>
5:13 pm - Friday April 20, 3759

ዌንዲ ሸርማን እየገመዱት ያለ ድር፣ [ከፕሮፌሰር አለማየሁ ገብረማርያም-ትርጉም በነጻነት ለሀገሬ]

As Ethiopia votes, what’s ‘free and fair’ got to do with it? [By Terrence Lyons ]የዩኤስ አሜሪካ ከፍተኛ የዉጭህ ፖሊሲ አስተዳዳሪ የሆኑት ማዳም ዌንዲ ሸርማን እ.ኤ.አ ግንቦት 1/2015 ለዋሽንግተን ፖስት በላኩት ደብዳቤ “ባደረግሁት ንግግር ላይ ስም የማጥፋት ድርጊት ፈጽሟል” በማለት በአርታኢ/ኢዲቶሪያል ቦርዱ ላይ ዘለፋ አካሂደዋል፡፡  የጉዳዩ መነሻ የሆነው  ዌንዲ ሸርማን እ.ኤ.አ ሚያዚያ 16/2015 በኢትዮጵያ በመገኘት ተደርጎላቸው በነበረው የፕሬስ ኮንፈረንስ ላይ በተናገሩት እና በሰጡት ትርጉም ላይ ነው፡፡

ያንን ጉዳይ “ዌንዲ ሸርማን እና ስኬት አልባው የኢትዮጵያ ምርጫ“ በሚል ርዕስ ከዚህ ሳምንት በፊት ባቀረብኩት ትችት ላይ በስፋት እና በዝርዝር ገልጨው ነበር፡፡

ኤዲቶሪያል ቦርዱ ስለወይዘሮዋ ጉዳይ እንዲህ የሚል ዘገባ አቅርቦ ነበር፣ “ዌንዲ ሸርማን እ.ኤ.አ ሚያዚያ 16/2015 አዲስ አበባን እየጎበኙ በነበሩበት ጊዜ ‘ኢትዮጵያ ወደፊት ነጻ፣ ፍትሀዊ እና ታማዕኒነት ያለው ምርጫ ታካሂዳለች የሚል እምነት ያለን ሲሆን በዴሞክራሲ ጎዳና ላይ በመጓዝ ላይ ትገኛለች…‘ኢትዮጵያ በተለይ ካላት የፕሬስ ሪከርድ አንጻር የወ/ሮ ሸርማን አጉል ሙገሳ ሚዛን የሚደፋ አይደለም፡፡“ ኤዲቶሪያል ቦርዱ በኢትዮጵያ ያለው አገዛዝ የዜጎችን ሰብአዊ መብት በዘፈቀደ በስፋት በመደፍጠጥ ረገድ በቂ ማስረጃ የቀረበበት እና ፍትሀዊ ያልሆነ የምርጫ ስልትን እየተጠቀመ ያለ መሆኑን ግልጽ አድርጓል፡፡

በግልጽ ሊታይ በሚችል መልኩ ወደ ኋላ ተንሸራትተው በመሄድ እና አሳዛኝ በሆነ ሀሰትነትን በተላበሰ ሁኔታ እንዲሁም የታዛዥነት እና የሎሌነት ስብዕናን በተላበሰ መልኩ ማዳም ሸርማን “የኢትዮጵያ ዴሞክራሲ በማበብ ላይ ያለ ዴሞክራሲ ነው” በማለት የዋሽንግተን ፖሰት ጋዜጠኞች ፍትሀዊ ባልሆነ መልኩ እየዘገቡ መሆናቸውን በመክሰስ እራሳቸውን ድብቅ የኢትዮጵያ የሰብአዊ መብት ተሟጋች አድርገው አቅርበዋል፡፡

በሸርማን ለዋሽንግተን ፖስት የተጻፈውን ደብዳቤ ለበርካታ ጊዚዚያት በመደጋገም አንብቤዋለሁ፡፡ ደብዳቤው በውል እና በሰከነ አዕምሮ ታስቦበት ያልተጻፈ በመሆኑ ይህንን ደብዳቤ ባነበብኩበት በእያንዳንዱ ጊዜ የበለጠ እየተደናገርኩ ነው የመጣሁት፡፡ ሸርማን የተናገሩትን እና በካሜራ ተቀርጾ ያለውን እና “የኢትዮጵያ ዴሞክራሲ በማበብ ላይ ያለ ነው” ያሉትን ንግግር ሽምጥጥ አድርገው በመካድ አላልኩም አልወጣኝም ለማለት ፈልገው ነው? ወይስ ደግሞ በማበብ ላይ ስላለ ዴሞክራሲ በደፈናው መናገራቸውን እንጅ ስለእውነተኛ ምንነቱ እና ስለኢትዮጵያ ዴሞክራሲ ምንም የተናገርኩት ነገር የለም ለማለት ፈልገው ነውን? ወይም ደግሞ የተናገሩት ቀጥታ ለተናገሩት ነገር ተቃራኒ መሆኑን ለመናገር ፈልገው ነው?

ሸርማን በጻፉት ደብዳቤ ላይ እንዲህ ብለው ነበር፣ “ቀደም ሲል በይፋ እደተናገርኩት ሁሉ ኢትዮጵያ የተሟላ ዴሞክራሲን ለመጎናጸፍ ረዥም መንገድ መጓዝ ይኖርባታል፡፡ ፕሬዚዳንት ኦባማ እንዳቀረቡት ሀሳብ ሁሉ በቀጣይነት በቅርቡ የሚካሄደው ምርጫ አንድ እርምጃ ወደፊት የሚያስኬድ እንደሆነ ባቀረብኩት ተስፋ በተሞላ ትችቴ ላይ ግልጽ አድርጌ ነበር፡፡ በቅርቡ ባደርግሁት ጉዞም እንዲህ ብዬ ነበር፣ ‘ዴሞክራሲ እስከተነሳ ድረስ ኢትዮጵያ ዴሞክራሲን በመገንባት ላይ ያለች ገና ታዳጊ ሀገር ናት፡፡ እናም በቀጣይነት የፖለቲካ ስርዓቱ እየበሰለ ሲሄድ ለህዝቡ ትክክለኛ አማራጭ የሚያቀርብ ይሆናል፡፡‘“ ሸርማን እንዲህ ብለዋል፣ “በአፍሪካ ከየትኛውም ሀገር በላይ እስረኞች የታጎሩባት ሀገር እንደሆነች አውቃለሁ፡፡ የሲቪል ማህበረሰብ ተወካዮች ‘ችግሮችን በመፍታት ላይ ነን፣ እናም ድምጽ ለሌላቸው ህዝቦች ድምጽ እየሆንናቸው ነው፡፡‘“

የዋሽንግተን ፖስት ጋዜጣ እንዴት በእርሳቸው ጉዞ ጊዜ ስህተት ያለበትን የውንጀላ መግለጫ ይዞ ሊወጣ ይችላል?

ዋሽንግተን ፖስት በእርሳቸው የተቀረጸ የቪዲዮ ቴፕ ንግግር መሰረት የእርማት ስራ ሰርቷል፡፡ ሸርማን በካሜራ እየተቀረጹ ጋዜጣዊ መግለጫ መስጠትን ነው የመረጡት፡፡ መግለጫውንም የሰጡት በእራሳቸው ፈቃደኝነት ላይ በተመሰረተ ሁኔታ ነው፡፡ በኢትዮጵያ በመጨረሻ ባደረጉት ጉዞ ጊዜ እና በመጨረሻው በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ሙሉውን በመጀመሪያ፣ በመካከል ወይም ደግሞ በመጨረሻ ለመስጠት ምርጫ አላደረጉም ነበር፡፡

ሸርማን በአሁኑ ጊዜ አፋጣጭ በሆነ ትችት፣ በህዝብ ዘንድ ታላቅ ነቀፌታ እና አስከፊ ውግዘትን በመጋት ላይ ይገኛሉ፡፡ ነገሮችን በማለሳለስ እና በመቀባባት ትችቶችን በመዋጥ ላይ ይገኛሉ፡፡

ሸርማን በተናገሩበት የጊዜ ሰሌዳ እና በተናገሩበት ጊዜ ሀሳባቸውን በመግለጽ ጥንቃቄ ማድረግ እና በእርሳቸው ንግግር ላይ የነበረውን ዘለፋ እያጋነኑ ማቅረባቸው ለመሳሳታቸው አንድ ማሳያ ነገር ነው፡፡

ሸርማን አዲስ አበባ ለስብሰባ በተቀመጡበት ጊዜ በጻፉት ደብበዳቢያቸው ላይ እንዲህ የሚል ጽሁፍ አስፍረው ነበር፣ “የፖለቲካ ምህዳሩ እየጠበበ መምጣቱ፣ የነጻው ፕሬስ ጋዜጠኞችን በቁጥጥር ስር ማዋል እና ማሰር እንዲሁም የሰላማዊ አመጸኞችን አንደበት ለመሸበብ ሲባል የጸረ ሽብር ህጉን ከህግ አግባብ ውጭ የመጠቀሙ ሁኔታ አሳስቦኛል፡፡“

ሸርማን ይህንን አሳስቦኛል የሚለውን አባባላቸውን የተናገሩት እ.ኤ.አ ሚያዚያ 16/2015 ይህንን መግለጫ ከመስጠታቸው በፊት ነበርን? ይህ ከሆነ “የፖለቲካ ምህዳሩ እየጠበበ መምጣቱ፣ የነጻው ፕሬስ ጋዜጠኞችን በቁጥጥር ስር ማዋል እና ማሰርን በማስመልከት እ.ኤ.አ ሚያዚያ 16/2015 በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ለምንድን ነው ያላቀረቡት? እነዚህ ጉዳዮች  ጋዜጣዊ መግለጫ በሰጡበት ወቅት ስለልማት እና ሽብር ማንሳታቸው ብቻ በቂ ነበርን?

በጉዟቸው ማጠናቀቂያ ላይ ጉዳዩ አሳስቦኛል የሚለው አባባል የሰብአዊ መብት ጉዳይ እ.ኤ.አ ከሚያዚያ 16/2015 በኋላ እና ትችታቸውን አቅርበው ከተመለሱ በኋላ ነውን?

እ.ኤ.አ ሚያዚያ 16/2015 ሸርማን ጋዜጣዊ መግለጫ በሰጡበት ዕለት ፍሪደም ሀውስ/Freedom House እንዲህ የሚለውን የእራሱን መግለጫ አውጥቶ ነበር፣ “ኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊ ካልሆኑ የአፍሪካ ሀገሮች መካከል አንዷ ናት፡፡ ሸርማን ይህንን በቀጣዩ ወር አጋማሽ በኢትዮጵያ የሚካሄደውን ምርጫ ታማዕኒነት ያለው ብለው በመጥራት የኢትዮጵያ መንግስት ዜጎቹ ስላላቸው የምርጫ መብት ፍጹም በሆነ መልኩ የመነፈጉን ሁኔታ አጽድቀው ባርከውለታል፡፡ ይኸ አባባል ብቻ መንግስት ድፍረቱን እንዲያገኝ እና በሰላማዊ ዜጎች ላይ የሚያደርገውን አፈና በተጠናከረ መልኩ እንዲያካሄድ ግፊት አድርገዋል፡፡   “

ሸርማን ጋዜጣዊ መግለጫውን ከሰጡ እና ከጉዟቸው በኋላ ነው ይህንን አባባላቸውን አጽንኦ በመስጠት መናገር የፈለጉት?

ሸርማን አ.ኤ.አ ሚያዚያ 16/2015 በቪዲዮ ቴፕ በተቀጸ ጋዜጣዊ ንግግራቸው ላይ እንዲህ ብለው ነበር፣ “ከኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ከቴዎድሮስ አድሀኖም ጋር በኢትዮጵያ እየተመዘገቡት ስላሉት እጅግ በርካታ ስለሆኑት የልማት ግቦች እና ስኬቶች ብቻ ሳይሆን ስለሌሎች ጉዳዮች መጠነ ሰፊ የሆነ ውይይት አድርገናል፡፡“ ሸርማን የፖለቲካ ምህዳሩ እየጠበበ ስለመምጣቱ፣ የነጻው ፕሬስ ጋዜጠኞችን በቁጥጥር ስር ስለማዋሉ እና በየእስር ቤቶቹ ስለመታጎራቸው እንዲሁም የሰላማዊ የፖለቲካ እስረኞችን አንደበት ለመሸበብ ሲል የጸረ ሽብር ህጉን ከህግ አግባብ ውጭ በመጠቀም ገዥው አካል እያደረገ ስላለው ህገወጥ ጉዳይ አንዲት ቃል ትንፍሽ የማለት ድፍረቱ አልነበራቸውም፡፡

እ.ኤ.አ ሚያዚያ 17/2015 በዩኤስ ኤምባሲ በአዲስ አበባ በወጣው የፕሬስ መግለጫ ስለሸርማን እንዲህ የሚል ዘገባ ሰፍሮ ነበር፣ “ስለኢትዮጵያ ልማትን ጨምሮ ስለምጣኔ ሀብት እድገት፣ ስለጸጥታ እና ዴሞክራሲን ከመገንባት አኳያ ስለሚያስፈልጉ ፍላጎቶች በበርካታ ጉዳዮች ላይ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋር መጠነ ሰፊ የሆነ ውይይት አድርገዋል፡፡“ የፖለቲካ ምህዳሩ እየጠበበ ስለምምጣቱ የነጻው ፕሬስ ጋዜጠኞችን በቁጥጥር ስር ስለማዋሉ እና በየእስር ቤቱ ስለማጎሩ እንዲሁም የጸረ ሽብር ህጉ በተሳሳተ መንገድ ሰላማዊ የፖለቲካ ተቀናቃኞችን ለማጥቂያነት እየዋለ ስለመሆኑ ጉዳይ አንዲትም ቃል ትንፍሽ አላሉም፡፡

ሸርማን ከአገዛዙ ባለስልጣኖች ጋር በርካታ በሆኑ ጉዳዮች ላይ ውይይት አድርገዋል፣ ሆኖም ግን የፖለቲካ ምህዳሩ እየጠበበ ስለመምጣቱ፣ የነጻው ፕሬስ ጋዜጠኞችን በቁጥጥር ስር ስለማዋሉ እና በየእስር ቤቱ ስለማጎሩ እንዲሁም የጸረ ሽብር ህጉ በተሳሳተ መንገድ ሰላማዊ የፖለቲካ ተቀናቃኞችን ለማጥቂያነት እየዋለ ስለመሆኑ የሚያሳስባቸው መሆኑን ብቻ ገልጸው አልፈዋል፡፡

ሆኖም ግን ያሳስበኛል የሚለው አባባል በተጨባጭ ምን የሚፈይደው ነገር ይኖራል?

በዲፕሎማሲ ቋንቋ ንግግር ላይ የሚነገር ሆኖም ግን አንድ የሚያበሳጨኝ እና እብድ እንድሆን የሚያደርገኝ ቃል አለ፡፡ ያም ቃል “ያሳስበኛል” የሚለው ነው፡፡ የፖለቲካ ምህዳሩ እየጠበበ ስለመምጣቱ የነጻው ፕሬስ ጋዜጠኞችን በቁጥጥር ስር ስለማዋሉ እና በየእስር ቤቱ ስለሚታጎሩ ዜጎች እንዲሁም የጸረ ሽብር ህጉ በተሳሳተ መንገድ ሰላማዊ የፖለቲካ ተቀናቃኞችን ለማጥቂያነት እየዋለ ስለመሆኑ ጉዳይ ያሳስበኛል ሲባል በተግባራዊ ትርጉሙ ምን ማለት ነው?

ለበርካታ ዓመታት የአሜሪካ የመንግስት መምሪያ እና ኋይት ሀውስ በኢትዮጵያ እየተፈጸሙ ስላሉት የሰብአዊ መብት ጥሰቶች ያሳስበኛል የምትለዋን ቃል በተደጋጋሚ ሲጠቀሙ ቆይተዋል፡፡ ባለፉት አስርት ዓመታት በርካታ ደርዘን በሚሆኑ መግለጫዎች ላይ ሲባል የቆየውን ስመዘገብ መቆየቴ የሚታወስ ነው፡፡

እንዴት ነው አንድ ሰው በሺዎች የሚቆጠሩ የፖለቲካ እስረኞች በማጎሪያ እስር ቤት ገብተው በሚማቅቁበት ሁኔታ፣ ሌሎች በሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎች ከህግ አግባብ ውጭ በሚገደሉበት፣ ለቁጥር የሚያዳግቱ ዜጎች በሚሰቃዩበት ሁኔታ እና ሌሎች በተጠናከረ መልኩ የፖለቲካ ደባ እና ግፍ በሚፈጸምባቸው ሁኔታ “ጉዳዩ አሳስቦኛል” የሚል መግለጫ ሊሰጥ የሚችለው?

ጉዳዩ አሳስቦኛል ማለት ስለሰብአዊ መብት ረገጣ ጉዳይ የአዞ እንባ ማንባት ማለት ነውን?

ጉዳዩ አሳስቦኛል ማለት ስለሰብአዊ መብት ማውራት ማለት ነውን?

በሰብአዊ መብት ላይ ጨዋታ መጫወት ማለት ነውን?

ስለሰብአዊ መብት የይስሙላ ንግግር እና ዲስኩር ማሰማት ማለት ነውን?

ጉዳዩ አሳስቦኛል የሚሉትን በደርዘኖች የሚቆጠሩ የዩኤስ አሜሪካ የፖሊሲ መግለጫዎችን በማጥናት እንዲህ የሚለውን የተቃራኒ ትርጉም ይሰጣል ወደሚል መደምደሚያ ላይ ደርሻለሁ፣ “ስለኢትዮጵያ የሰብአዊ መብት አጠባበቅ ሁኔታ ጉዳያችን አይደለም፡፡“ የዩኤስ በኢትዮጵያ ውስጥ ስላለው የሰብአዊ መብት ውይይትን አስመልክቶ የአሜሪካ ፖሊሲ አውጭዎች ስለዚህ ሀረግ አጠቃቀም ያላቸውን እምነት በማስመልከት አንድ ትችት አቀርባለሁ የሚል እምነት አለኝ፡፡

ማዳም ሸርማን ግንቦት ሰባትን በማውገዝ እና ጥላሸት በመቀባት እንደ አሸባሪ ቡድን ድርጅት  በመቁጠር ያን ያህል የአየር ሰዓት መፍጀታቸው ሆኖም ግን በጨቅላው የኢትዮጵያ ዴሞክራሲ በየዕለቱ እጅግ በጣም አስደንጋጭ የሆነ የሰብአዊ መብት ድፈፍጠጣ እየተፈጸመ እየተመለከቱ ጉዳዩ አሳሰስቦኛል በማለት ማለፋቸው በጣም አስደንጋጭ ሁኔታ ነው፡፡

ሸርማን ስለሰብአዊ መብት አጠባበቅ፣ ስለፖለቲካ እስረኞች ወይም ደግሞ ስለመልካም አስተዳደር ባደረጓቸው ይፋ የፕሬስ መግለጫዎች ሁሉ አንድም ቃል ትንፍሽ አላሉም፡፡ ሸርማን እነዚህን ጉዳዮች በይፋ ሳይሆን በግል መልዕክት ያስተላለፉ መሆናቸውን እንድንቀበል ለማሳመን ይሞክራሉ፡፡

የዋሽንግተን ፖስት ኤዲቶሪያል ቦርድ ዓይኖቹን ጨፍኖ፣ ጆሮዎቹን ደፍኖ ወ/ሮ ሸርማን ስለሰጡት መግለጫ የጻፈው ስህተት መሆኑን አምኖ ይቅርታ መጠየቅ ይኖርበታልን?

እነርሱ ያላሉትን እና ያልተናገሩትን በስህተት ግንዛቤ እንደተወሰደ መቆጠሩ፣ የሌለ ባህሪ እንዳላቸው ተደርጎ መወሰዱ፣ በእነርሱ ላይ ስህተት ዘገባ መቅረቡ እና ስህተት ትርጉም መሰጠቱ በማለት አጉልተው በመናገር የሀሰት ተናጋሪዎች እና አጭበርባሪ ፖለቲከኞች መደበቂያ ምሽግ ሊሆኑ ይችላሉን?

ለወ/ሮ ሸርማን በተለየ ምክንያት ልዩ ምስጋና አለኝ፡፡ እኔ ለምሰጣቸው ኮርሶች የዲፕሎማሲ አስመሳይነት እና አጭበርባሪነት ልዩ የጥናት አካል ሆነው ሊያገለግሉኝ ይችላሉ፡፡ እስከ አሁን ድረስ የአሜሪካ ዲፕሎማቶች እና ፖሊሲ አውጭዎች ከህዝባዊ ወያኔ ሀርነት ትግራይ (ወያኔ) ወሮበላ የዘራፊ ቡድን ስብስብ አመራሮች ጋር ስለሚጫወቱት የሰብአዊ መብት ጥበቃ የቁማር ጨዋታ በርካታ ጽሁፎችን ጽፊያለሁ፡፡

የዲፕሎማሲ አስመሳይነት (የአባማ አስተዳደር የሚጠቀምባቸውን የዲፕሎማሲ አስመሳይነት ለመግለጽ ጥቅም ላይ የዋለ) የሚሉትን ቃላት የዲፕሎማሲ አጭበርባሪነት ከማለት ጋር በማዋሀድ ለመጠቀም ሞክሪያለሁ፡፡ ከዚህ በኋላ ተማሪዎቼ ተጨባጭነት ያለው ምሳሌን በመያዝ የአስመሳይ-አጭበርባሪነት ዲፕሎማሲን እና ሆን ተብሎ እና በስሌት ስለሚነገር መንታ ምላስ፣ የሸፍጥ ስምምነት እና ለመገንዘብ በሚያስቸግር ቋንቋ የማታለል፣ አሳስቶ የማዘዝ፣ የመምራት፣ የተሳሳተ ግንዛቤ የማስጨበጥ እና እውነታዎችን አዛብቶ ለህዝብ የማቅረብ የሸፍጥ ተንኮሎችን የመማር ዕድሎችን ያገኛሉ፡፡

ለዋሽንግተን ፖስት የተጻፈው የሸርማን ደብዳቤ በቁስል ላይ እንጨት የመስደድ ያህል ነው፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ “ኢትዮጵያ ገና በማደግ ላይ ያለ ዴሞክራሲ ያላት ሀገር ናት“ በማለት  የግንዛቤ ክህሎታችንን ዘልፈዋል፡፡ በአሁኑ ጊዜ ምንም ልንገነዘብ የማንችል ደደቦች እና ነፈዞች አድርገው በመቆጠር የጉዳት ሰለባ እንድንሆን አድርገዋል፡፡ እርሳቸው ያሉትን ነገር እርሳቸው እንዳላሉት፣ የሰማነውን ነገር እንዳልሰማነው አድርገን እንድናሰብ ሊያሳምኑን ይፈልጋሉ፡፡ ማንም ቢሆን ሸርማን እንደሚያስቡት እና እንደሚያምኑት እኛ ደደቦች እና ነፈዞች እንዳልሆንን ሊነግራቸው ይገባል!

ማዳም ሸርማን ሁሉንም ነገር እርግፍ አድርገው በመተው “በጣም አዝናለሁ” ቢሉ የተሻለ ነው፡፡ ሆኖም ግን አይችሉም፡፡ በእብሪት የተወጠረው ህሊናቸው ይህንን እንዲያደርጉ አይፈቅድላቸውምና፡፡ ወ/ሮ ሸርማን በሩድያርድ ኪፕሊንግ የተቋጠሩትን እንዲህ የሚሉትን የግጥም ስንኞች አስታወሱኝ፣

ሁሉንም ቃላት አላስታውስም፣

አጭር ረዥም ይሆኑ አላውቅም፣

ማራኪ ሳቢ ይሆኑ አላውቅም፣

በውበታቸው አልደነቅም፣

በአገባባቸው አልጨነቅም፡፡

ግን ቃላት ናቸው ሀረግ ስብስብ፣

ከጫፍ እሰከ ጫፍ የሚያሰባስብ፣

አዕምሮን ገዥ ስሜት የሚስብ፡፡

ስለሰው ልጅ ስቃይ የሚሉት አላቸው፣

ስለወንድ ስለሴት ዘጋቢዎች ናቸው፣

ስለውበት ሚስጥር ተራኪዎች ናቸው፣

ስለሁሉም ነገር ሁሉን ነገር ናቸው፡፡

የመኖር ጥበቡ ስልቱና ዘዴው፣

ከክፉዎች ጋራ አብሮ መኖር ነው፣

እንደሆኑት ሆኖ እንዳፈጣጠሩ፣

ከክፉዎች መልካም ከየዋሆች ጥሩ፣

ከሸፍጠኞች የዋህ ከኩሩዎች ኩሩ፣

ከግማሽ ጭራቆች በሩቅ ከሚፈሩ፣

ከግማሽ ግኡሳን በጽድቅ ከሚመሩ፣

በምድር ከሚተሙ ባየር ከሚበሩ፣

እንደሆኑ ሆኖ መኖር ነው ሚስጥሩ፡፡

እውነታው ግልጥልጥ ብሎ ሲታይ ግን በቪዲዮ ቴፕ የተቀረጸው የሸርማን ንግግር ማንም እንዲያየው፣ እንዲያነበው እና የህሊና ዳኝነቱን እንዲሰጥ ተቀምጦ ይገኛል፡፡ ሸርማን እርሳቸው የሚፈልጉትን ነገር ሁሉ ለማግኘት ሲሉ እንዲመቻቸው እያደረጉ ይናገራሉ፡፡ ሆኖም ግን ቃላቱ ሁሉ የእርሳቸው ቃላት ናቸው፡፡ በአሁኑ ጊዜ ክብር ያለው ነገር ማድረግ ያለባቸውከሆነ የእርሳቸውን ክብር ዋጥ ያድርጉ እና ይቅርታ በመጠየቅ ቃላትን ይመገቡ፡፡

ለታሪክ ሲባል ማዳም ሸርማን ለፕሬስ የሰጡት መግለጫ በቴፕ ተቀድቶ የተቀመጠው እንደሚከተው ቀርቧል፡

ለጅ-7/G-7 ስብሰባ ሲባል ከጀርመን ከሉቤክ ነው የመጣሁት፣ እናም ከሚስትሩ (ከኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቴዎድሮስ አድሀኖም ጋር በኢትዮጵያ ስለተከናወኑት በርካታ ስኬቶች ብቻ ሳይሆን ስለሁሉም የምዕተ ዓመቱ የልማት ግቦችመጠነ ሰፊ የሆነ ውይይት አካሂደናል፡፡ ኢትዮጵያከአፍሪካ አህጉር ፈጣን የምጣኔ ሀብት በማስመዝገብ ላይ ከሚገኙትሀገሮች አንዷ ናት፡፡ ኢትዮጵያ ዴሞክራሲ የሰፈነባት እና ወደፊትየሚደረገው ምርጫነጻ፣ ፍትሀዊ፣ ታማዕኒነት ያለው፣ግልጽ እና ሁሉን አካታች እንደሆነ እንዲሁም ኢትዮጵያ በቀጣይነት ዴሞክራሲን እያጠናከረችእና በየጊዜውምርጫእያካሄደች በመገስገስ ላይ ያለች ሀገር ናት፡፡ በጣም እየተሻለች እና እየተሻሻለች የመጣች ሀገር ናት፡፡

ከዚህም በተጨማሪ የጅ-7 የመወያያ ርዕሶች ስለሆኑት እና በጅ-7 ስብሰባ ላይ በአህጉሩ ስለሚከሰቱ ሁሉም አደጋዎች እና አሳሳቢ ጉዳዮች ውይይት አድርገናል፡፡ ስለሆነም ይኸ ነገር ሶማሊያን የሚያጠናክር ከሆነ ወይም ደግሞ በኢትዮጵያ ላያ ሊሰነዘር የሚችለውን አደጋ ማለትም ከአልሻባብ እስከ ቦኮሃራም፣ ከዳሽ እስከ አልቃይዳ እና ከዚህም በላይ ከኢትዮጵያ ተጨባጭ ሁኔታ እና ኢትዮጵያ አሸባሪ ብላ ከሰየመቸው ግንቦት 7 በተባለውአሸባሪቡድን ዙሪያ ሰፊ ውይይትአድርገናል፡፡ ዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ ምንም ዓይነት ቡድን ግንቦት 7 ጨምሮ በዴሞክራሲያዊ ምርጭስልጣንየያዘንመንግስት በኃይል ለመጣል መሞከር ወይም መናገር እንደማይቻል እምነት አላት፡፡ እናም እነዚህን ጉዳዮች በተሳካ ሁኔታ ተፈጻሚ ለማድረግ ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ያለንን ስራ አጠናክረን እንቀጥልበታለን፡፡

በአሁኑ ጊዜ ዓለም ከበርካታ ነገሮች ጋር ተጋፍጧል፡፡ እናም ኢትዮጵያ ጠንካራ የሆነች እና በፈጣን እድገት ላይ የምትገኝ ሀገር ናት፡፡ እናም የተረጋጋች፣ ሰላም እና ጸጥታ የሰፈነባት እንድትሆን በማረጋገጥ ብልጽግናዋ እንዲቀጥል ጥረት እናደርጋለን፡፡ እንደዚሁም የልማት አጋርነታችን ተጠናክሮ እንዲቀጥል እና ማንኛውንም የጥቃት አደጋ ለመመከት እና ልዩ ትኩረት አድርገን እንደምንሰራ እምነት አለኝ…

የዘጋቢዎችን ጥያቄ ለመመለስ ምርጫዎች በጣም ጠቃሚዎች ናቸው…ድምጽ መስጠት ጠቃሚ ነገር ነው፡፡ በምርጫው ዕለት ከምርጫ ጣቢያዎች በመገኘት ድምጽ እንድትሰጡ ሁሉንም ኢትዮጵያውያን/ት እማጸናለሁ፡፡ ሆኖም ግን እዚህ መሆኔ ደግሞ በጣም ደስ ብሎኛል ምክንያቱም በበርካታ ሁኔታዎች ኢትዮጵያ በማበብ ላይ ያለን ዴሞክራሲ የያዘች ሀገር ናት፡፡ እናም ማንኛውም ምርጫ በእኛ ሀገር እንዳለው ምርጫ ሁሉ የተሻለ እና የተሻሻለ ለነጻነት ክፍት የሆነ፣ ማንኛውም ምርጫ ፍትሀዊ፣ ነጻ እና ታማዕኒነት ያለው፣ ተቃዋሚ የፖለቲካ ቡድኖች መሳተፍ እንዲችሉ ምህዳሩ እንዳይጠብ ማድረግ እና የእያንዳንዱ ሰው የድምጽ ውጤት ትርጉም እንዳለው ግልጽ ሊሆን ይገባል፡፡ በእኛ ሀገር እያንዳንዱ ምርጫ ከጊዜ ወደጊዜ እየተሻሻለ አጠቃላይ እየሆነ እና የእያንዳንዱ ሰው መብት መከበር እንዳለበት እንዲሁም ኢትዮጵያ በአሁኑ ጊዜ እንደዚያ ያለውን ስራ በመስራት ላይ የምትገኝ ሀገር መሆኗን እናውቃለን፡፡ (አጽንኦ ተጨምሯል፡፡)

“ማታለል በጀመርንበት ጊዜ ምን ዓይነት ድር ማድራት ጀመርን!”

ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር!

ግንቦት 7 ቀን 2007 .

Filed in: Amharic