>

ሻእቢያና ታዝሎ የኖረበት አንቀልባ!??! (ያሬድ ጥበቡ)

“ሻዕብያ ጊዜያዊ መንግሥት እንደመሠረተ የገንዘብ ስጦታ እንዳደረግለት ይጠይቃል፡፡ የአቶ መለስ ቡደን በመጀመሪ የ200 ሚሊዮን ብር፣ቀጥሎ የ100 ሚሊዮን ብር ስጦታ ሲያደርግ በኢሕአዴግ ሥራ አስፈጻሚ ውስጥ ጥያቄ ይነሳል፡፡ “ካስፈለገ ብድር ይውሰድ እንጂ እንዴት የሕዝብ ገንዘብ በምስጢር እንሰጣለን” የሚል ተቃውሞ ነበር የተነሳው፡፡ “የትምክህተኞን አሉባልታ እየሰማችሁ ነው ዝም በሉ፤ ኤርትራ የደም ካሳ ብትጠይቅ ብዙ ለመክፈል እንገደድ ነበር” ሲል የአቶ መለስ ቡድን በውሳኔው ጸና፡፡ በወደብ አገልግሎትና በዘይት ማጣሪያው እንዲሁም በአስመራ የተለያዩ ተቋማት ተቀጥረው የሚያገለግሉ ኢትዮጵያውያን ሲባረሩም፣ “ይህ ተገቢ አይደለም” በሚል ጥያቄ ላነሱም የአመራሩ አባላት የአቶ መለስ ቡድን “በጭቆናና ስለላ የተሳተፉ የደርጉ ቢሮክራሲ አባላት ናቸው” የሚል መልስ በመስጠት ዜጎቹን የመከላከል ኀላፊነት ለመወጣት ሳይችል ቀርቷል፡፡
 በ1985 እና 1986 ዓመታት የኢትዮጵያ ብሔዊ ባንክና ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር በኤርትራ ላይ የገንዘብ ጥያቄ አነሱ፡፡ ጉዳዩ በኤርትራ ባንኮች ውስጥ ቀልጦ የቀረውን የኢትዮጵያውያን ገንዘብ አካውንት የተመለከተና በኤርትራ ያሉ ፋብሪካዎች በደርግ ዘመን የተበደሩትን ብድር እንዲከፍሉ የሚጠይቅ ነበር፡፡ የነዚህን የኢትዮጵያ ተቋማት ጥያቄ ላነሱ የአመራር አባላት የተሰጣቸው መልስ “በዚህ በኤርትራ ጉዳይ ላይ የማይሆኑ ነገሮች እየጎረጎራችሁ የትምክህተኞች መሣሪያ እየሆናቸሁ ነው፤ ተጠንቀቁ!” የሚል ነበር፡፡ ኤርትራን በተመለከተ ሌሎች ጥቃቅን ጉዳዮችም እየተነሱ ልዩነት የፈጠሩ ሲሆን በሁሉ ጉዳዮች ላይ የሻዕብያን ፍላጎት በማስተናገድ ጥያቄ የሚያነሱትን በትምክህተኝነት ክስ በማስፈራራት ለሰባት ዓመታት ለቀጠለው የወያኔ ኢሕአዴግ ውድቅ ፖሊሲ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስና ቡድናቸው ተጠያቂ ነው፡፡”
“ወጥቼ አልወጣሁም” – ገጽ 101-102
Filed in: Amharic