>

የህወሓት ግፍ በጥቂቱ የተገለጸበት የፍርድቤት ውሎ!!! (ታምሩ ጽጌ)

የህወሓት ግፍ በጥቂቱ የተገለጸበት የፍርድቤት ውሎ!!!
ታምሩ ጽጌ
* በርካታ ዜጎችን የግንቦት ሰባት አርበኞችና የኦነግ አባል እንደሆኑ በመንገር፣ ብልታቸውን በፒንሳ መጎተት፣ ጥፍራቸውን በጉጠት በመንቀል፣ ራቁታቸውን በማድረግ በላይተር ማቃጠል፣ ሴቶችን እርቃናቸውን በበርካታ እስረኞች መሀል ማሰርና ማሰቃየት፣ ውኃ እየደፉ በመደብደብ አሰቃቂ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች መፈጸማቸውን መርማሪ ቡድኑ አስረድቷል!
በዓለምአቀፍ የአሸባሪዎች የመረጃ ቋት ውስጥ በአሸባሪነት እስካሁን ተመዝግቦ የሚገኘው ህወሓት (የትግራይ ህዝብ ነጻ አውጪ ግምባር) ላለፉት 27ዓመታት በግፍ በነጻ አውጪ ስም ኢትዮጵያን በሚገዛበት ጊዜ ለጥቅሙ ባሰማራቸው አረመኔዎች የተፈጸመው ግፍ ጥቂቱ ፍርድቤት ተነግሯል። (http://www.start.umd.edu/gtd/search/Results.aspx?perpetrator=2127) ሪፖርተር ባወጣው የዜና ዘገባ መሠረት በሰብዓዊ መብቶች ጥሰት ተጠርጥረው የተያዙት የህወሃት የደኅንነት አባላት በሕዝብ ላይ የፈጸሙትን ግፍ መርማሪ ቡድኑ ሲያቀርብ ጥቂቱን ግፍ በዚህ መልኩ ገልጾታል።
“… በጨለማ ቤት ውስጥ ለረዥም ጊዜ በማሰርና በመደብደብ ማሰቃየት፣ እግርና እጅ በሰንሰለት አስሮና ጣሪያ ላይ ሰቅሎ መግረፍ፣ በኤሌክትሪክ ገመድ መግረፍ፣ በሙሉ አካላቸው ታስረው በደረሰባቸው ደብደባ አካላቸው ጎድሎ በዊልቸር፣ በዱላና በሰው ተደግፈው እስከሚሄዱ መደብደብ፣ ራቁታቸውን አስሮ ገንዳና ቆሻሻ ቦታ ውስጥ በመጣል በጉንዳን ማስበላት፣ ዱላው በዝቶባቸው ያመኑ እስረኞች ቃል እንዲሰጡ ሲደረጉ፣ ‹አልፈጸምንም› ሲሉ በድጋሚ እየተቀባበሉ ድብደባ እንደተፈጸመባቸው ቡድኑ ገልጿል።
“ተጠርጣሪዎቹ በጎንደር ደኅንነት ቢሮ፣ በሐዋሳና በባህር ዳር የታሰሩ በርካታ ዜጎችን የግንቦት ሰባት አርበኞችና የኦነግ አባል እንደሆኑ በመንገር፣ ብልታቸውን በፒንሳ መጎተት፣ ጥፍራቸውን በጉጠት በመንቀል፣ ራቁታቸውን በማድረግ በላይተር ማቃጠል፣ ሴቶችን እርቃናቸውን በበርካታ እስረኞች መሀል ማሰርና ማሰቃየት፣ ውኃ እየደፉ በመደብደብ አሰቃቂ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች መፈጸማቸውን መርማሪ ቡድኑ አስረድቷል።”
ሙሉው የዜና ዝርዝር ከዚህ እንደሚከተለው ቀርቧል፤ (https://www.ethiopianreporter.com/article/14014)
በሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ተጠርጥረው የታሰሩ የደኅንነት አባላት ፈጽመውታል የተባለ ድርጊት ተገለጸ
* “መንግሥት ምርመራው ተጠናቋል ስላለ ተጨማሪ ጊዜ ሊፈቀድ አይገባም” ተጠርጣሪዎች
በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ አሉ በተባሉ ሰባት ሥውር እስር ቤቶችና በክልል የተለያዩ እስር ቤቶች ውስጥ ከፍተኛና አሰቃቂ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ወንጀል ተጠርጥረው በእስር ላይ የሚገኙት የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት አባላት፣ የፌዴራል ፖሊስና የአዲስ አበባ ፖሊስ ወንጀል መርማሪ አባላትና የፌዴራል ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር ኃላፊዎችና አባላት ፈጽመውታል የተባለው የወንጀል ድርጊት በፍርድ ቤት ተገለጸ።
ተጠርጣሪዎቹ በተጠቀሱት ተቋማት ውስጥ ከምክትል ዋና ዳይሬክተር እስከ ሠራተኛ ሲሆኑ፣ የአርበኞች ግንቦት ሰባትና የኦነግ አባል ናቸው በማለት ቁጥራቸው በርካታ የሆኑ ዜጎች ላይ ሊፈጸሙ ሳይሆን ሊታሰቡ የማይችሉ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ወንጀል መፈጸማቸውን፣ የፌዴራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ቡድን ጉዳዩን እያየው ለሚገኘው ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ አሥረኛ ወንጀል ችሎት አስረድቷል።
በተለይ በከፍተኛ ሁኔታ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ተፈጽመውባቸዋል የተባለው ነሐሴ 28 ቀን 2008 ዓ.ም. ከቂሊንጦ እስረኛ ማረፊያ ቤት ቃጠሎ ጋር በተያያዘ፣ ተጠርጥረው በነበሩ እስረኞችና በጳጉሜን 2006 ዓ.ም. በኢትዮጵያና ናይጄሪያ ብሔራዊ ቡድኖች የዓለም ዋንጫ ማጣሪያ እግር ኳስ ግጥሚያ ላይ ቦምብ በማፈንዳት ተጠርጥረው በተያዙ ግለሰቦች ላይ ነው። የቂሊንጦን የእሳት ቃጠሎ ያስነሱትና ለ23 እስረኞች ሞት፣ ከ15 ሚሊዮን ብር በላይ ለሚገመት ንብረት ወድመት ተጠርጣሪዎቹ እስረኞቹ ናቸው በማለት ሸዋ ሮቢት ማረሚያ ቤት ተወስደው ምርመራ እንዲደረግባቸው መደረጉን መርማሪ ቡድኑ አስረድቷል።
በአቶ ጎሃ አጽብሃ የምርመራ መዝገብ የተካተቱት 33 ተጠርጣሪዎች፣ በወቅቱ አሸባሪ ድርጀቶች ናቸው በተባሉት ግንቦት ሰባትና ኦነግ ውስጥ አባል በመሆን፣ በተሰጣቸው ተልዕኮ ቂሊንጦን እንዳቃጠሉ ለማሳመን ከፍተኛ የሆነ የሰብዓዊ መብት ጥሰት እንደተፈጸመባቸው አስረድቷል። ታራሚዎቹን በጨለማ ቤት ውስጥ ለረዥም ጊዜ በማሰርና በመደብደብ ማሰቃየት፣ እግርና እጅ በሰንሰለት አስሮና ጣሪያ ላይ ሰቅሎ መግረፍ፣ በኤሌክትሪክ ገመድ መግረፍ፣ በሙሉ አካላቸው ታስረው በደረሰባቸው ደብደባ አካላቸው ጎድሎ በዊልቸር፣ በዱላና በሰው ተደግፈው እስከሚሄዱ መደብደብ፣ ራቁታቸውን አስሮ ገንዳና ቆሻሻ ቦታ ውስጥ በመጣል በጉንዳን ማስበላት፣ ዱላው በዝቶባቸው ያመኑ እስረኞች ቃል እንዲሰጡ ሲደረጉ፣ ‹‹አልፈጸምንም›› ሲሉ በድጋሚ እየተቀባበሉ ድብደባ እንደተፈጸመባቸው ቡድኑ ገልጿል።
ተጠርጣሪዎቹ በጎንደር ደኅንነት ቢሮ፣ በሐዋሳና በባህር ዳር የታሰሩ በርካታ ዜጎችን የግንቦት ሰባት አርበኞችና የኦነግ አባል እንደሆኑ በመንገር፣ ብልታቸውን በፒንሳ መጎተት፣ ጥፍራቸውን በጉጠት በመንቀል፣ ራቁታቸውን በማድረግ በላይተር ማቃጠል፣ ሴቶችን እርቃናቸውን በበርካታ እስረኞች መሀል ማሰርና ማሰቃየት፣ ውኃ እየደፉ በመደብደብ አሰቃቂ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች መፈጸማቸውን መርማሪ ቡድኑ አስረድቷል።
መርማሪ ቡድኑ ከላይ የጠቀሳቸውን ድርጊቶች የሰማው ከ70 በላይ ተጎጂዎችንና ሌሎች እማኞችን ቃል በመቀበል መሆኑንም አስረድቷል። ከተጠርጣሪዎች የተወሰኑትን ቃል መቀበሉን፣ ያልተያዙ ተጠርጣሪዎችን ለሕግ ለማቅረብ ክትትል እያደረገ መሆኑንና የተጎጂዎችን የአካል ጉዳት መጠን ለማወቅ ለሆስፒታሎች ደብዳቤ መስጠቱን ገልጿል።
በተለይ ሸዋ ሮቢት ማረሚያ ቤት ተወስደው ድብደባና የተለያዩ ሥቃይ የደረሰባቸውን ተጎጂዎች ቃል መቀበልና የተለያዩ ማስረጃዎችን መሰብሰብ እንደሚቀረው በመግለጽ፣ ተጨማሪ 14 ቀናት እንዲፈቀድለት ጠይቋል።
ተጠርጣሪዎቹ በጠበቃና በተከላካይ ጠበቃ ተወክለው መርማሪ ቡድኑ ላቀረበው የምርመራ ሪፖርት ምላሽ ሰጥተዋል። መርማሪ ቡድኑ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ፈጽመዋል በማለት የገለጻቸው ተጠርጣሪዎች ከአራት ተቋማት የታሰሩ መሆናቸውን ጠቁመው፣ ማቅረብ ያለበት በተናጠል መሆን እንደነበረበት አስረድተዋል። በጠበቃ የተወከሉት ተጠርጣሪዎች እንደተናገሩት፣ እነሱን አስሮ ወንጀልና ማስረጃ መፈለግ ሕገ መንግሥቱን መጣስ መሆኑንም አክለዋል። የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት የኢኮኖሚ ዘርፍ ምክትል ዳይሬክተር መሆናቸውን የገለጹት አቶ ደርበው ደመላሽ ለፍርድ ቤቱ እንደገለጹት፣ የሥራ ድርሻቸው ፀረ ሰላም ኃይሎችን በመሰለል መከላከል እንጂ፣ ከአርበኞች ግንቦት ሰባትና ከኦነግ ጋር ምንም የሚያገናኛቸው ነገር የለም። ከልጅነታቸው ጀምሮ የሚታወቁት ሥራቸውን በአግባቡ በመሥራት፣ በመመሥገንና ዕድገት በማግኘት ነው። ይኼንን አሁን ያሰራቸውም አካል እንደሚያውቅና ይጠብቁት የነበረው ሽልማት እንጂ መታሰር እንዳልነበረም ተናግረዋል።
የሰኔ 16 ቀን 2010 ዓ.ም. ቦምብ ፍንዳታን በሚመለከት እንዲያጣሩ ተመድበው ውጤታማ ሥራ መሥራታቸውንም አክለዋል። በመሆኑም ፍርድ ቤቱ የዋስ መብታቸውን ጠብቆላቸው ከእስር እንዲለቀቁ ጠይቀዋል።
መርማሪ ቡድኑ ተጠርጣሪዎችን በምስክሮች እስሚያስለይ ድረስ በእስር እንዲቆዩ መጠየቁን የተቃወሙት ተጠርጣሪዎቹ፣ ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ በተጠርጣሪዎቹ ላይ ማስረጃ ሰብስብን ጨርሰናል ብሎ ከተናገረ በኋላ፣ 14 ቀናት ሊጠየቅባቸው እንደማይገባም አስረድተዋል። መርማሪ ፖሊስ ለፍርድ ቤቱ ሲያስረዳ በተጠርጣሪዎቹ የተደበደቡ ሰዎች እንደሞቱ በደፈናው ከመግለጽ ባለፈ ስንት ሰዎች እንደ ሞቱ፣ የት እንደተቀበሩና መቼ ድርጊቱ እንደተፈጸመ ሳይገልጽ፣ ዝም ብሎ ተጨማሪ ጊዜ ቀጠሮ መጠየቅ ተገቢ አለመሆኑን ተናግረዋል።
የተጠረጠሩበት ወንጀል እውነት መሆን አለመሆኑ ሳይረጋገጥ ደመወዛቸው በመታገዱ፣ ቤተሰቦቻቸው በተለይም ሕፃናት ልጆቻቸው በጉዳት ላይ መሆናቸውን በመጠቆም፣ ፍርድ ቤቱ መፍትሔ እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል። ሕፃናትን ምግብ መከልከል የሰብዓዊ መብት ጥሰት መሆኑን በመናገር፣ እነሱ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ፈጽመዋል እየተባለ ሌላ የሰብዓዊ መብት ጥሰት እንዳይፈጸም ብለዋል።
መርማሪ ቡድኑ በሕጉና በአግባቡ ምርመራ ማድረግ ሲገባው፣ ለ30 ደቂቃ ያህል ተጠርጣሪን ቃለ መጠይቅ ካደረገ በኋላ የሕይወት ታሪካቸው ነው መባሉ ተገቢ አለመሆኑን አስረድተዋል።
ለ27 ዓመታት የአገሪቱን ብሔራዊ ጥቅም ለመጠበቅና ሕዝብን ለማገልገል እንደሠሩ የገለጹት ተጠርጣሪዎቹ፣ መርማሪ ፖሊስ ጊዜ ቀጠሮ ለማስፈቀድ ብቻ ከመሥራት ይልቅ በአግባቡ መሥራት እንዳበት ተናግረዋል። ሁሉም የመንግሥት ተቋማት ውስጥ የሚሠሩ መሆናቸውን በመጠቆም፣ ሰነዶች ለመሰብሰብ የሰዓታት ሥራ በመሆኑ 14 ቀናት ተገቢ አለመሆኑን ገልጸዋል።
በተለይ የቂሊንጦን ቃጠሎ በሚመለከት በተጠርጣሪዎቹ ላይ የሰብዓዊ መብት ጥሰት መፈጸም እንደሌለበት፣ ከቀድሞ የጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ አቶ ጌታቸው አምባዬ ጋር ጭምር ተነጋግረውና ተስምማተው እንደነበርና በወቅቱ በታራሚዎቹ ላይ ጉዳት እንዳይደርስ መሥራታቸውን የጠቆሙት የፌዴራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ አባል ኮማንደር ዓለማየሁ ኃይሉ፣ አሁን እንዲታሰሩ የተደረጉት ሆን ተብሎ እሳቸውን ለማሰቃየት መሆኑን ተናግረዋል።
ፍርድ ቤት ምርመራውን እያቀረቡ ያሉት መርማሪዎች ምንም እንደማያውቁና ምርመራው ከተሠራ አምስት ወራት እንደሆነው ገልጸው፣ ‹‹ትናንትና የነበረው ዛሬ የሚደገም ከሆነ ምን ዋጋ አለው?›› በማለትም ጠይቀዋል። በአጠቃላይ እየተመረመሩ ያለበት ሁኔታ አግባብ እንዳልሆነና ምርመራው መጠናቀቁ በኃላፊዎች ጭምር ከተነገረና በመገናኛ ብዙኃን ከተላለፈ በኋላ፣ እንደገና ለምርመራ ተጨማሪ ጊዜ መጠየቅ ተገቢ አለመሆኑን በማስረዳት ዋስትና መብት እንዲከበርላቸው ጠይቀዋል።
ከተጠርጣሪዎቹ ውስጥ 15 የመንግሥት ሠራተኞችና ወርኃዊ ደመወዝተኛ መሆናቸውን በመሃላ በማረጋገጥ፣ መንግሥት ተከላካይ ጠበቃ እንዲያቆምላቸው ጠይቀው ተመድቦላቸዋል።
የተመደቡት ተከላካይ ጠበቆች መርማሪ ቡድኑ ያቀረበውን የምርመራ ሒደት ተቃውመዋል። ተጠርጣሪዎቹ ይሠሩ የነበረው በተለያዩ አራት ተቋማት ውስጥ በመሆኑ የተጠረጠሩበት ጉዳይ ተለይቶ መቅረብ እንዳለበት በመግለጽ ተከራክረዋል። ምርመራ መጠናቀቁ በመንግሥት ተነግሮ እያለ፣ እንደ አዲስ ተደርጎ የምርመራ ጊዜ መጠየቁ ተገቢ አለመሆኑንም አክለዋል።
ፍርድ ቤቱ የግራ ቀኙን ክርክር መርምሮ ብይን ለመስጠት ለዛሬ ኅዳር 19 ቀን 2011 ዓ.ም. ከሰዓት በኋላ ቀጠሮ ሰጥቷል።
ከብረታ ብረት ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን (ሜቴክ) ከፍተኛ ኃላፊዎች ጋር በጥቅም በመመሳጠር 945,770 ብር የመንግሥት ገንዘብ ወስዳለች የተባለችውን ተጠርጣሪና የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን የመዝናኛ ፕሮግራሞ አስተዋዋቂ ወ/ሮ ፍፁም የሺጥላን በሚመለከትም፣ መርማሪ ቡድኑ ለፍርድ ቤቱ ተጨማሪ ሪፖርት አቅርቧል።
ተጠርጣሪዋ የሜቴክ ዋና ዳይሬክተር ከነበሩት ሜጀር ጄኔራል ክንፈ ዳኛው ጋር በመመሳጠር፣ የሜቴክ ሠራተኛ ሳትሆን እንደሆነች የሚገልጽ ደብዳቤ ለራሷና ለጓደኛዋ በማጻፍ፣ ለእያንዳንዳቸው 11,500 ዶላር በድምሩ 23,000 ዶላር የመንግሥት ገንዘብ በመውሰድ ለአንድ ወር አሜሪካ ቆይታ አድርጋ መመለሷን ገልጿል። ወ/ሪት ትዕግሥት ታደሰ የተባለችው ተጠርጣሪ ደግሞ ባልተያዘ ተጠርጣሪ የቤት መኪናና ቤት ከመግዛቷም በተጨማሪ ሌላ ሀብት አፍርታለች የሚል ጥርጣሬ እንዳለው ገልጾ፣ ያንን ለማጣራት የተለያዩ መንግሥታዊ ተቋማት ማስረጃ እንዲሰጡት ደብዳቤ መጻፉን አስረድተዋል። ሌላው አቶ ቸርነት ዳና የድለላ ፈቃድ ሳይኖረው፣ እንዳለው በማስመሰልና ከሜቴክ ከፍተኛ ኃላፊዎች ጋር በመመሳጠር ዋይቲኦ ከተባለ የቻይና ኩባንያ ጋር ሜቴክ ውል እንዲገባ በማድረግ፣ በ42 ሚሊዮን ዶላር 1,480 የእርሻ ትራክተሮች በማስገዛት ሰባት ሚሊዮን ብር ኮሚሽን ማግኘቱን አስረድቷል። ሜቴክ የመግዛት ፍላጎት ሳይኖረው እንዲገዛ በማድረግ በመንግሥት ላይ ከባድ ጉዳት ማድረሱን በመግለጽ ለተጨማሪ ምርመራ የ14 ቀናት ጊዜ ጠይቋል።
በተከላካይ ጠበቃ የተወከሉት ወ/ሮ ፍፁም የሺጥላና ወ/ሪት ትዕግሥት በሰጡት ምላሽ ወ/ሮ ፍፁም 18 ቀናት የታሰረች ቢሆንም፣ የተጠየቀችው የምስክርነት ቃል እንድትሰጥ እንጂ የተከሳሽነት ቃል እንዳልሰጠች አስረድተዋል። ወ/ሪት ትዕግሥት የማስተርስ ዲግሪ ተማሪ በመሆኗ ፍርድ ቤቱ ፈተና እንድትፈተን እንዲፈቅድላት ጠይቀዋል። በተጨማሪም የተጠረጠረችበት ጉዳይ የሚንቀሳቀስና የማይንቀሳቀስ ንብረት በመሆኑ፣ የእሱን ትክክለኛነት ለማረጋገጥ ሰነድ ለማግኘት 14 ቀናት መጠየቅ ተገቢ አለመሆኑንም ተከላካይ ጠበቆቹ ገልጸዋል። ሊብሬና ካርታ የሚገኘው ከመንግሥት ተቋም በመሆኑ እሷን በእስር ሊያቆይ የሚችል ነገር እንደሌለም አክለዋል።
ፍርድ ቤቱ የግራ ቀኙን ክርክር ከሰማ በኋላ፣ ለመርማሪ ቡድኑ አሥር ቀናትን በመፍቀድ ለኅዳር 27 ቀን 2011 ዓ.ም. ቀጠሮ ሰጥቷል።
በአዳር ለማክሰኞ ለኅዳር 18 ቀን 2011 ዓ.ም. የቀረቡት ደግሞ በእነ ብርጋዴር ጄኔራል ጠና ቁርንዲ መዝገብ በከባድ የሙስና ወንጀል የተጠረጠሩ 26 ኃላፊዎችና ሠራተኞች ናቸው። የፌዴራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ቡድን እያንዳንዱ ተጠርጣሪ ፈጽሟል ያለውን የወንጀል ድርጊት ለፍርድ ቤቱ አስረድቷል። አራት ተጠርጣሪዎች ለቀረበባቸው የጥርጣሬ ክስ ምላሽ እየሰጡ ሰዓት በመምሸቱ፣ በአዳር ለረቡዕ ኅዳር 19 ቀን 2011 ዓ.ም. ቀጠሮ ተሰጥቷል።
የፌዴራል ፖሊስ መርማሪ ቡድን በሰብዓዊ መብት ጥሰት ከተጠረጠሩት መካከል ወ/ሮ አዳነች ተሰማና አቶ ጌታሁን አሰፋን በፖሊስ ጣቢያ በዋስ መልቀቁን ለፍርድ ቤቱ የገለጸ ሲሆን፣ ወ/ሮ ሙሉ ፍሰሐ የተባሉትን ተጠርጣሪ ፍርድ ቤቱ በ3,000 ብር ዋስ እንዲለቀቁ ትዕዛዝ ሰጥቷል። በሌላ በኩል የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት የአንድ ክፍል ኃላፊ የነበሩትን አቶ ተስፋዬ ገብረ ፃዲቅንና ሰነዶችን በማሸሽ ተጠርጥረው ታስረው የነበሩትን አቶ ፊሊሞን ግርማይና አቶ ቴዎድሮስ ጣዕምአለውን፣ እያንዳንዳቸው በአሥር ሺሕ ብር ዋስ እንዲለቀቁ ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ ሰጥቷል።
የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ምክትል ዋና ዳይሬክተር የነበሩትን ሐሺም ቶፊቅ (ዶ/ር) በመሸሸግና የጦር መሣሪያ በማሸሸ ተጠርጥረው የታሰሩት ባለቤታቸው ወ/ሮ ዊዳት አህመድና አቶ ሰሚር አህመድን በሚመለከት፣ መርማሪ ቡድኑ ዝርዝር ጥርጣሬውን እንዲያቀርብ ትዕዛዝ በመስጠት ለኅዳር 19 ቀን 2011 ዓ.ም. ቀጠሮ ሰጥቷል።
የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት ምክትል ዋና ዳይሬክተርና የአገር ውስጥ ደኅንነት ኃላፊ የነበሩትን አቶ ያሬድ ዘሪሁንን በማስመለጥና ሰነዶችን በመሸሸግ ተጠርጥረው የነበሩትን ንሰሐ አባት አባ ኃብተ ማርያም ኃይለ ሚካኤልና አቶ አሸናፊ ታደለን፣ ፖሊስ በዋስ መልቀቁን የሚያረጋግጥ ደብዳቤ ለፍርድ ቤቱ አቅርቧል።
Filed in: Amharic