>
5:13 pm - Sunday April 18, 2979

የመረራ ክስ ምን ይነግረናል? (በዘላለም ክብረት)

 

በሰዎች የእድገት መሰላል በተለምዶ ‹ሃያዎቹ› (twentysomethings) የሚባለው የዕድሜ ክልል እጅግ ወሳኝ እንደሆኑ ብዙ ጥናት መጥቀስ ይቻላል፡፡ ሰዎች ከልጅነት ጊዜያቸው ወደ ጉልምስና የሚሸጋገሩበት ጊዜ መሆኑም ነው የወሳኝነቱ መነሻ፡፡ ይሄን ወሳኝ የዕድሜ ክልል ገና ሲጀምረው በ21 ዓመቱ ወደ እስር የተወረወረው አፍላው ወጣት መረራ ጉዲና ከ7 ዓመታት እስር በኋላ የዛኔው የደርግ ምክትል ፕሬዝደንት ፍስሃ ደስታ ‹‹እንኳን ደስ አላችሁ የኢትዮጵያ አብዮትን ለተወሰነ የታሪክ ወቅት አብረን ስንመራ ቆይተን ዛሬ አብዮታችን የላቀ ዘላቂ ድል ሲጎናፀፍ የደስታው ተካፋይ እንድትሆኑ በምህረት ፈተናችኋል›› ብለው መስከረም 02፣ 1977 ከሌሎች መቶ የሚሆኑ የፖለቲካ እስረኞች ጋር ሲለቀቅ ዕድሜው 28 ደርሶ ነበር፡፡ ወሳኞቹ ‹ሃያዎቹ› እንደዋዛ በእስር አለፉ፡፡ የደርግን አብዮታዊ ድግስ ለማድመቅ ‹በምህረት› ከእስር የተፈታው መረራ፤ ይህ ከሆነ ከ32 ዓመታት በኋላ ተመልሶ ‹ሃያዎቹን› ወዳሳለፈበት ወህኒ ከተወረወረ ይሄው አንድ ዓመት ሞላው፡፡ በእነዚህ 32 ዓመታት ውስጥ ያቋረጠውን ትምህርት አጠናቆ፣ ብዙዎችን አስተምሮ፣ እንዲሁም ‹ታሟል› የሚለውን የኢትዮጵያ ፖለቲካ ከበሽታው ያገግም ዘንድ የቻለውን ሁሉ፤ በመሰለው መንገድ አድርጓል፡፡ ለዚህ ልፋቱ ክፍያው እስር መሆኑ ደግሞ አሳዛኙ የአገሪቱ ምሥል ማሳያ ነው፡፡

መረራ አሁን እስር ቤት ነው፡፡ መረራ የታሰረበትን አንደኛ ዓመት አስመልክቶ መረራ ላይ ከቀረቡበት ሦስት ክሶች አንዱን ከነማስረጃው ዘርዘር አድርገን በማየት የክሶቹን መነሻና ዓላማ ለመመልከት ብንሞክር የመረራን ንጽሕና የበለጠ ለመረዳት እንዲሁም መረራን ለማሰር የተሄደበትን ረጅም ርቀት እንረዳለን፡፡

የፌደራል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ዶ/ር መረራ ጉዲና ላይ ሦስት የተለያዩ ክሶችን ያቀረበ ሲሆን የመጀመሪያው ክስ የፀረ-ሽብርተኝነት ሕጉ እንዲህ እንደዛሬ የሁሉም የፖለቲከኛ እስረኞች የክስ መነሾ ከመሆኑ በፊት ለብዙ የፖለቲካ እስረኞች የእስር ምክንያት ሁኖ የኖረው በወንጀል ሕጉ አንቀፅ 238 ላይ ‹‹ሕገ-መንግስቱንና ሕገ-መንግስታዊ ሥርዓቱን በኃይል ለማስወገድ መሞከር›› ተብሎ የተደነገገው ነው፡፡ ዶ/ር መረራ ጉዲና ‹‹በአጠቃላይ በአለፉት ሦስት ዓመታት ውስጥ በኦሮሚያ ክልል ውስጥ ሲካሔዱ የነበሩትን ተቃውሞዎች ሁሉ አስተባብሯል›› ተብሎም ነው ክስ የቀረበበት፡፡ ሁለተኛው የዶ/ር መረራ ክስ ከአስር ወራት ትግበራ በኋላ ለተነሳው የአስቸኳይ ጊዜ ሁኔታ መነሻ የሆነው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅን የሚያጣቅስ ሲሆን፤ ዶ/ር መረራ ‹በጥቅምትና ሕዳር 2009 አውሮፓ በነበሩበት ወቅት ቤልጅየም ውስጥ አዋጁን በመጣስ ‹‹ከአሸባሪዎች ጋር ተገናኝተዋል›› የሚልም ነው የክሱ ፍሬ ነገር በአጭሩ፡፡ ‹‹ሕገ-መንግስቱን የሚያከብር ሕገ-መንግስታዊ ሥርዓት ብቻ ነው ለአገሪቱ መድኅን የሚሆናት›› እያለ የፖለቲካ ዕድሜውን ለገፋው መረራ ጉዲና ‹‹ሕገ-መንግስታዊ ሥርዓቱን ለማፍረስ ሞክረኻል›› ብሎ ክስ ማቅረቡ የከሳሾን ማንነት ከማሳየት ባለፈ በትንተና ጊዜ ሊጠፋበት የሚገባ ጉዳይ አይደለም፡፡ በተመሳሳይ በሁለተኛው ክስ ላይ ‹ተጣሰ› የተባለው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ከተሻረ ወራት ቢያልፉትም ዶ/ር መረራ ግን ያለምንም ሕጋዊ መነሻ አስከአሁን ድረስ የተሻረው አዋጅ ተጠቅሶ የቀረበበት ክስ የዋስትና መብቱን አስከልክሎት በእስር ላይ ይገኛል፡፡

ከእነዚህ ሁለት ክሶች ባለፈ ዶ/ር መረራ ላይ በሦስተኝነት የቀረበው ክስ ነው ስለአጠቃላዩ የክሶቹ ዓላማ እና ሒደት የሚያስረዳን፡፡ ዶ/ር መረራ ከተከሰሰባቸው ሦስት ክሶች ውስጥ በሦስተኝነት የቀረበው ክስ ብዙ ነገሮችን ወደኋላ ሒደን እንድናይ የሚያደርግና የመረራን አሳሪዎች ምን ያክል ርቀት እንደተጓዙ አመላካች ነው፡፡ በዶ/ር መረራ ላይ የቀረበው ሦስተኛ ክስ ‹‹በ1996 ዓም የወጣውን የወንጀል ሕግ አንቀፅ 486/ለ ላይ የተመለከተውን በመተላለፍ›› የሚል ሲሆን፤ ዝርዝሩም፡

ተከሳሽ ጥርጣሬን የሚፈጥር የሃሰት ወሬ ለማውራት በማሰብ የኢትዮጵያና የናይጄሪያ ብሄራዊቡድን ጥቅምት ወር 2ዐዐ6 ዓም በአዲስ አበባ ስታዲየም ከቀኑ በ1ዐ፡ዐዐ ሰዓት በሚያደርጉትጨዋታ የአልሸባብ የሽብር ቡድን አባል የሆኑት እነ አብዱራህማን መሃመድ ጥቃት ለማድረስበዝግጅት ላይ እያሉ የፀጥታ ሃይሎች በነበረው ጥብቅ ጥበቃ ምክንያት የሽብር ቡድኑ አባሎችታጥቀውት የነበረውን ፈንጂ በአዲስ አበባ ከተማ ቦሌ ክ/ከ ቀበሌ ዐ1 ፈንድቶ የሽብር ቡድኑ አባሎችየሞቱ መሆኑ እየታወቀ ተከሳሽ በ21/2/2ዐዐ6 ዓም ለአሜሪካ ድምፅ ራድዮ ጣቢያ በሰጡትመግለጫ አሸባሪዎቹ አፈነዱ የተባለው የውሸትና የመንግስት ድራማ ነው በማለት የገለፁ በመሆኑበፈፀሙት ሕዝቡ በመንግስት ላይ እምነት እንዳይኖረው የሚያደርግ የሐሰት ወሬዎችን ማውራትወንጀል ተከሰዋል፡፡

የሚል ነው፡፡

ከዚህ ክስ ጀርባ ብዙ ነገሮች አሉና እያንዳንዱን የክሱን አንጓ መመልከት ስለአጠቃላዩ የክሶቹ መንፈስ ብዙ የሚለን ነገር ይኖራል፡፡

በመጀመሪያ ክሱ የቀረበበት ጊዜ አስገራሚ ነው፡፡ ዶ/ር መረራ ጉዲና በጥቅምት 21/2/2006፤ ከሦስት ዓመታት በፊት ለአሜሪካ ድምጽ ራዲዮ ተናገሩት የተባለው ሐሳባቸው ነው ‹‹ጥርጣሬን የሚፈጥር የሃሰት ወሬ ለማውራት›› የሚል ክስ ያስቀረበባቸው፡፡ ከሣሽ ከሦስት ዓመታት በላይ ምን ሲጠብቅ ቆይቶ ክሱን እንዳቀረበባቸው የሚያውቀው ራሱ ከሳሽ ብቻ ነው፡፡ ነገር ግን ይህ ሒደት የሚነግረን ከጀርባው ሲውጠነጠን የነበረው ሐሳብ ነው፡፡ የጉዳዩ አመጣጥ ባጭሩ እንዲህ ነው፡፡

ጥቅምት 03፣ 2006 ከሰዓት በኋላ የኢትዮጵያ መንግስት የዜና ምንጮች አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ በተለምዶ ቦሌ ሚካኤል እየተባለ የሚታወቀው አካባቢ ሁለት ሶማሊያዊያን ‹አሸባሪዎች› የኢትዮጵያና የናይጀሪያን ጨዋታ ለመመልከት የወጣው ሕዝብ ላይ የአጥፍቶ መጥፋት ፍንዳታ ለመፈፀም እየተዘጋጁ እያለ የአንደኛው ቦምብ ራሱ ላይ ፈንድቶ ሁለቱም ‹አሸባሪዎች› መሞታቸውን የሚገልፅ ዜና ይዘው ወጡ፡፡ በወቅቱ መንግስታዊ የዜና ማሰራጫዎች ስለሽብርተኝነት አስከፊነት የተለያዩ ዘገባዎችን ከመስራታቸውም ባለፈ፤ የተለያዩ ተቃዋሚዎችን በማናገር በዜናዎቻቸው ይዘው ወጡ፡፡ በወቅቱ አንዳንድ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላት ፓርላማው በአስቸኳይ ተሰብስቦ የፀረ-ሽብርተኝነት ሕጉን የበለጠ ጥብቅ እንዲያደርገው ጠየቁ፡፡ እንደ አንድ የተቃዋሚ ፓርቲ መሪ ዶ/ር መረራ በወቅቱ በመንግስታዊው የዛኔው ኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የዛሬው የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን ስለጉዳዩ ጥያቄ አቀረበለት፡፡ ዶ/ር መረራም ተቆራርጦ በቀረበው መልሱ “ሰው አንዳንድ ጊዜ የኢትዮጵያ መንግስት ለራሱ ፖለቲካ ብሎ የሚያደርገው ያው የለመደው ስራ ነው ይላል … አጥፍቶ ጠፊ አጥፍቶ ይጠፋል እንጂ በሜዳ ዝም ብሎ አያጠፋም” የሚል ጥርጣሬ ያዘለ መልስ ሰጡ፡፡

በወቅቱ የዜናውን ተዓማኒነት የተጠራጠሩት ዶ/ር መረራ ብቻ ሳይሆን ብዙዎች ነበሩ፡፡ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ‹የአጥፍቶ መጥፋቱን ሙከራ ሊያደርጉ ሲሉ ሞቱ› ያላቸውን በወቅቱ ስማቸው ያልተጠቀሰ (በኋላ በእነ መሐመድ አብዱራህማን እና የፌደራል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ክስ መዝገብ ላይ አብዲና ሐሰን እንደሚባሉ የተጠቀሱ) ሁለት ግለሰቦች ሬሳ በደብዛዛው ያሳየ ሲሆን፤ የትግራይ ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ትሕዴን) በበኩሉ ‹‹በአደረኩት ማጣራት በኢትዮጵያ በቴሌቪዥን ሟች ተብለው የታዩት ሁለት ግለሰቦች “ምክትል ኢንስፔክተር ሞላ መላኩ የተባሉ የፖሊስ አባልና አቶ ሞገስ አስቻለው የተባሉ ሲቪል ናቸው” በማለት መንግስታዊ ሴራ እንደሆነ ገልጾ ጉዳዩን አጣጥሎትም ነበር፡፡ በጉዳዩ ላይ ‹‹ተባብራችኋል›› በሚል ክስ ከቀረበባቸው አስር ግለሶች መካከል ቤት አከራይ በመሆን የተጠቀሱት ሁለት ኢትዮጵያዊያን ተከሳሾች ቤታቸው ውስጥ የፈነዳው ጋዝ እንደሆነና ምንም አይነት የአጥፍቶ መጥፋት ሙከራ እንዳልነበር ለፍርድ ቤት በተደጋጋሚ ማስረዳታቸውም ሌላው በጉዳዩ ላይ ጥርጣሬ የሚፈጥር ሁኔታ ነበር፡፡

ዶ/ር መረራ እንግዲህ በዚህ ሁሉ መሐል ነው በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ላቀረበላቸው ጥያቄ እንደ አንድ የፖለቲካ መሪ መልስ የሰጠው፡፡ በዚህ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ንግግር መሰረት አድርጎ የአሜሪካ ድምፅ ራዲዮ (ቪኦኤ) የአማርኛው የስርጭት ክፍል ጥቅምት 21 እና 22፣ 2006 በሁለት ክፍል የቀረበ ቃለ-መጠይቅ አቅርቦለትም ነበር፡፡ ይህ የአሜሪካ ድምፅ ራዲዮ የአማርኛው የስርጭት ክፍል ቃለ-መጠይቅም ነው ከሦስት ዓመታት በኋላ ዶ/ር መረራ ‹‹አሸባሪዎቹ አፈነዱ የተባለው የውሸትና የመንግስት ድራማ ነው›› በማለት የሃሰት ወሬን በማሰራጨት ክስ እንዲቀርብበት የሆነው፡፡ ፍንዳታው ድራማ ነበር ወይስ አልነበረም? ለመሆኑ ዶ/ር መረራስ የተባለውን ነገር አሰራጭቷል ወይ? ቢናገር የግል አስተያየቱን መስጠቱ እንዴት ወንጀል ይሆናል? የሚሉት ጥያቄዎች ተከትለው መቅረባቸው አይቀርም፡፡

በመጀመሪያ ዶ/ር መረራ ላይ በማስረጃነት ስለቀረበው የአሜሪካ ድምጽ የአማርኛ ስርጭትቃለ-መጠይቅን እንመልከት፡፡ ከቪኦኤ የድምጽ ቋት ያገኘነው የዶ/ር መረራ በሁለት ክፍል የቀረበ (ጥቅምት 21 እና ጥቅምት 22፣ 2006) የ14 ደቂቃ ቃለ-መጠይቅ ሙሉ ይዘቱ የሚከተለው ነው፡

የቃለ-መጠይቁ ርዕስ፣

‹‹የአዲስ አበባ ፖሊስ አንዳንድ ተቃዋሚዎች በቅርቡ በአዲስ አበባ የደረሰውን ፍንዳታ አስመልክተው የጥርጣሬ አስተያየት ሰጥተዋል ሲል ተቃወመ›› 

የሚል ሲሆን፤ ቃለ-መጠይቁም፡

ቪኦኤ፡ እንደምን አመሹ ዶ/ር መረራ?ዶ/ር መረራ፡ ደህና ነኝ፡፡ቪኦኤ፡ እስኪ ለኢትዮጵያ መንግሰት የሰጡት ቃለመጠይቅ ምንድን ነው? በተለይ በፀጥታ ጉዳዮችና በሽብር ላይ አስመልክቶ፡፡ዶ/ር መረራ፡ እኔ በዋናነት የኢትዮጵያ መንግስት ሽብርተኝነትንና የተቃዋሞ ፖለቲካን እያደባለቀ የሽብርተኝነት ሕጉን ተቃዋሚን ለማጥፋት ተቃውሞን ለማፈን የሚንቀሳቀስበት ሁኔታ እንጅ እውነተኛ ሽብርተኞችን መላጥቃት ለመከታተል እያደረገ አይመስልም፡፡ ብዙ ጊዜ ይደባለቅበታል፡፡ ተቃዋሚዎችን ሽብርተኞች ብሎ ብዙ ጊዜ ያስራል፡፡ ያምታታል፡፡ እንደዚህ ያለውን የተደባለቀ አድራጎቱን፡፡ ለምሳሌ አሁን የሙስሊም ማሕበረሰብ ተወካዮችን ሁለት ዓመትና ከዛ በላይ አንድ ሰው እንኳን ሳይገሉ፤ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ የሚሳተፉበት እንቅስቃሴ ነው፡፡ ነገር ግን ‹‹እንዲህ አይነት ንብረት ጠፋ››፤ ‹‹አገሪቷ በሽብር ተናደች›› … የሚል ነገር አናይም፡፡ በሰላም ጥያቄዎቻቸውን ጠይቀው በሰላም አቤቱታቸውን አቅርበው መንግስት ጆሮ ባይኖረውም በሰላም መብታቸውን ጠይቀው የሚገቡበት ሁኔታ ነው፡፡ ሽብርተኛ ማለት ደግሞ ተደብቆ የሚያቃጥል የሚያሸብር እንጅ በሰላም መብቱን የሚጠይቅ፤ በሰላማዊ ሰልፍ መብቱ እንዲከበርለት የሚጠይቅ፤ በሰላም ‹‹መንግስት ችግሮቼን ይፍታልኝ›› ብሎ የሚጠይቅ አይደለም፡፡ እንዲያውም የኢትዮጵያ መንግስት ሽብርተኞች ናቸው ብሎ የሚመድባቸው፤ የሚፈርጃቸው በፓርላማ ሁሉ የሚወስንባቸው አንዳንዶቹ ሽብርተኝነትን በዋናነት እየተዋጋች ነው የምትባለው አሜሪካ ውስጥ በሰላም እየተንቀሳቀሱ  ስብሰባዎችን እያደረጉ ፓርቲን እየሰበሰቡ የሚታገሉበት ሁኔታ ነው ያለውና አሜሪካኖቹ እንኳን (በዚህ በሽብር ዙሪያ የኢትዮጵያ መንግስት አጋር ናት የምትባለዋ) የኢትዮጵያ መንግስት ‹‹ሽብርተኞች ናቸው›. ብሎ የሚፈርጃቸውን ‹‹ሽብርተኞች ናቸው›› ብላ አልተቀበለችም፡፡ቪኦኤ፡ እነዚህ በዝርዝር ኦነግ፣ ኦብነግና፣ ግንቦት ሰባት ናቸው አይደል?ዶ/ር መረራ፡ አዎ! እና በተለይ ለተቀዋሚዎች ችግር የፈጠረው የኢትዮጵያ መንግስት ብዙ ነገሮችን ያደባልቃል፡፡ እያደባለቀ ተቃውሞን ለማፈን እየተንቀሳቀሰ በሰላም እንደሚታገሉ የምናቃቸው በቅርብ የምናቃቸውን ሰዎች መንግስትን በኃይል ለመገልበጥ ተንቀሳቅሰዋል፤ ሽብርተኝነት ውስጥ ተሳትፈዋል እየተባሉ ጋዜጠኞች ያለፕሬስ ምንም ነገር እንደሌላቸው የሚታወቁ ሰዎችን ያስራል፡፡ ዓመታትን ይፈጅባቸዋል፡፡ እና እነዚህ ደግሞ በአሜሪካ ተቋማት በነሲ.ኤን.ኤን (ሲ.ፒ.ጄ?) የሚሸለሙበት ሁኔታ ነው የሚያስራቸው፡፡ ሽብርተኞች ናቸው ወንጀለኞች ናቸው እያለ የሚያስራቸው፡፡ በዓለማቀፍ ደረጃ የሚታወቁ ተቋማት ሽልማት የሚሰጡበት ሁኔታ ነው ያለውና እኔ የኢትዮጵያ መንግስት እየገፋበት ያለው መንገድ የፀረ-ሽብር ትግሉን እንዳይጎዳ፤ ሽብርተኝነት ዙሮ ዙሮ ሁላችንም የሚጎዳ ነው እውነት ሆኖ ከመጣ፡፡ ስለዚህ ማደባለቁ ማንንም አይጠቅምም፡፡ አገሪቷን አይጠቅምም፤ መንግስትን አይጠቅምም፤ የኢትዮጵያ ሕዝቦችን አይጠቅምም፡፡ ተቃዋሚን ማሰር ከፈለገ መንግስት በሰራውና ተቃዋሚ በመሆኑ ማሰር ይሻላል፡፡ ከሽብርተኝነት ጋር እያደባለቀ የሐይማኖት መብታቸውን የጠየቁትን (እንደ እስላሞቹ አይነቱን) በሰላማዊ መንገድ እየጠየቁ እንዲያውም በርቱ ብሎ መሸለም እና ማመስገን ሲገባው፤ የኢትዮጵያ መንግስት ከሽብርተኝነት ጋር እያያያዘ የሚወስዳቸው እርምጃዎች እያስቸገሩ ነው ለወደፊቱም ትግሉን ይጎዱታል፡፡

በማለት የጥቅምት 21፣ 2006 ቃለ-መጠይቅ የተጠናቀቀ ሲሆን፤ በጥቅምት 22 የቀጠለው ቃለ-መጠይቅ ደግሞ እንደሚከተለው ነው፡

ቪኦኤ፡ ዶ/ር መረራ በቅርቡ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ተቃዋሚዎችን ማስጠንቀቂያ የሚመስል ንግግር ተናግረዋል፡፡ በእናንተ በኩል እነዚህ በመንግስት በኩል በተከታታይ የሚሰሙ በፖሊስም በሥራ አስፈፃሚውም በኩል የሚሰሙ በእናንተ ላይ ያነጣጠሩ ጥያቄዎች ላይ ምንድን ነው የእናንተ መልስ እንዴት ነው የምታዩአቸውስ፡፡ዶ/ር መረራ፡ እኛ በግልፅ በአደባባይ ሰላማዊና ሕጋዊ ትግላችንን ከመቀጠላችን ውጭ ምርጫ የለንም፡፡ ‹‹ሠላማዊና ሕጋዊ ትግላችሁን ትታችሁ ቤት ተቀመጡ›› ከሆነ ከኢትዮጵያ መንግስትም ሆነ ከምርጫ ቦርድ ፈቃድ ወስደን ድርጅት ፈጥረን ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት በኢትዮጵያ ውስጥ እንዲፈጠር የምንንቀሳቀሰው ለእዛ ነው፡፡ ሌላ ምክንያት የለንም፡፡ የኢትዮጵያ መንግስት ትልቁ ችግር ግን የሚናገረውና የሚሰራው እየተጋጨበት የተቃውሞ ፖለቲካንና ሽብርተኝነትን መለየት ያልቻለበት ሁኔታ ነው ያለው፡፡ በሰላማዊ ዜግነታቸው የሚታወቁ ከብዕር ውጭ ሌላ ነገር የሌላቸው ጋዜጠኞችን የፖለቲካ ድርጅት በተለይ ወጣት መሪዎችን የእኛንም አባላት ጭምር መንግስት ሲያስር ነበር፤ አሁንም እስር ቤት እየማቀቁ ነው፡፡ ለምሳሌ ከሁሉም በላይ የእስላሞችን ጉዳይ እንውሰድ፡፡ ከሁለት ዓመት በላይ በሽህዎች የሚቆጠሩ ብቻ ሳይሆን፤ በመቶ ሽህዎች የሚቆጠሩ ብቻ ሳይሆን፤ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ የሙስሊም ማሕበረሰብ አባላት በአብዛኛው ኢትዮጵያ ሲንቀሳቀሱ፤ በሰላማዊ መንገድ በአዲስ አበባ ውስጥም ሆነ ውጭ (መብታቸውን) ሲጠይቁ፤ አቤት ሲሉ፤ ፍርድ ቤት ሔደው ሲጠይቁ፤ የሚመለከታቸውን የመንግስት አካላት ሲጠይቁ ሽብርተኝነትን ጎረቤታችን ኬኒያ እንደምናየው፤ ሶማሊያ እንደምናየው፤ በመካከለኛው ምስራቅ እየተደረገ ያለው ሽብርተኝነት በምናቅበት ደረጃ ሲንቀሳቀሱ አናይም፡፡ በሠላማዊ መንገድ መብታቸውን ከመጠየቅ ውጭ፡፡ የጠየቁት መብት ደግሞ በጣም ቀላል ነው፤ ‹‹መንግስት በኃይማኖታችን ውስጥ ጣልቃ አይግባ››፤ ‹‹መንግስት የፈለገውን የኃይማኖት አንዱን ክፍል ይዞ ሌላኛው በጉልበት እንዲንቀሳቀስ››፤ ‹‹መሪዎቻችን ቀበሌ ውሰጥ አንምረጥ፤ ቀበሌ ለምሳሌ የመንግስት ተቋም ነው›› … ስለዚህ የእስላም መሪዎች ቀበሌ ውስጥ የሚመረጡበት ምክንያት በሕጉም በምኑም መንገድ አላውቅም እኔ፡፡ ክርስቲያን ወንድሞቻችን መሪዎቻቸውን ቤተክርስቲያን እንደሚመርጡ እነዚህ ወንድሞቻችንም መስጊዶቻቸው ውስጥ መሪዎቻቸውን ከመረጡ ኃይማኖቱ የግላቸው ነው የራሳቸው ነው፡፡ መንግስት ግን እዛ ውስጥ ጣልቃ ገብቶ፤ ‹‹ቀበሌ ካልመረጣችሁ›› በማለት በቀጥታም ሆነ በእጅ አዙር ሲንቀሳቀስ እኮ እናውቃለን፡፡ በዚህ በኢትዮጵያ ሕዝብ ውስጥ እኮ ነው የምንኖረው፡፡ እናም ማን የት ጣልቃ እንደገባ ኃይማኖቶች መንግስትን ያስቸገሩበት ሁኔታ ሳይሆን፤ መንግስት እንዲያውም በራሱ ሔዶ … የእኔ ስጋትና በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የሰጠሁትም ምክር ሕዝብ ያላሰበውን እንዳያሳስብ ነው፡፡ቪኦኤ፡ ዶ/ር መረራ በሰሞኑ ጉዳዮች ላይ እናተኩርና በተደጋጋሚም ከዚህ በፊትም እንደሚታወቀው፤ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ በፓርላማ ቀርበው፤ እንዲሁም የፀጥታና የደህንነት ኃይሎችም በተለያዩ ቃለመጠይቆች የሽብር ስጋት እንዳለና ከተቃዋሚዎች ጋር እያያዙ በተናገሩ ጊዜ፤ እንደምናስታውሰው ከሁለት ዓመት በፊት ጋዜጠኞች እስክንድር ነጋ፤ ርዕዮት ዓለሙ፤ ውብሸት ታዬ ከተቃዋሚዎች ደግሞ እነ አንዷለም አራጌ ታስረዋል፡፡ እና አሁን ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ በፓርላማ እየቀረቡ እንዲሁም ደግሞ የፀጥታ ኃይሎች የሚሰጡአቸውን መግለጫዎች ስትመለከቱ፤ እንዲያው እርስዎ እንደመሪነቶ፤ እንዲሁም ደግሞ እርሶ በሚመሩት ፓርቲና በሚሰሩባቸው መድረኮች ሰሞኑን ስጋት የፈጠረበት ሁኔታ አለ?ዶ/ር መረራ፡ በእኛ በኩል የኢትዮጵያ መንግስት ለአለፉት ዓመታት ይሄኑ ሲል ነበር አሁንም ያንኑ እያለ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ በሚያውቀው ደረጃ የዓለምአቀፍ ማሕበረሰብም በሚያውቀው ደረጃ አባሎቻችን ሰላማዊና ሕጋዊውን ትግል ከመግፋት ውጭ በሕገወጥ መንገድ በሴራ ውስጥ የተሳተፉበትና የሚሳተፉበት ምክንያት የለም፡፡ እኛ ሕጋዊና ሰላማዊ ትግላችንን እንቀጥላለን፡፡ የኢትዮጵያ መንግስትም እስከአሁንም እንደሚያደርገው አሁንም በብዛት አባሎቻችንን እንደ በቀለ ገርባ፣ ኦልባና ሌሊሳ፣ እነ አስፋው አንጋሱ፣ እነ ጉቱ ሙሊሳ የሚባሉ በመቶዎች የሚቆጠሩ አባሎቻችን እኮ እስር ቤት አሉ፤ ‹‹ከሕግ ውጭ መንግስትን ለመገልበጥ አሲራችኋል›› ተብለው፡፡ እኛ ሕጋዊና ሰላማዊ ትግላችንን ከመግፋትና ከማካሄድ ውጭ ምርጫ የለንም፡፡ የኢትዮጵያ መንግስት ማድረግ የነበረበት ከኢትዮጵያ ሕጋዊ ተቃዋሚዎች ጋር የመደራደር ሁኔታ ብሔራዊ የመግባባት ሁኔታን የመፍጠር ሂደትን በሰላማዊ መንገድ ሁሉም የአገሪቱ የፖለቲካ ኃይሎች የሚንቀሳቀሱበት ሁኔታ የመፍጠሩ፤ የማመቻቸቱ፤ ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ ሊያካሂድ የሚችል ምርጫ ቦርድ የመፍጠሩ ነፃ ሚዲያ በአገሪቱ ውስጥ እንዲፈጠር የማድረጉ፤ የሕግ የበላይነት በዚህ አገር እንዲከበር፤ ሁሉም ዜጎች በዚህ ውስጥ እንዲሳተፉ የማድረግ ሁኔታ ይጠበቅበታል፡፡ ያንን ከማድረግ ይልቅ ‹‹በግድ መግዛት አለብኝ››፤ ‹‹ከህግ ውጭ መንቀሳቀስ አለብኝ››፤ ‹‹ሠላማዊ ትግል የሚያካሂዱትን ጉልበት ስላለኝ ለማፈን እንቀሳቀሳለሁ›› … ካለ እኛም ትግላችንን ከመቀጠል ውጭ ሌላ አማራጭ የለንም፤ የኢትዮጵያ መንግስት ግን ደጋግሞ ማሰብ ያለበት ደጋግሞ ይሄን በገፋበት መንገድ ዘላቂ ሰላም ሊያመጣ የሚችል አይመስለኝም፡፡ እንዲያውም ወጣቱን ወዳላሰበው አቅጣጫና መንገድ እንዳይገፋ እኔ ስጋት አለኝ፡፡ የኢትዮጵያ መንግስትን ደጋግሜ የምመክረው ሕጋዊና ሰላማዊ ትግሉን ከሽብርተኝነት ጋር አያይዞ፤ ዓለምም እያወቀ፤ የኢትዮጵያ ሕዝቦችም እያወቁ እያደባለቀ መጠቀም መሞከሩ ማንንም አይጠቅምም፡፡ ማስፈራራቱም ማንንም አይጠቅምም፡፡ አባሎቻችንን ከዚህ በፊትም ሲያድን ነበር ያንን መቀጠሉ፤ የፖለቲካ ምህዳሩን የበለጠ ለመዝጋት (አሁንም ተዘግቷል) እስከሄደ ድረስ እኛ ምርጫ የለንም ለማለት ነው፡፡ ሕጋዊና ሰላማዊ ትግልን እስከመጨረሻው ከመቀጠል ውጭ፡፡ቪኦኤ፡ የኦሮሞ ፌደራሊስ ኮንግረስ ፓርቲ መሪ ዶ/ር መረራ ጉዲና ለሰጡኝ ማብራሪያ አመሰግናሁ፡፡ዶ/ር መረራ፡ እኔም ለተሰጠኝ እድል አመሰግናለሁ፡፡

እንግዲህ ዶ/ር መረራ ተናገረ ተብሎ በተከሰሰበት ጥቅምት 21፣ 2006ም ሆነ በጥቅምት 22 ቃለ-መጠይቅ ላይ ተናግሯል የተባለውን ‹‹አሸባሪዎቹ አፈነዱ የተባለው የውሸትና የመንግስት ድራማ ነው›› የተባለ ‹ሐሰተኛ› ወሬ አንድም ቦታ አናገኝውም፡፡ ነገር ግን የዚህ ክስ ይዘት ከሐሰተኛነቱ ይልቅ ሦስት ጉዳዮችን መዝዞ ይነግረናል፡፡

የመጀመሪያው ዶ/ር መረራ ጥቅምት 15፣ 2006 የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ጋዜጠኛ የአጥፍቶ መጥፋቱን ዜና አስመልክቶ ላቀረበለት ጥያቄ “ሰው አንዳንድ ጊዜ የኢትዮጵያ መንግስት ለራሱ ፖለቲካ ብሎ የሚያደርገው ያው የለመደው ሥራ ነው ይላል›› በማለት የሰጠው መልስ በክሱ ለማመልከት የተሞከረ ይመስላል፡፡ ነገር ግን የመረራ ከሳሽ በመንግስታዊው ቴሌቪዥን ‹‹የሐሰተኛ ወሬ›› ተሰራጨ ብሎ መንግስትን ራሱን መክሰስ ሲያሳፍረው፤ ይቀራረባል በሚል ሐሳብ ከአሜሪካ ድምፅ ቃለ-መጠይቅ ላይ ወስዶ ክስ ለማቅረብ የሞከረበት ርቀት አስገራሚ ነው፡፡

ሁለተኛው ምልከታ ደግሞ ወደ ክሱ ጥንስስ ይወስደናል፡፡ ዶ/ር መረራ ጉዲና የተከሰሱበትን የአሜሪካ ድምፅ ቃለ-መጠይቅ ከሰጡ ከአስር ቀናት በኋላ መንግስታዊው አዲስ ዘመን ጋዜጣ በሕዳር 2006 ‹ኢብሳ ነመራ› በተባሉ ፀኃፊ አማካኝነት በአጀንዳ አምዱ በተከታታይ “የአይነኬዎቹ ፍርሃት የጨመደደው ጋዜጠኛና ፖለቲከኛ” እና “መሠረት አልቦ አቋም” የሚሉ ሁለት ጽሑፎችን ያተመ ሲሆን፤ የጽሑፎቹ ዓላማም ዶ/ር መረራ የሰጡትን ቃለ-መጠይቅ ቃል በቃል እየነቀሰ መውቀስ፣ ማጣጣልና በመጨረሻ ‹ሕጋዊ ተጠያቂነት› እንዲኖር ጥሪ ማቅረብ ነበር፡፡ እንግዲህ የመንግስታዊው ጋዜጣ የእስር ጥሪ ዘግይቶም ቢሆን ከሦስት ዓመታት በኋላ መረራን ለእስር አብቅቶታል፡፡

ሦስተኛውና ብዙ ሰዎች ለክሱ ምክንያት በሆነው ጉዳይ ላይ ተመሳሳይ አቋም ይዘው እያለ መረራ ላይ ብቻ ይህ ክስ እንዲቀርብ የሆነበት ምክንያት አስገራሚነት ነው፡፡ ‹‹የኢትዮጵያ መንግስት የደኅንነት መስሪያ ቤት በዜጎቹ ላይ ጉዳት በማድረስ ተቃዋሚዎችን የችግሩ አድራሽ አድርጎ እንዲወቀሱ ያደርጋል›› የሚለው ወቀሳ ለረጅም ጊዜያት የቆየ ቢሆንም ይህ ወቀሳ በጠነከረ መልኩ ከማስረጃ ጋር መቅረብ የጀመረው የምስጢራዊ መረጃ አጋላጩ ዊኪሊክስ በጥቅምት 1999 በወቅቱ የአሜሪካ መንግስት ‘ሻርሼ ዴ ፌር (chargé d’affaires) ቪኪ ሐድልስተን ለአሜሪካ መንግስት የሥለላ ማዕከል (ሲ.አይ.ኤ)ና ሌሎች የአሜሪካን የደኅንነትና የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤቶች የላኩትንመልዕክት ይፋ ካደረገ በኋላ ነው፡፡ ቪኪ በመልዕክታቸው መስከረም 06፣ 1999 በአዲስ አበባ ከተማ ካራ ቆሬ አካባቢ በሦስት የተለያዩ ቦታዎች የቦምብ ፍንዳታዎች መከሰታቸውንና የኢትዮጵያ መንግስትም የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ) አባላት ቦንቦችን ለጥፋት ሲያዘጋጇቸው ራሳቸው ላይ ፈንድተውባቸው ሁለት ግለሰቦች ወዲያውኑ ሲሞቱ ሦስተኛው ግለሰብ ደግሞ ወደሆስፒታል በመሄድ ላይ እንዳለ ሕይወቱ እንዳለፈ የመንግስትን መረጃ ጠቅሰው ፤ የአሜሪካ መንግስት  ባደረገው ማጣራትም ከፍንዳታዎቹ ጀርባ የመንግስት እጅ እንዳለበት ገልፀዋል፡፡ አክለውም ሞቱ ተብለው በመንግስት የተጠቀሱት ግለሰቦች ከሳምንት በፊት በፖሊስ ተወስደው በደረሰባቸው ድብደባ ምክንያት በመሞታቸው መንግሥት በራሳቸው ጥፋት እንደሞቱ ለማስመሰል ቦንቦቹን እንዳፈነዳቸው ዶ/ር መረራ ጉዲና ያላቸውን መረጃ ለኤምባሲው እንዳካፈሉ አትተዋል፡፡ ኤምባሲው በራሱ ምርመራ አድርጎም ቦንቦቹ ከተጠቀሱት ቤቶች ውጭ በሦስተኛ አካል ተዘጋጅተው እንደፈነዱ ለማረጋገጥ መቻሉን ጠቅሰው ቪኪ ሐተታቸውን ይጨርሳሉ፡፡

የሁለቱም የፍንዳታ ሁነቶች መመሳሰል አስገራሚ ሲሆን፤ የመረራ ከሣሽ ‹‹መረራ በጥቅምት 1999 የተደረገውን ሴራዬን አጋለጡብኝ›› በሚል በቀል አዘል መንፈስ አስር ዓመታት ጠብቆ በሕዳር 2009 ከሦስት ዓመታት በፊት የሰጡትን አስተያየት እንደወንጀል ቆጥሮ አስሯቸዋል፡፡ ይህ ድርጊትም የመረራ ከሣሽ እርሳቸውን ለመበቀል የሄደበት ርቀት አስገራሚነት ከመናገሩ ባለፈ ለመረራ ግን የመንፈስ ‘ረፍት ነው፡፡ መረራን ለመበቀል አስር ዓመታትን ሲቆጥር የነበረ ሥርዓት የራሱን ሴራ ለመሸፈን ሲጥር የበለጠ ራሱን ማጋለጡ ደግሞ ለታሳሪው መረራ ድል ነው፡፡ አሁን የመረራን ጉዳይ የያዘው ፍርድ ቤት ውሳኔ ለመስጠት ቀጠሮ ይዟል፡፡ ለዳኞቹ ንጹሁን መረራን ‹ነፃ› ከመልቀቅ የቀለለ ነገርስ ይኖር ይሆን?

Filed in: Amharic