>

የአንቶኒ ብሊንከን መግለጫ ዋና ጭብጥና የዐብይ አሕመድ ሚና (መስፍን አረጋ)

የአንቶኒ ብሊንከን መግለጫ ዋና ጭብጥና የዐብይ አሕመድ ሚና

መስፍን አረጋ


በአቶ ብሊንከን (Anthony Blinken) የሚመራው ያሜሪቃው የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ‹‹የኢትዮጵያን ግጭት ባስቸኳይ የማቆም አስፈላጊነት›› (The Urgent Need to End the Conflict in Ethiopia) በሚል ርዕስ ጥቅምት 18፣ 2014 ዓ.ም (November 4, 2021) ላይ መግለጫ አውጥቷል፡፡  

የመግለጫው ጭብጥ አንድና አንድ ብቻ ስትሆን፣ እሷም መግለጽ በማያስፈልጋቸው ግልጽ ሐቆች መካከል የተሰነቀረችው ‹‹የኢትዮጵያ መንግስት ዘር ተኮር ሚሊሻወችን ክተት ማለቱን እንዲያቆም›› (We call on the Government of Ethiopia to halt its … mobilization of ethnic militias) የምትለው ናት፡፡

ወያኔ አማራን ለማጥፋት ከከተተና ከዘመተ ወራቶች እንዳለፉት ላቶ ብሊንከን መንገር አያስፈልግም፡፡  የኦሮሞ ክልልም እንደዚሁ ባያሌ ዙሮች ያስመረቀውን ከፍተኛ ሠራዊቱን እስካፍንጫው አስታጥቆ፣ ዝግጅቱን ሙሉ በሙሉ አጠናቆ፣ በተጠንቀቅ መጠባበቅ ከጀመረ ወራቶችን ማስቆጠሩን አቶ ብሊንክን አሳምሮ ያውቃል፡፡  ስለዚህም የአቶ ብሊንከን መግለጫ የሚመለከተው አማራንና አማራን ብቻ ነው ማለት ነው፡፡ 

የአማራ ሕዝብ እስካፍንጫቸው በታጠቁት በወያኔና በኦነግ የሕልውና አደጋ ስለተጋረጠበት፣ አደጋውን ለመቀለበስ መክተት፣ መዝመት ጀምሯል፡፡  አቶ ብሊንከን ደግሞ ክተት፣ ዝመት ማለትህን አቁመህ እጅህን አጣጥፈህ ተቀመጥና አስቀድመው በከተቱትና በዘመቱት በወያኔና በኦነግ ተጨፍጨፍ ይለዋል፡፡  

የአቶ አንቶኒ ብሊንከን መግለጫ ዋና ጭብጥ ይሄውና ይሄው ብቻ ነው፡፡  የዚህ መግለጫ ፍሬ ሐሳብ ሊመነጭ የሚችለው ደግሞ ከሌላ ከማንም ሳይሆን ወያኔና ኦነግ እስካፍንጫቸው እስኪታጠቁና አማራን ለማጥፋት በወለጋና በወሎ አቅጣጫ እስኪዘምቱ ድረስ ድምጹን ካጠፋ በኋላ፣ አማራ ራሱን ለመከላከል መነሳሳት ሲጀምር፣ ባደባባይ ወጥቶ አትክተት፣ አትዝመት ካለው ከኦነጋዊው ከዐብይ አሕመድ ነው፡፡  

ደጋግሜ ለማሳሰብ እንደሞከርኩት፣ አቶ ብሊንከን የኢትዮጵያን ወቅታዊ ሁኔታ የተመለከተን ማናቸውንም መግለጫ የሚያወጣው ከዐብይ አሕመድ ጋር ከተመካከረና ቢያነስ በተወሰነ ደረጃ የሐሳብ ስምምነት ላይ ከደረሰ በኋላ ብቻ ነው፡፡  የአቶ ብሊንከን መልዕከተኞች ሳመንታ ፓወርና ጀፈሪ ፌልትማን አዲስ አበባ ሲመጡ፣ ዐብይ አሕመድ በአካል አግኝቶ የማያነጋግራቸው፣ በስልክ የጨረሰውን ሻጥር ለማስተባበልና የአማራን ሕዝብ ለማታለል ሲል ብቻ ነው፡፡   

በነገራችን ላይ ከያኒ ታሪኩ ጋንኪሲ (ድሽታጊና) አትክተቱ፣ አትዝመቱ ብሎ ባደባባይ እንዲቀሰቅስ ያሳመነውና ያመቻቸለት ራሱ ዐብይ አሕመድ ቢሆን እንጅ ባይሆን አይገርመኝም፡፡  የዐብይ አሕመድን ያጭበርባሪነት ክሂሎት አለማድነቅ አይቻልም፡፡  ዘመቻን የሚቃወም መልዕክት በታዋቂ ከያኔ ለማስተላለፍ ሲል፣ ለዘመቻ የሚያነሳሳ አስመስሎ ሰልፍ በመጥራት፣ ብዙ ሺ ወጣቶችን ባደባባይ የመሰብሰብ ሐሳብ ሊመጣለት የሚችለው ሰይጣን ወይም የሰይጣን ቁራጭ ብቻ ነው፡፡ 

ዐብይ አሕመደ ከመቀሌ ለቆ የወጣብትን ምክኒያት በተጠየቀ ቁጥር ርስበርሳቸው የሚቃረኑ የተለያዩ መልሶችን እየሰጠ የሚዘበራርቀው፣ እየዋሸ ስለሆነ ነው፡፡  የሁኔታወች ሂደት በግልጽ የሚያመላክተው ደግሞ፣ ከመቀሌ ለቆ የወጣው፣ ወያኔ እስከ ደብረብርሃን ድረስ ዘልቆ የአማራን ክልል በሻሻ እንዲያደርግ ከወያኔ ጋር ተስማምቶ እንደሆነ ነው፡፡   አሁን ላይ ደግሞ በከያኒወች አማካኝነት ስለ ድርድር የሚሰብከው፣ ወያኔ ደብረብርሃንን ሊቆጣጠርና ሊዘርፍ ስለተቃረበ፣ ዘርፎ እንደጨረሰ ወዲያዉኑ ድርድሩን ይፋ ለማድረግ የአማራን ሕዝብ ስነልቦና ለማዘጋጀት ነው፡፡   

አበው እንደሚሉት እጅግም ስለት አፎት ይቀዳል፡፡  ዐብይ አሕመድ እጅግ የተዋጣለት አጭበርባሪ ቢሆንም፣ አጭበርብሮ እንደኖረ ተጭበርብሮ ይሞታል፣ ወያኔም ከሱ ያላነሰ አጭበርባሪ ነውና፡፡  ዐብይ አሕመድ አማራን ለማጥፋት የሚከተለው መንገድ ባላሰበው አቅጣጫ ወስዶት እሱን ራሱን እንደሚያጠፋው ሳይታለም የተፈታ ነው፡፡  መሠረታዊው ጥያቄ ግን ዐብይ አሕመድ የሚጠፋው አማራን ካጠፋ በኋላ ነው ወይስ ሳያጠፋ በፊት የሚለው ነው፡፡  ይህን ጥያቄ መመለስ የሚችለው ደግሞ ሌላ ማንም ሳይሆን የአማራ ሕዝብ ብቻ ነው፡፡  

የአማራ ሕዝብ ትልቁ ጠላት ወያኔም፣ ኦነግም ሳይሆን፣ ባጭበርባሪነት እጅጉን የተካነው፣ በወያኔ ጉያ ውስጥ በማደግ በአማራ ጥላቻ ጥርሱን የነቀለው፣ በጨካኝነቱ ወደር የሌለው፣ ሰይጣናዊው ዐብይ አሕመድ ነው፡፡  ይህ ኦነጋዊ ሰይጣን እስካልተወገደ ድረስ፣ የአማራ ሕዝብ መቸም ቢሆን እፎይታ አያገኝም፡፡ 

በመጨረሻም ምክር ቢጤ ለብአዴናውያን፡፡  ዐብይ አሕመድ አማራን አዳክማለሁ ብሎ ራሱን አዳክሟል፡፡  እስኪሞት ከማይለየው ከማጭበርበር ችሎታው ውጭ አሁን ላይ ይህ ነው የሚባል አቅም የለውም፡፡ በተለይም ደግሞ በማጭበርበርና በማሳመን (convince and confuse) ካልሆነ በስተቀር በነ ዶክተር አምባቸውና ጀነራል አሳምነው ላይ የፈጸመውን ዳግመኛ የመፈጸም ችሎታ የለውም፡፡  ስለዚህም እንደስካሁኑ አትፍሩት፡፡  ቆፍጠን ብላችሁ እምቢ አሻፈረኝ ብትሉት፣ አምቅ አቅሙ ወደር የሌለው ሰፊው የአማራ ሕዝብ በነቂስ እንደሚደግፋችሁ ስለሚያውቅ፣ ወያኔን ከሚለማመጠው ይበልጥ ይለማጣችኋል እንጅ ዝንባችሁን እሽ አይልም፡፡  ቢያንስ፣ ቢያንስ ግን አንመራዋለን ለምትሉት ለአማራ ሕዝብ ብላችሁ ሳይሆን ለገዛ ቆዳችሁ ብላችሁ የሚከተለውን ባጽንኦት ንገሩት፡፡  ወያኔ የፌደራል መንግሥትን ጣልቃ ሳይስገባ ትግራይን ወክሎ እስከተደራደረ ድረስ፣ በአማራ በኩል የምንደራደረው እኛ የአማራ ክልል አመራሮች እንጅ አንተን ፌደራለኛውን ምንም አያገባህም በሉት፡፡  አለበለዚያ ግን ድርድሩ ባለቀ ማግስት እያንዳዳቸሁ እየተለቃቀማችሁ፣ ባልሰራችሁት ወንጀል የጦር ወንጀለኞች ተብላቸሁ እንደሚፈረድባችሁና የተወሰናችሁት በስቅላት እንደምትቀጡ ቅንጣት አትጠራጠሩ፡፡  

Mesfin Arega

mesfin.arega@gmail.com

Filed in: Amharic