>
5:13 pm - Thursday April 19, 1364

እንደእናቴ ሣይሆን እንደሚስቴ አውለኝ! (ብሥራት ደረሰ)

እንደእናቴ ሣይሆን እንደሚስቴ አውለኝ!

ብሥራት ደረሰ

 

ይሄ የሰይጣን ሽንት ከመሰል ፀረ ኢትዮጵያ የውስጥና የውጭ ኃይሎች ጋር ኢትዮጵያን በረቀቀ መንገድ ብጥቅጥቋን ሊያወጣ  እንዴቱን ያህል እየተመሳጠረ እንደሆነ ከእውነተኛ የመገናኛ ብዙኃን እየተረዳነው የምንገኘው አሳዛኝ እውነት ነው፡፡ እነዚህ ጊዜ የሰጣቸው ፀረ ኢትዮጵያ ኃይሎች ወጧ እንዳማረላት ሴት አሁን እንዲህ እሽቅንድር ቢሉም የዘሩትን የሚያጭዱበትና የተወለዱበትን ቀን የሚረግሙበት ለነሱ ጨለማ ለኢትዮጵያ ደግሞ ወርቃማ ዘመን እየመጣ እንደሆነ ደግሞ ብቸኛ ተስፋችን አንድዬ የሆን እናምናለን፤ አምነንም ያን ብርሃናማ ዘመን በጉጉት እንጠብቃለን፡፡ ውድ ነገር በቀላሉ  አይገኝም፡፡ ዕንቁና ወርቅ የሚገኙት በብዙ ልፋትና ድካም እንደመሆኑ ነፃነትም እንዲሁ እንደኅብስተ መና ከሰማይ አትወርድም፡፡ ብዙ መስዋዕትነትን ትሻለች፡፡ ሆኖም እያንዳንዱ ድቅድቅ ጨለማ በማኅጸኑ የያዘውን የብርሃን ጸዳል ለሚረዳ ሰው ከኢትዮጵያ ተጨባጭ ሁኔታ በመነሳት መልካም ጊዜ እየመጣ እንደሆነ መገመት አያቅተውም፡፡ አሁን ካለንበት አስጨናቂ ወቅት ያልተናነሱ በርካታ የመከራ ዘመናትን ሀገራችን አሳልፋለችና የአሁኑ አዲስ አይደለም፡፡ 

አንድ አባውራ ከቤቱ ውጪ ሲያመሽ ቤተሰቦቹ  ያስባሉ፤ አብዝተውም ይጨነቃሉ፡፡ በተለይ የሰውዬው እናትና ሚስት በዚህ ረገድ የሚታወቁባቸው ሁለት የአስተሳሰብ ጎራዎች አሉ፡፡ እናት የምትጨነቀው “ልጄን ሰው ገድሎብኝ፣ ቀጥቅጠው አንዱ ጉድባ ውስጥ ጥለውብኝ … እንጂ በጤናው እንዲህ አያመሽም” በማለት ነው፡፡ (ቅናት ቢጤ የሚጠናወታት) ሚስት ደግሞ በበኩሏ “አሄሄ…. ይሄኔ ከአንዷ ኮማሪት ጋር እየተዳራ እንጂ …. ከዚያች ሴተኛ አዳሪ ጋር ዓለሙን እየቀጨ እንጂ … እንደዚህ በዋዛማ አያመሽም” በማለት ትብሰከሰካለች፡፡ ከሁለቱ አንድኛቸው ልክ የመሆን ዕድላቸው የተዘጋ ባይሆንም እውነቱን የሚያውቁት ግን አንድዬና አባውራው ብቻ ናቸው፡፡

ለማንኛውም ሀገራችንን እንደእናትየዋ ሳይሆን እንደሚስትየዋ ምኞት ያድርግልን፡፡ ጠላቶቿ መበታተኗንና መፈረካከሷን ቢመኙላትም ፈጣሪዋ ግን መቼም ቢሆን አይረሳትምና ፈጥኖ ይድረስላት፡፡ ለዚህም በርትተን እንጸልይ፡፡

አልዓዛርን በአራተኛው ቀን ከሙታን መንደር አስነስቶ የሕይወት እስትንፋስን የሰጠው የመይረም ልጅ ኢሳ፣ የእመብርሃን ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ ኢትዮጵያንም በዚህ የጭንቅ ሰዓቷ ደርሶ ጠላቶቿን የዶግ አመድ ያድርግላት፤ ለሌሎች በቆፈሩት ጉድጓድም ቀድመው ይግቡበት፡፡ ሀገራችንን ከሦስትና ከአራት ቦታ ከፍለው የተበጣጠቀች ኢትዮጵያን ለመሥራት የቋመጡ የዐውሬው ልጆች በዚህ የሰው ደም ጠጥቶ በማይጠግብ ዘንዶ ልዑካቸው አማካይነት የመጨረሻው ምዕራፍ ላይ ደርሰዋልና ፈጣሪ የደገሱትን የዕልቂት ድገስ ወደነሱ ያዙረው፡፡ ሆድ እንጂ ጭንቅላት የሌላቸውን እነዚህን ውሉዳነ አጋንንት በቶሎ ይገላግለን፡፡ በነሱ ምትክም ለሀገር የሚያስቡና ለዜጎቻቸው የሚጨነቁ እውነተኛ የሃይማኖት እረኞችንና የፖለቲካ ሰዎችን ይስጠን፡፡ ከልበ-ድፍን አምባገነኖች ባፋጣኝ ይታደገን፡፡   

ካለፈው ተነስተን የወደፊቱን ስንቃኝ ብዙ አስጨናቂ ሁኔታዎች እንዳሉ ሁሉ ተስፋ ሰጪ ነገሮችም እንዳሉ እንረዳለን፡፡ ከእያንዳንዱ ጥጋብ በኋላ ርሀብ አለ፤ ከእያንዳንዱ ድርቅና ርሀብ በኋላም ጥጋብ አለ፡፡ ከልደት ማግስት ሞት አለ፡፡ ከሠርግ ማግስትም ፍቺ አለ፡፡ ወጣትነት በእርጅና ይተካል፤ ጤናማነትም በበሽታ ይማረካል፡፡ ዕብሪትና ትምክህት ለሽንፈትና ለስክነት እጅ ይሰጣሉ፡፡ እዩኝ እዩኝ እንዳልተባለ ደብቁኝ ደብቁኝም ይባላል፡፡ ይሄ ተፈጥሯዊ አካሄድ መቼም ሊቀየር አይችልምና ጄኔራል አድሚራል አላዲን አቢይ አህመድ ቀን ሰጥቶት ሀገራችን ላይ መላ ጭቅቅቱን ስላራገፈና እንዳሻው ስለተጸዳዳ ነገሮች ባሉበት ይቀጥላሉ ማለት አይደለም፡፡ 

ስለሆነም ጨለማው ይነጋል፡፡ የመከራ ዶፍ ዝናቡም ይቆማል፡፡ ኢትዮጵያም ትነሳለች፡፡ ያኔም ስደትና መፈናቀል፣ መገዳደልና መጨካከን፣ የእንጀራ  ልጅነትና የእውነት ልጅነት፣ ላንዱ ማር ላንዱ ኮሶ መሆን …. ይቀራል፡፡  ነገር ግን የኢትዮጵያን የማይቀር ትንሣኤ የሚመኝና የሚፈልግ ሁሉ የኢትዮጵያ ጠላቶች በሸፍጥና በሤራ ተባብረው ሊያጠፉት እየተረባረቡበት የሚገኘውን ፋኖ መደገፍ አለበት፡፡ ፋኖ የአማራ ብቻ ሳይሆን የኢትዮጵያ ትንሣኤም እርሾና የሀገር መድኅን ነው፡፡ ፋኖ የምለው እውነተኛውን ፋኖ እንጂ በፋኖ ስም የሚሰማሩ ወንጀለኞችንና ነውረኞችን አይደለም፡፡ ለግል ጥቅሙ የቆመ ነውረኛና ባለጌ በየጎራው ሞልቷል፤ ከስንዴ እንክርዳድ፣ ከምርትም ግርድ አይጠፋምና በፋኖ ስም የአማራን ሕዝብና ወዳጆቹን የሚያንገላቱ ካሉ መከታተልና እርምጃ መውሰድ ተገቢ ነው፡፡ ያንን ብአዴን የሚባል ጭንጋፍም ሒሣቡን መስጠት ይገባል፡፡ አለበለዚያ ታጥቦ ጭቃ ነው፡፡ ከአማራ የሀገር ውስጥና የውጪ ዋና ጠላቶች ይልቅ የሚከፋው ጠላት በአማራ ስም ያደራጃቸው የጠላት ጉዳይ አስፈጻሚ መጋጃዎች ናቸው – ለምሣሌ ብአዴኖች፡፡ 

የሆኖ ሆኖ በሆዳቸው የሚያስቡ ሁሉ የመጨረሻ ዘመናቸው ደርሷልና ደስ ይበለን፡፡ ኢትዮጵያ እንደምትድን አዘውትረን የምንናገረውና ከልባችንም የምናምነው በፈጣሪዋ ተመክተን እንጂ የሚያድናት ኃይል በግልጽ ስለሚታይ አይደለም፡፡ የእረኛውን ዳዊትና የሰማይ ስባሪውን የጎልያድን ታሪክ እናስታውስ፡፡ የሚሆነው ልክ እንደዚያ ነው፡፡ እናም ብዙ አንጨነቅ፤ ግን ብዙ እንጸልይ፡፡ ከዐመፀኞች ጋርም አንተባበር፡፡ ሁሉም ያልፋል፡፡ ለሚያልፍ ነገር ደግሞ በሆድ አንገዛ፤ በዘር ልክፍትም አንጠመድ፡፡ የዐውሬው ተላላኪ ማንንም የማይምር እንደሆነ ሥልጣን ከያዘ ከ2010ዓ.ም ጀምሮ በሚያደርጋቸው ዕኩይ ተግባራቱ እያስተዋልን ነው፡፡ የእናቱን ልጅ አይምርም፡፡ የተራ ጉዳይ ነው፡፡ ተራው የደረሰን ሰው በምንም መንገድ ከመሬት ሳይደባልቀው አይተወውም፡፡ አብረው ከተሰለፉት መሃል አሁን ማንኛቸው ናቸው ከርሱ ጋር ያሉት? አቢይ አደገኛ ኮብራና አናኮንዳ ነው፡፡ ከመረዘ አይለቅም፡፡ ይህም የሰለጠነበት ነው፡፡ እንዲህ ያጨከነው ምናልባት በድህነት ማደጉ ሊሆን ይችላል፡፡ ድህነት ትዝ እያለ አበሳውን የሚያሳየው ሰው ሀብትም ሥልጣንም ይዞ የደረሰበትን የስኬት ጣርያ አያምንምና ብዙውን ጊዜ ራሱንና ሌሎችንም ማሰቃየቱ አይቀርም፡፡ አለመለከፍ ነው ወንድሜ፡፡ አለመረገም ነው እህቴ፡፡ እርሱ ተለክፏል፤ እኛም ተረግመናል፡፡ የርሱ ጭንቀት ወንበሩ እንጂ 120 ሚሊዮኑ ሕዝብ ጭዳ ቢሆንለት ጉዳዩ አይደለም፡፡ የተፈጠረበት ሥጋና ደም እጅግ ጨካኝ ከሆነ ንጥረ ነገር የተቀመመ ነው፡፡ ይህ ሰው በሥነ ልቦናው ዘርፍ MPD (Multiple Personality Disorder) በሚባል ደዌ የሚሰቃይና በዚያም ምክንያት ሀገርንና ሕዝብን መቀመቅ ለመክተት ቀን ከሌት የሚኳትን ብዔል ዘቡል ነው፡፡ ይህ በሽታ በአንዴ ብዙ ስብዕናዎችን (ሰዎችን) ለመሆን የመባዘን ሥነ ልቦናዊ ደዌ ነው፡፡ በጠበል ከሆነ እንጂ በምንም ዓይነት ዘመናዊም ሆነ ባህላዊ ህክምና አይድንም፡፡ …. ሰላም ለሀገራችን፡፡ ለደጉ ዘመን ያብቃን፤ ዘመነ ፍዳውን ያሳጥርልን፡፡

 

Filed in: Amharic