>

እቴጌ ጣይቱ ብጡል በአጭር የህይወት ዘመን የረዥም ታሪክ ባለቤት!!! (በዳንኤል ወ/ኪዳን)

እቴጌ ጣይቱ ብጡል በአጭር የህይወት ዘመን የረዥም ታሪክ ባለቤት!!!
ፀሐፊ ዳንኤል ወ/ኪዳን
* ጣይቱ ብጡል ማን ናቸው?
«ብርሃን ዘ ኢትዮጵያ» በሚል ቅፅል ስም የሚታወቁት እቴጌ ጣይቱ ከአባታቸው ደጃዝማች ብጡል ኃይለ ማርያም እና ከእናታቸው ወይዘሮ የውብዳር በነሐሴ12ቀን1832 ዓ.ም በጌምድር ውስጥ ደብረታቦር ከተማ ተወለዱ። በየኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ስርዓት መሠረት በተወለዱ በ 80 ቀናቸው ጥቅምት 23 ቀን1833 ዓ.ም በደብረ ታቦር እየሱስ ቤተክርስቲያን ክርስትና ተነሱ። በልጅነት ዘመናቸው በዚሁ ደብር ውስጥ ዳዊት ደገሙ። ከዚያም በጊዜው ይሰጡ የነበሩትን ሌሎች የሃይማኖት ትምህርቶች በየታላላቅ አድባራት በመዘዋወር ያጠናቀቁ ስለመሆናቸው ታሪክ አዋቂዎች ይናገራሉ።
የተማሩባቸውም መጻሕፍት የተጻፉት በግዕዝ ቋንቋ ስለነበር ቋንቋውን አጣርተው ያውቁ ነበር። እናታቸው ወይዘሮ የውብዳር ባለቤታቸው ደጃዝማች ብጡል ኃይለ ማርያም ከሞቱ በኋላ በጅሮንድ መዩ የተባሉትን የአፄ ቴዎድሮስ ባለሟልን አግብተው ነበር። እርሳቸውም ጣይቱ ብጡል ትምህርት እንዲቀስሙ ለማድረግ ልዩ መምህር ቀጥረውላቸዋል። እቴጌ ጣይቱ በማኅደረ ማርያም ሆነው ይማሩና መፃሕፍትን ይቀጽሉ በነበሩበት ጊዜ ለቤተክርስቲያን መጋረጃ መሥሪያ በትርፍ ጊዜያቸው ፈትል እየፈተሉ ያቀርቡ ነበር። በበገና ቅኝትና ድርደራም በኩል የታወቁ ባለሙያ እንደነበሩ ይነገርላቸዋል።
 
* የጣይቱና የምኒልክ ጋብቻ
የሸዋው ንጉሥ ምኒልክ በሸዋ የአፄ ቴዎድሮስ እንደራሴ ከነበሩት አቶ በዛብህ ጋር ነሐሴ 17 ቀን 1857 ዓ.ም በጋዲሎ አካባቢ በተደረገው ጦርነት ድል አድርገው ወደ አንኮበር ገቡ። በነሐሴ 24 ቀን ነገሡ። በነገሡም በአሥራ ሁለት ዓመታቸው የፋሲካን በዓል በባሕር ዳር አቅራቢያ ሱሉልታ ላይ ዋሉና ደብረ መይ በጣይቱ ብጡል እናት በወይዘሮ የውብዳር ቤት ከጣይቱ ጋር ተጫጭተው ስለጋብቻቸው ተነጋገሩ። ከዚያም ዋና ከተማቸው ወደነበረችው ደብረ ብርሃን ተመለሱ።
ከተጫጩ ከሁለት ዓመት በኋላ ወይዘሮ ጣይቱን ለማስመጣት በቤተ መንግሥቱ በተደረገው ምክር መሠረት አለቃ ተክለማርያም ወልደ ሚካኤል ደብዳቤ ተሰጥቷቸው ተላኩ። በዚያም አስፈላጊው ሁሉ በተፋጠነ ሁኔታ ተሟልቶ በጐጃም በኩል ደንገጡሮችና አሽከሮች አስከትለው ጉዞውን ጀመሩ። ደብረ ብርሃንም በገቡ ጊዜ ንጉሡ ምኒልክ ታላቅ አቀባበል አደረጉላቸው። ከዚያም ጣይቱ ወንድማቸው ራስ ወሌ ብጡል ዘንድ ለጥቂት ዓመታት ተቀምጠው ከቆዩ በኋላ የጋብቻቸው ሥነ-ሥርዓት የፋሲካ ዕለት ሚያዝያ 25 ቀን1875 ዓ.ም በአንኮበር መድኃኔ ዓለም ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ቁርባን ተቀብለው ተጋቡ።
አፈወርቅ ገብረ ጊዮርጊስ «ዳግማዊ አጤ ምኒልክ» በተባለው መጽሐፋቸው ከገጽ39 እስከ 41ላይ «ከልጅነት ጀምረው ሲመኟት እንደ ህልም ሲአልሟት ትኖር የነብረችው ጣይቱ ብጡል በ18 75ዓ.ም ደብረ ብርሃን ገባች። ንግሥተ ሸዋ ሆነች ወዲያው የፋሲካ ዕለት አንኮበር መድኃኔዓለም ቆርበው ተጋቡ። … ፀሐይቱ ለማለት ጣይቱ ተባለች ነገር ግን ከጣይቱ እጣይቱ ለመባል ይገባታል» ይላሉ።
«ብርሃን ዘ ኢትዮጵያ»
ንጉሡ «አፄ ምኒልክ ንጉሠ ነገሥት ዘኢትዮጵያ» የሚለውን ስም በተቀዳጁ በማግሥቱ ጥቅምት 27 ቀን 1882ዓ.ም ወይዘሮ ጣይቱ ብጡል እቴጌ ተብለው ተሰየሙ። የሥርዓተ ዘውዱ አፈፃፀም በከፍተኛ መሰናዶ የተጠናቀቀ በመሆኑ እጅግ ደማቅ እንደነበር ከተፃፉ ጽሑፎች ለማወቅ ይቻላል። እቴጌ ጣይቱም ጳጳሱ አቡነ ማቴዎስ ከንጉሠ ነገሥቱ እጅ የተቀበሉትን ዘውድ ደፉላቸው። ከዚያን ጊዜ ጀምሮ በታወቁበት «እቴጌ ጣይቱ ብርሃን ዘ ኢትዮጵያ» በሚል የክብር ስም ማኅተም ተቀረፀላቸው። እነዚሁ ታሪካዊ ሂደቶች እቴጌዪቱን በኢትዮጵያ ዱኛዊ፣ ወታደራዊና ማኅበራዊ ኑሮ ውስጥ ከፍተኛና ብሩህ ሚና ለመጫወት የቻሉ አድርጓቸዋል።
ፖለቲካዊ ተግባራት
እቴጌ ጣይቱ በዱኛ አስተዳደር አንፃር የነበራቸው ችሎታና ተግባራዊ እንቅስቃሴ በታሪክ አዋቂዎች ዘንድ ተደናቂነትን አትርፎላቸዋል። በየጊዜው ይነሱ በነበሩ የሀገር ጉዳዮች ላይ ይይዙት የነበረው አቋም፣ ይሰጡት የነበረው ውሳኔና ያስተላልፉ የነበረው ትዕዛዝ ተሰሚነትና ተቀባይነት እያገኘ እንደመሄዱ መጠን ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ ይሄድ ለነበረው የዱኛ ሥልጣናቸው ዓይነተኛ ምክንያት ነበር።
እቴጌ ጣይቱ በኢትዮጵያ ዱኛ ተሳትፏቸው የገነነውና በአገር አስተዳደርም ውስጥ ከፍተኛ ሚና መጫወት የጀመሩት፤ ኢትዮጵያ ሚያዝያ 25ቀን 1981ዓ.ም በውጫሌ ላይ ከኢጣሊያ ጋር በተፈራረመችው ውል ውስጥ በኢጣሊያንኛው ትርጉም ሀገሪቷን ነፃነት እንደሌላት ጥገኛ በማስመሰል ዓላማ ላይ የተመረኮዘ ውንብድና መኖሩ ከታወቀ ወዲህ ነው።
ይህ ለአድዋ ጦርነት መነሳት ምክንያትና ዋነኛ መንስዔ የሆነው ጉዳይ ሊታወቅ የቻለው እቴጌ ጣይቱ የውጫሌ ውል አንቀፅ 17ላይ አለቃ ዓፅመ ጊዮርጊስ የተባሉት ቋንቋ አዋቂ አፄ ምኒልክ በሰጧቸው ትዕዛዝ መሠረት ነው። ያኔ የውሉን ሰነድ በመመርመር የውሉ 17ኛ አንቀፅ የያዘውን የትርጉም መዛባት ያለበት መሆኑን አሳወቁ። ጉዳዩ ኢትዮጵያ የምትጐዳበት ስለመለሆኑ ጭምር በማስረዳት በሰጡት ቃል እቴጌ ጣይቱ በጥንቃቄ ተመለከቱት።
ጉዳዩን አፄ ምኒልክ በመጀመሪያ ሳይረዱ አለቃ ዓፅመ ጊዮርጊስ እንዲታሰሩ ቢያደርጉም እቴጌ ጣይቱ ግን እኚህ ሰው ትክክለኛ የኢትዮጵያ ወዳጅ መሆናቸውን ለአፄ ምኒልክ በማስረዳት ከሦስት ዓመታት እስራት በኋላ ማስፈታታቸው ይታወቃል። በዚህ በኩል ሲታይ እቴጌ ጣይቱ የምኒልክ የቅርብ አማካሪ በመሆን በፖለቲካ ተግባሮች ምን ያህል አስተዋፅኦ እንዳበረከቱ መገንዘብ ይቻላል። እቴጌ እንደተናገሩትም «ዓፅመ ጊዮርጊስ ቢታሰር ቢፈታም ለሀገሩ የሚገባውን ሠርቶ ነው። ኧረ ለመሆኑ ኢትዮጵያዊ ነኝ የሚለው ዮሴፍ፣ ኢጣሊያኖች በተንኮል ገብተው በማታለል ይህን የመሰለ ሥራ ሲሠሩ አነጋጋሪ ሆኖ ሳለ እንዴት ሳያስጠነቅቅዎ ቀረ?» በማለት የእቴጌ ጣይቱ የቁጣ መዓት ወደ ዮሴፍ ዞረ።
ከዚያም ጨምረው «ከእንግዲህ ወዲህ የኢትዮጵያን ጥቅም የሚነካ፣ ሥር የሚነቅል፣ መሠረት የሚያፈርስ ጉዳዩን ሁሉ እኔ ሳላየው እንዳያልፍ ይፍቀዱልኝ» ብለው ለንጉሡ ባመለከቱት መሠረት «አንቺ ሳታይው ሳትመረምሪው አያልፍም» በማለት ፈቀዱላቸው። ይህ ሁኔታ የሚያመለክተው እቴጌ ጣይቱ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ የነበራቸው ቦታ ምን ያህል ከፍተኛ እንደሆነ ነው። ውሉንም ለማስተካከል አፄ ምኒልክ ያደረጉት የዲፕሎማሲ ጥረት ውጤታማ ሊሆን ባለመቻሉ ሚኒስትሮች የጦር አለቆችና መኳንንት የሚገኙበት ጉባዔ እንዲጠራ አደረጉ።
እያንዳንዱ ሰው ስለተነሳው ችግር ያለውን አስተያየት የሀገር ፍቅር በተሞላበት አንደበትና የጋለ መንፈስ ሲገለፅ ቆየ። እቴጌ ጣይቱም «እኔ ሴት ነኝ ጦርነት አልወድም። ሆኖም ይህን ኢትዮጵያን የኢጣሊያ ጥገኛ የሚያድርግ ውል ከመቀበል ጦርነትን እመርጣለሁ» የሚል አቋማቸው በታሪክ ቅርስነቱ ለትውልድ ትተውት ያለፉት አባባል ዘመን ተለውጦ ዘመን እየተተካ በሄደ ቁጥር የሚነገር ሆነ። ስለዚህ የእቴጌን ጀግንነት የቁርጠኛ ኢትዮጵያዊ ልጅ ለመሆናቸው ሌላ ማረጋገጫ ማቅረብ አያስፈልግም። እቴጌ ጣይቱ ወንድማቸው ራስ ወሌን አተኩረው በማየት በታወቀው ጀግና አንደበታቸው የተሰበሰበውን ሕዝብ ስሜት ለመቀስቀስ ድምፃቸውን እንዲያሰሙ ማድረጋቸው ይነገራል።
«መልኩ ከመልካችን የማይመሳሰል እግዚአብሔር በባህር ከልሎ የሰጠንን አገራችንን የሚቀማ ጠላት መጥቶ እንዴት ዝም እንላለን? እንዋጋለን እንጂ!» በማለት የሀገሪቱን ውበትና ልምላሜ የምታፈራውን እህልና የከብት ዓይነት እየጠቃቀሱ በማንሳት ተናገሩ። ቀጥለውም «ኧረ ለመሆኑ ተራራው ሸለቆው ወንዛወዙ ጨፌው ሜዳው ማነው ቢሉት የማነው ብሎ ሊመልስ ነው እንገጥመዋለን እንጂ!» በማለትም የተሰበሰበውን ሕዝብ ልብ የሚነካና ወኔ የሚቀሰቅስ ንግግር አደረጉ። በዚህ የተዋጣ የቅስቀሳ ችሎታቸውም ባገኙት መድረክና አጋጣሚ የሚጠቀሙ አንደበተ ርቱዕ መሆናቸው ይነገራል።
ስለ እቴጌ ጣይቱ ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ በምሳሌነት ሊቀርብ የሚችል ሌላ ዓይነተኛ ታሪክ አለ። ይኸውም አፄ ዮሐንስ በሞቱ በአንድ ዓመታቸው በመጋቢት 1882 ዓ.ም አፄ ምኒልክ አገሩን ለማረጋጋት ሲሉ መሃል ትግራይን ለመጐብኘት ሄዱ። ይህ የሆነው እቴጌ ጣይቱ ለሸዋም፣ ለወሎም፣ ለበጌምድርም፣ ለየጁም መካከል በሆነችው ደሴ ከተማ ሆነው አገሩን እንዲጠብቁ በማለት ነው። እዚያ ሆነው ያከናወኑት ተግባር የረጋ አስተዋይና የተዋጣላቸው ዲፕሎማት አሰኝቷቸዋል። በተለይም በሁለት የጦር አበጋዞች መሃል የሚፈጠር አለመግባባትን አግባብቶ በመፍታት በኩል ተወዳዳሪ አልነበራቸውም።
እቴጌ ጣይቱ ከሕዝቡ ጋር በነበራቸው ግንኙነት በተለይም ያሳዩት በነበረው ርህራሄና ልግስና በጣም የተወደዱና የተመሰገኑ አድርጓቸዋል። ግልፅ የሆነው የፖለቲካ አስተያየታቸውና ጽኑ የሆነው ተግባራዊ ውሳኔያቸው፣ ዘዴንና ሥልጣንን እንዲሁም ምክርን ኃይልን ምን ጊዜ በእንዴት ያለ መጠን መጠቀም እንዳለባቸው በትክክል የመገመት ችሎታቸው ሲታይ በዓለም ከታወቁት የፖለቲካ አርበኞች ውስጥ ሊወሳ የሚገባ ታሪካዊ ስፍራ እንዳላቸው አጠራጣሪ አይሆንም። መልካም ስማቸውን ለማትረፍ ካስቻላቸው ጉዳዮች ጽኑ በሆነ መንፈሳዊ ኑሯቸው አኳያ የሚታየው የልግስናና የቤተ ክርስቲያን ነፃ ተግባሮች አንዱና ዓይነተኛው ነው። ይህ ከሃይማኖት መሪዎች ጋር ልዩ ግንኙነት ለመመስረት ያስቻላቸው ከመሆኑም በላይ የፖለቲካ ሥልጣናቸውን ለማጠናከር ከፍተኛ አስተዋፅኦ እንዳደረገ ከሌሎች ታላላቅ የፖለቲካ ሰዎች ታሪካዊ አነሳስ ለመገንዘብ ይቻላል።
በዚህ በኩልም እቴጌ ጣይቱ ብጡል በማህበራዊ ህይወት ሲያደርጉ የነበሩት በጐ ተግባር በመንፈሳዊ ኑሯቸው በእምነቱ ተከታዮች ዘንድ ያላቸው ተቀባይነት እጅግ የጐላ ነበር። ከነዚህም ውስጥ ለየካ ቅዱስ ሚካኤል ሰላሳ ጋሻ መሬት፣ ለሐመረ ኖህ ኪዳነ ምሕረት አሥራ ስድስት ጋሻ መሬት የሰጡ መሆኑ ለአብነት ያህል የሚጠቀሱ ናቸው።
እቴጌ ጣይቱ ለኢትዮጵያ ፖለቲካዊ ወታደራዊና ኢኮኖሚያዊ ሁኔታዎች መረጋጋት የሚያረጋግጥ የሀገር ግንባታ ተግባሮች በማከናወን ረገድና የአዲስ አበባ ከተማ መቆርቆር በእቴጌ ጣይቱ ከተጠናቀቁት የግንባታ ተግባሮች አንዱ ነው። ስለ እቴጌ ጣይቱ ሲወሳ በአዲስ አበባ ፒያሳ አካባቢ የሚገኘው የከተማዋ የመጀመሪያው ሆቴል «ጣይቱ ሆቴል» አብሮ ይነሳል። ምንም እንኳን እቴጌ ጣይቱ የተቀረፀላቸው ሐውልትና ለትውልድ የሚተላለፍ ስማቸውን የሚያስጠራ ከአብራካቸው የወጣ ልጅ ባይኖራቸውም፤ የአፄ ምኒልክን ልጆች አክብሮታዊ ፍቅር ሳይለያቸው ቤተሰባዊ ፍቅርን እየተላበሱ እንደኖሩ ከተለያዩ መጻህፍት ለመረዳት ይቻላል።
የሥልጣን ፍጻሜ
እቴጌ ጣይቱ ከደንገ ጡራቸውና የእንጀራ ልጅ ልጃቸው ጋር ባላቸው ዳግማዊ አፄ ምኒልክ ከሞቱ በኋላ በልጅ እያሱና በደጃዝማች ተፈሪ መኮንን መካከል የሥልጣን ሽኩቻ ተፈጠረ። በጦሩ መካከልም መከፋፈል በመታየቱ አገራዊ ችግሩ የከፋ ሆነ። በልጅ እያሱ አስተዳደር ዘመንም እቴጌዪቱ ከቤተ መንግሥት ተወግደው በግዞት ላይ ለአንድ ዓመት ከመንፈቅ ከሃያ ሁለት ቀናት ተቀመጡ። ሆኖም ታማኝ አሽከሮቻቸውና መላው ሠራዊት የእቴጌነታቸውን ልዕልና አላጐደለባቸውም። መሳፍንቱ መኳንንቱና ወይዛዝርቱም ቢሆኑ ተገቢውን አክብሮት ሳይነፍጓቸው ዕለት በዕለት ይጠይቋቸው ነበር። አቤቶ እያሱም ቢሆኑ የተለያዩ ስጦታዎችን ይዘው በመሄድ ይጠይቋቸው ነበር። የጦር ሚኒስትሩ ፊታውራሪ ሀብተ ጊዮርጊስ ዲነግዴም የተለያዩ እጅ መንሻ ይዘው ይጠይቋቸው ነበር።
የልጅ እያሱ ሥልጣን ብዙም ሳይቆይ ከላይ በተገለጸው ‘የሥልጣን ክርክር’ ተሸንፈው መስከረም 17 ቀን 1909ዓ..ም የሚኒስትሮች ካቢኔ ወይዘሮ ዘውዲቱ ምኒልክ ንግሥተ ነገሥታት ተብለው መንግሥቱን በመምራት እንዲተኳቸው መደረጉ ለእቴጌ ጣይቱ ታላቅ ድል ሆነ። በመሆኑም የእቴጌም የእስራት ቀንበር ሦስት ወር ባልሞላ ጊዜ ሊወድቅላቸው ቻለ። ንግሥት ዘውዲቱ ሥልጣናቸው ተዳክሞ ትዕዛዛቸው እንዳይዛባ በማለት ከተጓዙበት ከእንጦጦ ሳይቀር ምክር መለገሳቸውን አላቋረጡም ነበር።
እቴጌ ጣይቱ የደረሰባቸውን ፈተና ሁሉ በትዕግስት ተቀብለው ጥቂት እፎይ ካሉ በኋላ ከአፄ ምኒልክ ጐን ሆነው የኢትዮጵያን አንድነትና ጥንካሬ ለማረጋገጥ ሲታገሉ ያለፉት ዘመን ከዕለታት አንድ ቀን ትዝ ስላላቸው ከሰገነት ላይ ብቅ ብለው «ያ ቤት የትኛው ነው?» ብለው ሲጠይቁ ከደንገጡሮቹ አንዷ «የእመቤቴ እልፍኝ ግምጃ ቤት ነበር» አለች። እሳቸውም ትንሽ ተከዝ ብለው ከቆዩ በኋላ ቀበል በማድረግ «ነበር ለካስ እንዲህ ቅርብ ኖሯል» አሉ ይባላል።
እቴጌ ጣይቱ ሰኞ የካቲት አራት ቀን 1910ዓ.ም በመንፈቀ ሌሊት ህመም ፀንቶባቸው ከሚወዱትና ከሚወዳቸው ሕዝብ በሞት ተለዩ። የዕረፍታቸውን ዜና የኀዘኑንም ሥነ ሥርዓት ለማወጅ የቤተ መንግሥቱ መድፍ ሃያ አምስት ጊዜ ድምፁን አሰማ። በኀዘኑ ሥርዓትም ላይ እቴጌ በአድዋ ጦር ሜዳ ላይ ያሳዩትን የቆራጥነትና የጀግንነት ሙያቸውን እየጠቀሱ በግጥም እየገለጡ በማሞገስ ይሸልሉ ይፎክሩና ያቅራሩ ነበር። የእቴጌም አስክሬን በወርቅ ሐረግ በተከበበ የእንጨት ሳጥን ተደርጐ በብረት ሳጥን ውስጥ ከገባ በኋላ በቀድሞ ቤተ ፀሎታቸው ውስጥ ሸራ ቤት እየተባለ ይጠራ በነበረው መንበረ ፀሐይ እንጦጦ ማርያም ቤት ውስጥ በታላቅ ክብር አረፉ። ለተሰበሰበው ሕዝብ ትልቅ ግብዣ ተደርጐ የቀብሩ ፍፃሜ ሆነ።
እቴጌ ጣይቱ ከማረፋቸው አስቀድመው ለንግሥት ዘውዲቱ «ልጄ ማሚቴ ሆይ አደራዬን ሰጥቼሻለሁ» ብለው መናዘዛቸው በታሪክ ይወሳል። በዚሁ መሠረት ንግሥት ዘውዲቱ በታኅሣሥ ወር1920 ዓ.ም የአፄ ምኒልክን ዓፅም ከቤተ መንግሥቱ አስወጥተው ለማረፊያው በታዕካ ነገሥት በአታ ቤተ ክርስቲያን አሳንፀው በነበረ ጊዜ የእቴጌንም ዓጽም እዚሁ እንዲያርፍ ቢፈልጉም የእንጦጦ ማርያም ካህናት እቴጌ ጣይቱ ለኛም እናታችን ናቸውና መታሰቢያነታቸውን እንሻለን በማለት የተቃውሞ ድምፅ አሰሙ። ቢሆንም የኑዛዜውን ቃል አብራርተው በማስረዳታቸው ፈቅደውላቸዋል። በመጨረሻም የእቴጌ ጣይቱ፣ የአፄ ምኒልክና የንግሥት ዘውዲቱ መካነ መቃብር በታዕካ ነገሥት በዓታ ቤተ ክርስቲያን ምድር ቤት ውስጥ በመንበሩ ትይዩ ሳጥኖች ተፈልፍለው በተሰሩ እብነ በረድ ታሽገው እንደቆዩ በወለሉ ላይ መደዳውን ተቀምጠው ይገኛሉ።
እቴጌ ጣይቱ በሞት የተለዩዋቸውን የሕይወት ጓደኛቸውን ጥለው በግዞት እንዲቆዩ በተገደዱበት በእንጦጦ አፋፍ ላይ ሆነው አዲስ አበባ ብለው የሰየሟትን መዲና በዓይን በመቃኘት «ያ ቤት የትኛው ነው?» ብለው የጠየቁት የምኒልክን መቃብር በዓይናቸው ሲፈልጉ ይሆን? የሰው ሕይወት ኃላፊ ነው፤ ታሪክ ግን ሠሪዋን ለዘላለም ታስታውሳለች። በዚያች ደቂቃ እቴጌ ጣይቱ ስማቸውን የሚያስጠራ ታሪካቸውን የሚያስታውስ አንድ የምኒልክ የደም ቋጠሮ ሀረግ ሳያሠሩ ማለፋቸው ሳያሳዝናቸው እንዳልቀረ መገመቱ ቀላል ነው። ይህንም ሀዘን ለግዞት ወደ እንጦጦ ከመውጣታቸው ጥቂት ጊዜ በፊት ሊሸኟቸው በተሰበሰቡት መኳንንትና ወይዛዝርት ፊት የገጠሙት ግጥም አንጀት የሚበላ ነበር።  «ተወዶ ከመኖር ተጠልቶ መውለድ
ማን ያይብኝ ነበር ይህን ሁሉ ጉድ»
Filed in: Amharic