>

የ ኧርኔስቶ ‹‹ቼ›› ጉቬራ (Ernesto "Che" Guevara) 90ኛ ዓመት የልደት መታሰቢያ (ልኡል አምደጽዮን ሰርጸድንግል)

 የ ኧርኔስቶ ‹‹ቼ›› ጉቬራ (Ernesto “Che” Guevara) 90ኛ ዓመት የልደት መታሰቢያ (ልኡል አምደጽዮን ሰርጸድንግል)

አርጀንቲናዊው የማርክሲስት አብዮተኛ፣ ሐኪም፣ ደራሲ፣ መምህር፣ ዲፕሎማት፣ የወታደራዊ ሳይንስ ባለሙያና የጦር መሪ … ኧርኔስቶ ‹‹ቼ›› ጉቬራ (ቼ ጌቫራ – Spanish) የተወለደው ከዛሬ 90 ዓመታት በፊት (ሰኔ 7 ቀን 1920 ዓ.ም) ነበር፡፡
ዝነኛው የእግር ኳስ ተጨዋች ሊዮኔል ሜሲ በተወለደባት ሮዛሪዮ ከተማ ውስጥ የግራ ዘመም ፖለቲካ አቀንቃኝ ከሆኑ ቤተሰቦች የተወለደው የተወለደው ቼ፣ በበርካታ የነፃነትና የእኩልነት ተጋድሎ ታሪኮች ውስጥ እንደምሳሌና ጀግና የሚቆጠር ሰው ነው፡፡
የ1960ዎቹ ኢትዮጵያውያን አብዮተኞችም ‹‹ፋኖ ተሰማራ ፋኖ ተሰማራ እንደ ሆቺ ሚንህ እንደ ቼ ጉቬራ›› እያሉ ስሙን ዘምረውበታል፡፡
በወጣትነት እድሜው የደቡብ አሜሪካ አገራትን ተዘዋውሮ የተመለከተው ‹‹ቼ››፣ በየሀገራቱ የነበረው ድህነትና ኢ-ፍትሃዊነት የላቲን አሜሪካ ሕዝብ ከተጫነበት የጭቆና ቀንበር እንዲወጣ የበኩሉን አስተዋፅኦ ማበርከት እንዳለበት አስገደደው፡፡
ዝነኛው አብዮተኛ ‹‹ቼ›› አስቦም አልቀረ፡፡ በጓቴማላ፣ በኩባ፣ በሜክሲኮ፣ በቦሊቪያ … እየተዘዋወረ ከነፃነት ታጋዮች ጎን ተሰልፎ አምባገነኖችን ተፋልሟል፡፡  ከአሜሪካ ምድርም ወጥቶ ወደ አፍሪካ ተሻገረና ከአልጀሪያና ከኮንጎ የነፃነት ተዋጊዎች ጋር ተገናኝቶ እርዳታ እንዳደረገ ታሪኩ ያስረዳል፡፡
አብዮተኛው ቼ በህዳር 1959 ዓ.ም የቦሊቪያ ዋና ከተማ ላ ፓዝ ሲደርስ፣ የአምባገነኑ ሬኔ ባሬንቶስ ሐገር የመጨረሻ መዳረሻዬ ትሆናለች ብሎ አላሰበም ነበር፡፡ በማርክሲስታዊ ርዕዮተ ዓለም ተከታይነቱና በአብዮተኛነቱ ምክንያት የማርክሲዝም-ሌኒኒዝም ርዕዮተ-ዓለምን ለማጥፋት ላይ ታች ስትል በነበረችው አሜሪካና፣ በድህነትና በጭቆና ቀንበር የሚማቅቀውን ሕዝብ ‹‹እያሳመፀብን ነው›› ብለው … እንኳን እርምጃው ስሙ ባስፈራቸው የደቡብ አሜሪካ አምባገነኖች በጥብቅ ሲፈለግ የነበረው ‹‹ቼ››፣ (መስከረም 28 ቀን 1960 ዓ.ም/October 8 1967 G.C) ፌሊክስ ሮድሪጌዝ በተባለ ኩባን ከድቶ ለአሜሪካው ማዕከላዊ የስለላ ተቋም (CIA) ሲሰራ በነበረና፣ ክሎስ ባርቢ በተባለ የናዚ የጦር ወንጀለኛ ምክርና ጥቆማ ‹‹ቼ›› በቦሊቪያ ወታደሮች ቆስሎ ተማረከ፡፡
‹‹ …1800 የሬኔ ባሬንቶስ ወታደሮች ጥቂት ቁጥር ያላቸውን ተዋጊዎች ከበው የተኩስ ናዳ ሲያዘንቡባቸው ‹‹ቼ›› ቆስሎ ስለነበር፣ ከመማረክ ውጭ አማራጭ አልነበረውም›› ሲል የአብዮተኛውን የሕይወት ታሪክ የፃፈው ሊ አንደርሰን ጽፏል፡፡
በተያዘበት እለትም ተዋጊ ጓዶቹ የት እንዳሉ ሲጠየቅ ትንፍሽ ሳይል ቀረ፡፡ ቦሊቪያንና ሕዝቧን እንዳሻው ሲያሽከረክራቸው የነበረው ፕሬዝደንቱ ሬኔ ባሬንቶስ፣ ጀግናው አብዮተኛ ከታሰረበት ሊያመልጥ ይችላል ብሎ በመስጋቱ ‹‹ተዋጊ ጓዶቹ የት እንዳሉ እንደገና ይጠየቅ›› ብላ ስትጮህ የነበረችውን አሜሪካን እንኳ አልማሰማም ብሎ በቶሎ እንዲገደል ትዕዛዝ አስተላለፈ፡፡ ቀደም ሲል ጓደኞቹ በ‹‹ቼ›› ተዋጊዎች የተገደሉበት ማሪዮ ቴራን የተባለ የ27 ዓመት የመጠጥ ሱሰኛና የአምባገነኑ ሬኔ ባሬንቶስ ወታደር ‹‹ቼ›› ን ለመግደል ጥያቄ አቅርቦ ስለነበር ተፈቀደለት፡፡
ሱሰኛው ማሪዮ ቴራን ‹‹ቼ››ን ሊገድለው ወደእርሱ ሲጠጋ ‹‹… ልትገድለኝ እንደመጣህ አውቃለሁ፤ ተኩስ! ፈሪ! አንተ መስራት የምትችለው ሰው መግደል ብቻ ነው …›› ብሎ ሲሞት እንኳ እንደማይፈራ ነግሮታል፡፡ ገዳዩ ቴራንም ዝነኛው አብዮተኛ ላይ ዘጠኝ ጊዜ አከታትሎ ተኮሰበት! አምስት ጥይቶች እግሮቹ ላይ፣ ቀኝ ትከሻው፣ ክንዱ፣ ደረቱና ጉሮሮው ላይ ደግሞ አንድ አንድ ጥይቶች አርከፈከፈበት፡፡ የዝነኛው አብዮተኛ ሕይዎትም አ ለ ፈ!
የአብዮተኛው ኧርኔስቶ ‹‹ቼ›› ጉቬራ  የረጅም ጊዜ ወዳጅና የትግል ጓድ የነበሩት የኩባው መሪ ፊደል አሌሃንድሮ ካስትሮ ሩዝ (ፊደል ካስትሮ)፣ እ.አ.አ በ1997 በሳንታ ክላራ ከተማ ለወዳጃቸው የመታሰቢያ ሃውልት እንዲቆምላቸው አድርገዋል፡፡
እ.አ.አ ከ1957 እስከ 1968 ለአሜሪካው ማዕከላዊ የስለላ ተቋም (CIA) ሲሰራ የነበረና በኋላ ደግሞ ከድቶ ኩባ የቀረ አንድ የስለላ ሰው ‹‹በወቅቱ ሲ.አይ.ኤን በዓለም ላይ እንደ ‹‹ቼ›› ጉቬራ የሚያስፈራውና የሚያስጨንቀው ሰው አልነበረም፤ ምክንያቱም ሰውየው ማንኛውንም ዓይነት ትግል ለመምራትና በድል ለማጠናቀቅ ያለው ችሎታ ብቻ ሳይሆን ግርማ ሞገሱም ጭምር ያስፈራ ነበር›› በማለት አሜሪካ ‹‹ቼ››ን ምን ያህል ትፈራው እንደነበር ምስክርነቱን ሰጥቷል፡፡
Feliz Cumpleaños Che Guevara! 
Filed in: Amharic