>
5:13 pm - Tuesday April 19, 0191

እነ አቶ በረከት በማረሚያ ቤቱ ኢንተርኔት የለም ሲሉ ለፍርድ ቤት ተናገሩ - ቢቢሲ አማርኛ

እነ አቶ በረከት በማረሚያ ቤቱ ኢንተርኔት የለም ሲሉ ለፍርድ ቤት ተናገሩ (ቢቢሲ አማርኛ)

በጥረት ኮርፖሬት የሃብት ብክነት የተጠረጠሩት አቶ በረከት ስምኦንና አቶ ታደሰ ካሣ ዛሬ በባህር ዳርና አካባቢዋ ፍርድ ቤት ቀርበዋል።

የአማራ ክልል ፀረ ሙስና ኮሚሽን መርማሪ ባለፈው በተሰጠው የጊዜ ቀጠሮ ማስረጃዎችን ማየቱንና የምስክሮችን ቃል መቀበሉን አሳውቋል።

ሆኖም ጉዳዩ ከባድ፣ ውስብስብና ድንበር ተሻጋሪ ከመሆኑም በላይ ምስክሮች እና ሰነዶች በሃገር ውስጥ እና ከሃገር ውጪ መገኘታቸውን አስታውሶ ምርመራውን አለማጠናቀቁን አስታውቋል።

• በረከት ስምኦን ከየት ተነስተው እዚህ ደረሱ

ከዚህ ተጨማሪ የ14 ቀን የጊዜ ቀጠሮ እንዲሰጠው ጠይቋል።

የሕግ ሥልጣን በሌለው አካል መከሰሰሳቸውን የጠቀሱት አቶ በረከት ሰምኦን ተጨማሪ የጊዜ ቀጠሮው ውድቅ አንዲሆን ጠይቀው ነበር።

የዳሽን ቢራ ሁሉም ሰነዶች ተሟልተው እንደሚገኙ የተናገሩት አቶ ታደሰ ካሣ በበኩላቸው መነግሥት አስረን አናጣራም፤ አጣርተን ነው የምናስረው ማለቱን ጠቅሰው የተጠየቀው የጊዜ ቀጠሮ አነሱን በእስር ለማቆየት ብቻ መሆኑን በመጠቆም ውድቅ አንዲሆን ጠይቀዋል።

የግራ ቀኙን የተመለከተው ፍርድ ቤቱ የጉዳዩን ውስብስብነትና መረጃዎች በሃገር ውስጥም ሆነ በውጭ መገኘታቸውን ከግምት በማስገባት የ14 ቀን ጊዜ ቀጠሮውን ፈቅዷል።

• አቶ በረከት ስምኦን እና አቶ ታደሰ ካሳ ወደ ባህር ዳር ተወሰዱ

• አቶ በረከት ስምኦን ከብአዴን ማእከላዊ ኮሚቴ አባልነት ታገዱ

አቶ በረከት ስንገባም ስንወጣም አየተሰደብንና ስማችን እየጎደፈ ነው ብለዋል።

ጠበቃ ማግኘት ባለመቻላቸው ፍርድ ቤቱ እንዲያቆምላቸውና ከቤተሰባቸው ጋር የመገናኘት ዕድል እንዲመቻችላቸው ጠይቀዋል።

በተጨማሪም ተከሳሾቹ በማረሚያ ቤት ለመፃፍ የሚያስችላቸው ኮምፒዩተር እንዲገባላቸው ጠይቀዋል። አቶ በረከት በማረሚያ ቤት ውስጥ ኢንተርኔት የለም ሲሉም ተደምጠዋል።

የሚደርስባቸውን ዘለፋ በተመለከተ ፍርድ ቤቱ ከፀጥታ አካላት ጋር በመሆን የሚደርስባቸውን ዘለፋ ለማስቆም እንደሚሰራ አስታውቋል።

Filed in: Amharic