሰኔ ካሳለፍናቸው ሦስት ሰኔዎች የከፋ እንዳይሆን አሁንም ስጋቴን ደግሜ ለመግለጽ ወደድኩ። አዎ ኢትዬጵያ ዛሬም በግጭት ነጋዴዎች ተከባለች።
ዛሬ በሰማነው መልካም ዜና የአባይ ጉዳይ በተገለጸው መልኩ ለጊዜው እልባት ካገኘ እና ውጥረቱ እረገብ ካለ መንግስት ትኩረቱን ውጥንቅጡ ወደወጣው ፖለቲካችን ማዞር አለበት።
– ብሔራዊ መግባባትን የሚፈጥሩ መድረኮችን ማዘጋቸት፣
– ከባለ ድርሻ አካላት ጋር በአገሪቱ ቀጣይ እጣ ፈንታ ላይ ቁጭ ብሎ መወያየት፣
– ሰሞኑን የተፈጸመውን ዘር ተኮር ጥቃት የሚያጣራ ገለልተኛ ኮሚሽን በአፉጣኝ ማዋቅር፣
– የተጀመረውን አጥፊዎችን ለፍርድ የማቅረቡን ሂደት አጠናክሮ መቀጠል፣
– ክስተቱን የፖለቲካ ተቀናቃኞችን ለማጥቂያ ወይም ሌላ የፖለቲካ ግብ ማሳኪያ ለማድረግ ከመሯሯጥ መቆጠብ (ለዚህም የአጫሉን ሞት ተከትሎ በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች በግፍ መገደላቸው እየታወቀ፣ ከአንድ ሺ በላይ ቤቶች እና ከ200 በላይ መኪኖች መቃጠላቸው እየታወቀ በመላው አለም በሚገኙ የኢትዬጲያ ኤምባሲዎች ለሃጫሉ ሀውልት ማሰሪያ ገንዘብ አዋጡ እየተባለ መጠየቁ የፖለቲካ ቁማር እንጂ ሌላ ምን ይባላል?)፣
– ተጠርጥረው ለተያዙ ሰዎች ተገቢውን የሕግ ጥበቃ ማድረግ እና ነጻና የተፋጠነ የፍትህ ሂደት መኖሩን ማረጋገጥ፣
ባጠቃላይ መንግሥት ከሕግ ውጪም ቢሆን በተራዘመው ቀሪ የሥልጣን ጊዜው እንደ ባተሌ ሴት ሰላሳ ድስት ጥዶ ነገሮችን ሁሉ እያደር ገሚሱ ጥሬ፣ ገሚሱ ብስል እና ገሚሱ ያረረ እንዳይሆን ዋነኛ ትኩረቱን ኮቪድን መከላከል፣ የጠፋውን የሕግ የበላይነት ማስፈን፣ አገራዊ መግባባትን መፍጠርና ነጻና ፍትሐዊ ምርጫ ለማካሄድ የሚያስፈልጉ ቅድመ ዝግጅቶችን ከወዲሁ ማከናወን ይኖርበታል።
ይች አገር ሌላ የእልቂት እና የግጭት ሰኔን ልታስተናግድ አይገባም። ከሁለቱ ሰኔዎች ያልተማረው መንግስት በ3ኛው ሰኔ ብዙ በሰውና በንብረት ላይ ኪሳራ ላስከተሉ ችግሮች አገሪቱን ዳርጓታል። አራተኛው ሰኔ ትንሳያችን ካልሆነ መጥፊያችን ይሆናል።
Filed in: Amharic