>

‹‹ኢዜማ አዲስ አበባ ላይ እንጣመር ብሎን ጥያቄውን ውድቅ አድርገንበታል...!!!››   (የአብን  አመራር ዶ/ር ደሳለኝ ጫኔ)

‹‹ኢዜማ አዲስ አበባ ላይ እንጣመር ብሎን ጥያቄውን ውድቅ አድርገንበታል…!!!›› 
 የአብን  አመራር ዶ/ር ደሳለኝ ጫኔ 

 የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትሕ (ኢዜማ) ከፍተኛ አመራሮቹን ልኮ አዲስ አበባ ላይ ድምጽ መከፋፈል እንዳይኖር ‹‹አብረን በጥምረት እንሥራ ቢልም ጥያቄውን ውድቅ አድርገነዋል» ሲሉ የቀድሞው የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ ሊቀመንበር ዶክተር ደሳለኝ ጫኔ ተናግረዋል፡፡
ዶክተር ደሳለኝ ኢትዮ ኒውስ ከተባለ የኦንላይን ሚዲያ ጋር ባደረጉት ቆይታ ከኢዜማ በኩል ተነስቷል ያሉትን የአብረን እንሥራ ጥያቄ ውድቅ ለማድረጋቸው ምክንያት ነው ያሉት ‹‹አንዳንድ የኢዜማ አመራሮች ያላቸው የኢትዮጵያዊነት አመለካከትና የአማራን ሕዝብ በሚመለከቱበት መነጽር ደስተኛ ስላልነበሩ›› መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡
የሁለቱ ፓርቲ አባላት ከሰሞኑ በማኅበራዊ ትስስር መድረኮች የቃላት ምልልስ ውስጥ ገብተው የተስተዋሉ ሲሆን፣ ዶክተር ደሳለኝ ይህንኑ በቆይታቸው አንስተውታል፡፡
‹‹ግብዝነት አለባቸው›› የሚሏቸው የኢዜማ ፓርቲ ሰዎች ባልደራስን የአብን የአዲስ አበባ ተወካይ ብሎ እስከመተቸት መድረሳቸውን ያነሱት ዶክተር ደሳለኝ፣ የኢዜማ ሰዎች ወደዚህ ዓይነት ሁኔታ ውስጥ የገቡት ‹‹ተስፋ አድርገውበት የነበረው አዲስ አበቤ የአብንና ባልደራስን ጥምረት በስፋት በመቀበሉ ተደናግጠውና ብስጭት ውስጥ ገብተው ነው›› ብለዋል።
ዶክተር ደሳለኝ አክለውም አብን ከተለያዩ ፓርቲዎች ጋር በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ አብሮ ለመሥራት ሞክሮ የተሻለ ፍሬ ያፈራው ከባልደራስና መኢአድ ጥምረት ጋር እንደሆነ በማመልከት፣ ጥምረቱን ‹‹ፓርቲያቸውም ሆነ ደጋፊዎቻቸው የተደሰቱበት›› መሆኑን ገልጸዋል።
እኛና ባልደራስ አዲስ አበባ ላይ ሰፊ ሕዝባዊ መሠረት አለን ሲሉ የተናገሩት የአብን አመራሩ፣ ‹‹60 በመቶ የአዲስ አበባ ነዋሪ አማራ ነው ወይም ራሱን በአማራነት የሚገልፅ ነው›› ያሉ ሲሆን፣ ‹‹ከዚህ 60 በመቶው ውስጥ ሰፊው ቁጥር አብን ይወክለኛል ብሎ ያስባል››፣ ‹‹ራሳቸውን በኢትዮጵያዊነት የሚገልጹ›› አማራዎችም ባልደራስን እንደሚደግፉ አስረድተዋል፡፡
ዶክተር ደሳለኝ ጫኔ የድምጽ ክፍፍልን ለማስቀረት አዲስ አበባ ላይ በአንድ ፓርቲ ምልክት መወዳደር አዋጭ ነው ብሎ በማመን እጩዎችን እንዳቀረቡ በመግለጽ፣ ‹‹አሁን ይህን በማድረጋችን የሚያሙን ኢዜማዎች ከእነሱ ጋር ተመሳሳይ ነገር እንድናደርግ ጠይቀውን ሳንቀበላቸው ቀርተናል›› ሲሉ ተደምጠዋል፡፡
ምንጭ:- Amba Digital – አምባ ዲጂታል
Filed in: Amharic