>
5:13 pm - Tuesday April 20, 9926

"ኑ ቀብዳችሁን ውሰዱ፤ ለአሸባሪውም አጥልቁለት....!!!" ዶክተር በድሉ ዋቅጅራ

“ኑ ቀብዳችሁን ውሰዱ፤ ለአሸባሪውም አጥልቁለት….!!!”

ዶክተር በድሉ ዋቅጅራ

.


.
የምእራባውያን የብዙሀን መገናኛዎች፣ አልጃዚራንም ጨምሮ የጠ/ሚንስትራችንን ወደ ግንባር መዝመት ‹‹የኖቤል ሽልማት አሸናፊው. . . ›› በሚል አሹዋፊ ቅጽል አጅበው ዘገቡት፡፡
.
ለመሆኑ የሱዳንን ተቀናቃኞች አስማምቶ ሰላም ስላወረደ፣ ከኤርትራ እርቅ አውርዶ የሀያ አመት ባላንጣነትን ስለፋቀ፣ ደቡብ ሱዳንን ስላሸማገለ፣ ለአስርታት በስደት የቆዩ ተቃዋሚዎችን ያለ ቅድመ ሁኔታ ወደ ሀገራቸው ያስገባ፣ ዛሬ ሀገር ለማፍረስ የሰይጣን ፋስ ይዘው ያገኙትን የሚቆርጡ የህወሀት የሀያ ሰባት አመት መሪዎች በይቅርታ የዘረፉትን እንዲበሉ የፋቀደ፣ . . . ለዚህ አይደለምን ጠ/ሚንስትራችን ኖቤል የተሸለመው?
.
ለካ ኖቤሉ የሰላም ስራ ማረጋገጫ ሳይሆን፣ የቅኝግዛት ቀብድ ነበር፡፡ አዎ፣ መሪያችን ‹‹ለምእራባውያን ተላላኪ አልሆንም›› ሲል ለምእራባውያኑ እርግብነቱ አበቃ፣ ቁራ አደረጉት፤ የወይራ ዝንጣፊውን ወስደው ነፍጥ አስነክሰው ሳሉት፡፡ ወይራውን እሳት ለሚተፋው የህወሀት ሰይጣናዊ ድራጎን አስነከሱት፤ ተቃጠለ፤ ከሲኦል አመድ ተቀላቀለ፡፡
.
ህወሀት በምንም መንገድ በመንግስትነት ወይም በሰው ሚዛን ሊቀመጥ አይችልም፡፡ በኢትዮጵያ ታሪክ እንደህወሀት የሚጠላትን ሀገር የመራ መንግስት የለም፤ ይኖራልም ብዬ አላስብም፡፡ መንግስት ሆኖ፣ ሀገሩን የ1000 ኪ.ሜ የባህር በር የነፈገ፣ ከ300 ቢሊየን የአሜሪካ ዶላር በላይ የዘረፈ፣ ህዝቦችን በእኩልነት ስም በብሄር ከፋፍሎ ለማፍረስ ህልሙ እርሾ ያስቀመጠ፣ አሸባሪ ሽፍታ ሆኖ ሲጠብቀው በኖረ ሰራዊት ላይ ጭፍጨፋ ያፈጸመ፣ በተቀማው ለም መሬት እየተንገበገበ ከመኖር በቀር ለበቀል ያልተነሳው የአማራ ህዝብ ላይ አሰቃቂ እልቂትና ሰይጣናዊ ውድመት ያካሄደ፣ የአፋር ህዝብን የጨፈጨፈ፣ በመላው ሀገሪቱ የተካሄዱ የብሄር ግጭቶችን አቅዶ ያስፈጸመ፣ . . .  ወዘተ.  ይህ አሸባሪ ቡድን ዛሬ ለምእራባውያኑ ሰላማዊ እርግብ ነው፤ ህዝብ ባይኖረውም መንግስት ሊያደርጉት ተነስተዋል፡፡
.
አዎ! ጠ/ሚንስትሩ ኖቤል አይገባውም ነበር፡፡ ለአሜሪካ ፈቃድና ድርጎ የማያረግድ፣ ለግዳጃቸው የማይዘምት፣ በጣርነታቸው የማይሞት፣ አሸባሪ አሽከራቸውን በተባባሪ ባንዳዎች ሴራ ሸዋ ሮቢት ሲያደርሱት በመደራደር ወይም ሀገር ጥሎ በመፈርጠጥ ፋንታ ሊዋጋ የሚዘምት፣ እንዴት ለዚህ ሰው የምእራባውያን የቅኝ ግዛት ቀብድ፣ የኖቬል ሽልማት ይገባዋል? አይገባውም፡፡
እና፣ እባካችሁ ኑ ቀብዳችሁን ውሰዱ፤ ለህወሀትም አጥልቁለት፡፡
Filed in: Amharic