>

ከአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ(አብን) የተሰጠ ወቅታዊ መግለጫ

ከአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ(አብን) የተሰጠ ወቅታዊ መግለጫ


በአባሎታችን ላይ እስራትን በጅምላ እየፈፀመ ካለው የመንግስት ስልጣንን ከያዘው የብልፅግና ፖርቲ ጋር አብረን ጉባዔ መቀመጥ የሚቻለን እንዳልሆነ እየገለፅን በቀጣይም ሌሎች የትግል አማራጮችን ለመተግበር የምንገደድ መሆኑን እናውቃለን!
 
የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ(አብን) ጥቅምት 18 እና 22 የጠራውን ሰልፍ ለሕዝባችን ሰላምና መረጋጋት ሲባል መሰረዙ ይታወቃል።
ሆኖም በትላንትናውና በዛሬው ዕለት የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት በንቅናቄአችን አባላትና ደጋፊወች እንዲሁም በወጣቶች ላይ እስር፣ ወከባና ማስፈራራቱ ተጠናክሮ መቀጠሉን ተገንዝበናል።
በአመራሮቻችን፣ በአባላቶቻችንና በደጋፊዎቻችን ላይ እየተፈፀመ ያለው ያልተቋረጠ ወከባ እንዲቆም፣ ለሕገ-ወጥ እስር የተዳረጉት ሁሉ በአስቸኳይ እንዲፈቱ አሳስበናል።
ቀደም ሲል እንደገለፅነው መንግስትም ማሳሰቢያችንን ተቀብሎ እንደሚፈፅም ስምምነቱን ገልፆ ነበር። እኛም ሕዝባችን ቀጣዩን ኺደት በግልፅ ለመከታተል ይችል ዘንድ በወቅቱ አሳውቀናል። ሕዝባችን በቀጣዩ ሁሉ ዳኝነቱን እንዲሰጥ ለማስቻልና ለውይይቶች በር ለመክፈት በሚል ምናልባት ከተለመደውና እንደድርጅት ለኛ ጠቃሚ ከነበረው አሰራር አለፍ ብለን ጭምር ለመግለፅ ሞክረናል።
ሆኖም አሁን ጉዳዩን የሚከታተሉ የድርጅታችን አመራሮች እስካሁን በተግባር የተለወጠ ነገር እንደሌለና ችግሮቹ ተባብሰው እንደቀጠሉ፣ የክልሉ መንግስት ስምምነቱን አለማከበሩን አረጋግጠዋል።
አሁንም ይህ አሉታዊ ድርጊት እንዲቆም፣ የክልሉ መንግስትም የሕዝባችንን ሰላም ከሚያደፈርስ ማንኛውም ተግባር እንዲታቀብ አብን እያሳሰበ የታሰሩ የንቅናቄአችን አባላት እንዲሁም ወጣቶች እስከ ነገ እኩለ ቀን ድረስ ከእስር የማይፈቱ ከሆነ ከዚህ በፊት ለተሻለ አገራዊ ሰላምና መግባባት ሲባል ከኦሮሞ ድርጅቶችና ከብልፅግና ጋር የፈረምነው ስምምነት አካል የሆነውና ከነገ ጀምሮ ለሁለት ቀናት በናዝሬት ከተማ ከሚካሄደው የአማራ-ኦሮሞ ኃይሎች የጋራ መድረክ የምንወጣ መሆኑን ከወዲሁ ማሳወቅ እንወዳለን።
በተለይ ለአጠቃላይ ተግዳሮቶቹን በተለይም እስራቱን እየፈፀመ ካለው የመንግስት ስልጣንን ከያዘው የብልፅግና ፖርቲ ጋር አብረን ጉባዔ መቀመጥ የሚቻለን እንዳልሆነ እየገለፅን በቀጣይም ሌሎች የትግል አማራጮችን ለመተግበር የምንገደድ መሆኑን ለማሳወቅ እንወዳለን።
Filed in: Amharic