>

ፕ/ር ጌታቸው ኃይሌ እና ዶክተር አክሎግ ቢራራን ጨምሮ ከ40 በላይ ትውልደ ኢትዮጵያዊያን ምሁራንና ታዋቂ ሰዎች በወቅቱ የሀገራችን ጉዳይ ለዶ/ር አቢይ ያስተላለፉት መልእክት


ግልጽ ደብዳቤ ለክቡር ጠ/ሚንስትር ዶር ዐብይ አህመድ !!!
(በአሜሪካ ከምንገኝ ተቆርቋሪ ትውልደ ኢትዮጵያዊያን)
ለባልደራሱ ሰብሳቢ እና የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ታላቁ እስክንድር ነጋ ኢትዮጵያውያን ከየዓለማቱ አጋርነታቸውን እየገለጡለት ነው::
———–
ፕ/ር ጌታቸው ኃይሌ እና ዶክተር አክሎግ ቢራራን ጨምሮ ከ40 በላይ ትውልደ ኢትዮጵያዊያን ምሁራንና ታዋቂ ሰዎች በወቅቱ የሀገራችን ጉዳይ ለዶ/ር አቢይ ያስተላለፉት መልእክት 
March 26, 2019
መጋቢት 18, 2011 ዓ.ም.
ለክቡር ጠ/ሚንስትር ዶር ዐብይ አህመድ
አዲስ አበባ፤ ኢትዮጵያ
ጉዳዩ፦ አዲስ አበባና የሰብአዊ መብት ታጋዩ የጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ጉዳይ
በአሜሪካ ከምንገኝ ተቆርቋሪ ትውልደ ኢትዮጵያዊያን
ውድ ጠ/ሚንስትር ዶር ዐብይ፤
መጀመሪያ አገራችንን ኢትዮጵያንና መላውን 110 ሚሊየን አስደናቂ ስብጥር ሕዝቧን በቅንነት፤ ሚዛናዊ በሆነ መንገድ ለዘላቂ ሰላምና እርጋታ፤ ለፍቅር፤ ለፍትህ፤ ለአብሮነት፤ ለእውነተኛ የዜጎች እኩልነት፤ ለሕግ የበላይነት፤ ለፍትሃዊ፤ ዘላቂ እድገት እና በመድብለ ፓርቲዎች ውድድር፤ ነጻና ፍትሃዊ ምርጫ ተካሂዶ፤ በሕዝብ ተሳታፊነትና ወሳኝነት ሊመሰረት ለሚገባው የዲሞክራሲ አገዛዝ የጀመሩት የአንድ ዓመት የለውጥ ጉዞ ስኬታማ እንዲሆን ያለንን ምኞት እንገልጻለን።
ሁላችንም የምንኮራባት ታሪካዊዋ ኢትዮጵያ ከርስ በርስ ግጭትና ጥላቻ፤ ከድህነት፤ ከረሃብ፤ ከስደት፤ ከሰው ሰራሽ ፍልሰትና ከኋላ ቀርነት ኡደት (Cycle) ወጥታ በአፍሪካ ደረጃ ብቻ ሳይሆን በዓለም ደረጃ ቦታዋን እንድትይዝ የጀመሩት ሰላማዊ ለውጥ ሁሉንም ኢትዮያዊያን እንደሚያሳትፍ እንገምታለን፤ ተስፋ እናደርጋለን። በኛ ግምገማ፤ የኢትዮጵያ ብሄራዊ አንድነት፤ ነጻነትና ሉዐላዊነት እንዲሁም ዲሞክራሳዊ አገዛዝ ሊመሰረት የሚችለው የእያንዳንዱ ዜጋ መብት በሕገ-መንግሥቱ ሲከበር ነው። ይህም ማለት የማንኛውም ኢትዮጵያዊ፤ በየትኛውም ገጠር ሆነ ከተማ፤ የመኖር፤ ቤት፤ ንብረትና ቤተሰብ የመመስረት፤ እንደ ልብ የመንቀሳቀስ፤ የመምረጥና የመመረጥ መብቱ ወይንም መብቷ ሲጠበቅ ነው። እርሰዎ ለእነዚህ መብቶች መከበርና ለኢትዮጵያና ለኢትዮጵያዊነት እሴቶች እንደቆሙ እናምናለን።
ይህ እምነታችን እንዳለ ሆኖ፤ በርስዎ መንግሥት ብቻ ከሶስት ሚሊየን በላይ የሚገመተው የአገር ውስጥ እትዮጵያዊ የፈለሰ ሕዝብ ገና ወደ ቀየው እንዲመለስና ተመልሶ እንዲቋቋም ከመደረጉ በፊት ሌሎች በብዙ ሽህ የሚገመቱ ወገኖቻችን ለተመሳሳይ አደጋ መጋለጣቸው እጅግ በጣም እንዳሳሰበን ልንገልጽልዎት እንፈልጋለን። ይህ ሕዝብን ከሕዝብ ጋር የሚያናክስና አገርን የሚያፈርስ ሁኔታ ከአሁኑ ጀምሮ በአስቸኳይ እንዲቆም ያልተቆጠበና የተቀነባበረ የፌደራል መንግሥት ጥረት ይጠይቃል።
በከተማ ሆነ በገጠር ብሄር ተኮር የሆነ ፍልሰት፤ ግድያ፤ ማሰርና ማስፈራራት ለሁሉም ኢትዮጵያዊያን አደገኛ ሂደት ነው። “ይህችን ታላቅ አገር ተቀራርቦ ከመስራት ውጭ ሌላ አማራጭ” የለም እና “ኢትዮጵያ አትበተንም፤ አንተ እስከ ሃሳብህ ድረስ ትበተናለህ እንጅ” ብለው ያሰመሩባቸውን መርሆዎች እኛም እንጋራለን።
በዚህ ዙሪያ እኛን እጅግ ካሳሰቡን አስኳል ጉዳዮች መካከል፤ ባለፉት ሃያ ስምንት ዓመታት የራሳቸውን ህይወት፤ ቤተሰብና ኑሮ ወደ ጎን ትተው ለሁሉም ኢትዮጵያዊያን ሰብአዊ መብቶች፤ ነጻነትና ክብር ከታገሉትና በእስር ቤት ከተሰቃዩት ታላቅ ኢትዮጵያዊያን መካከል ዓለም ያደነቀውና ያከበረው ጋዜጠኛና የሰብአዊ መብት ታጋዩ አቶ እስክንድር ነጋ አንዱ መሆኑ እየታወቀ ዛሬ በሱ ህይወት ላይ የሚካሄደው ዛቻና ማስፈራራት እርሰዎና መንግሥተዎ ከቆማችሁለት መንፈስ ጋር ይጋጫል። ልዩነትም ቢኖር ሰብአዊ መብት መከበር አለበት የሚለው እርሰዎ በተደጋጋሚ ያስተጋቡት እሴት ይህን ኢትዮጵያዊም ይመለከተዋል።
ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ከ1993 ጀምሮ ለኢትዮጵያዊያን ነጻነት፤ መብትና ክብር ሲታገል የቆየ ታላቅና ደፋር ኢትዮጵያዊ ነው። ጋዜጠኛውና የሰብአዊ መብቶች ጠበቃ እስክንድር ነጋ፤ የራሱንና የቤተሰቡን የግል ጥቅም ወደ ጎን ትቶ፤ ህይወቱን ለአደጋ አጋልጦ ዘውግና ኃይማኖት ሳይለይ እስካሁን ለቆመለት የተቀደሰ ዓላማ የሚታገል ኢትዮጵያዊ ነው።
ክቡር ጠ/ሚንስትሩ እንደሚያውቁት፤ ጋዤጠኛ እስክንድር ነጋ፤ በ July 13, 2012፣ ህወሓት በበላይነት ይመራው በነበረው ጨካኝና አፋኝ የኢህአዴግ መንግሥት በፈጠራ ወሬ “ሽብርተኛ ነህ” ተብሎ ተከስሶ ለ 18 ዓመታት እንዲታሰር ተፈረደበት። ለ 7 ዓመታት በቃሊቲ እስር ቤት ሲሰቃይ ከቆየ በኋላ በ February 2018 ተፈታ። አንድ ወር ሳይሞላ፤ በ March 2018, እንደ ገና ታሰረ። የታሰረበት ዋና ምክንያት ብዙ ሚሊየን የኢትዮጵያ ሕዝብ መለያ አድርጎ የተቀበለውን “አረንጓዴ፤ ብጫና ቀይ የሆነውን ሰንደ ዓላማ ” በስብሰባው አዳራሽ ስለተጠቀመ ነው።
የሰብአዊ መብት አክቲቪስትና የመናገር ነጻነት “ጀግና” ተብሎ የተጠራው እስክንድር ነጋ ዓለም ያከበረው ኢትዮጵያዊ ነው። በ May 1, 2012, እስክንድር ነጋ በዓለም ደረጃ የታወቀውን የ Pen/Barbara Goldsmith Freedom ሜዳል ተሸልሟል። እንደገና በ May 18, 2017 የ International Press Institute (IPI)’s 69th World Freedom Hero Award ተሸልሟል። Amnesty International, the Committee to Protect Journalists (CPJ), Freedom House, Human Rights Watch እና ሌሎች የታወቁ ድርጅቶችና ግለሰቦች ይህ ኢትዮጵያዊ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ብቻ ሳይሆን ለመላው ዓለም ሕዝብ ሰብአዊ መብት ተሟጋች መሆኑን መስክረውለታል። ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ባለፉት ሃያ ስድስት አመታት የከፈለውን ዋጋና ያበረከተውን አስተዋጾ በዚህ አጭር ደብዳቤ ለማቅረብ አይቻልም።
በኛ እምነት፤ በቅርቡ በአዲስ አበባ የተከሰተው አለመግባባት ለሁላችንም አስደንጋጭ የሆነው የባለቤትነት ጥያቄ የሁሉም ኢትዮጵያዊያን ጉዳይ ነው። የአንድ ዘውግ ወይንም የአንድ ክልል ጉዳይ አይደለም። እንዲያውም የአዲስ አበባ ጉዳይ የመላው ኢትዮጵያ ሕዝብ ብቻ ሳይሆን፤ የመላው የጥቁር አፍሪካ አገሮች ጉዳይ ነው።
የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪ የሆነው ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ ከሚመለከታቸው የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ጋር ሆኖ ያደረገው ሰላማዊና ጨዋነት የተሞላበት ውይይትና አቤቱታ ያስመስግናል እንጅ ግለሰቡን፤ ቤተሰቡን፤ በመላው ኢትዮጵያና በዓለም ዙሪያ የሚገኙ በብዙ ሚሊየን የሚቆተሩ ወዳጆቹን፤ አድናቂዎቹንና ደጋፊዎቹን የሚያስወቅስና የሚያሳሳብ ጉዳይ አይደለም። የቆመለት ጉዳይ የግል ዝና ወይንም ጥቅም ጉዳይ አይደለም፤ የሁላችንም ጉዳይ መሆኑን ልናስምርበት እንፈልጋለን።
ሕገ መንግሥቱ እንደሚደነግገውና የአዲስ አበባ የአሥተዳደር ህግና ደንብ እንደወሰነው፤ ልምድ በሆነው የአስተዳደር መመሪያ መሰረት ነዋሪው ከ 5 ሚሊየን በላይ የሚገመተው የአዲስ አበባ ሕዝብ ራሱን የማስተዳደር፤ ፖሊሲዎችንና መመሪያዎችን የማሻሻል መብት እንዳለው እኛም እናምናለን።
የአዲስ አበባ ሕዝብ መመራትና መስተዳደር ያለበት ነዋሪው ሕዝብ በመረጣቸው ሃላፊዎች መሆን አለበት። ጋዤጠኛ እስክንድር ያደረገው ከዚህ የተለየ አይደለም። ደጋግሞ የተናገረው የነዋሪዎቹ ሰብአዊና ዲሞክራሳዊ መብት ይጠበቅ ነው።
ስለዚህ፤ ክቡር ጠ/ሚንስትር ዶር ዐብይ አህመድን በትህትና የምንጠይቀው በእስክንድር ነጋ ላይ የሚካሄደው ማስፈራራትና አላስፈላጊ ዛቻና በአስቸኳይ እንዲቆምና በዚህ የታወቀና ጨዋ ኢትዮጵያዊ ላይ አደጋ እንዳይደርስበት ትኩረት እንዲሰጡልን ድምጻችን ለማሰማት ነው።
ተቆርቋሪ ትውልደ ኢትዮጵያዊያን
ፕሮፌሰር ጌታቸው ኃይሌ
ዶር አምባቸው ወረታ
አቶ መስፍን መኮነን
አቶ ነጋሽ ገብሬ
ዶር ታደለ ዓለሙ
ዶር ያእቆብ ኃይለማርያም
ዶር አክሎግ ቢራራ
ዶር አልማዝ ዘውዴ
ፕሮሬሰር ከበደ ገሰሰ
አቶ ግርማ ተፈራ
ወይዘሮ ጽጌረዳ ሙሉጌታ
አቶ ዘውገ ገድሉ
ፕሮፌሰር ብርሃኑ ምንግሥቱ
አቶ ከፋለኝ አስራት
አቶ ስዮም ዘነበ
አቶ አስማማው እጂጉ
ዶር ስዩም ሰሎሞን
አቶ አባተ ካሳ
አቶ መላኪ ውቤ
አቶ ተስፋየ አንበርብር
አቶ አለማየሁ አበበ
ወይዘሮ ሲና አስረስ
አቶ እስክንድር እዮብ
አቶ ብርሃኑ አለሙ
አቶ ልዑልሰገድ ሙሉሸዋ
ዶር እርምያስ ሽኩር
አቶ ተስፋየ ተሰማ
ወይዘሮ አሰገደች መኮነን
አቶ ሙሉጌታ ፈለቀ
አቶ አዳነ ንጉሴ
አቶ ውብሸት ተሰማ
አቶ ተፈሪ መኮነን
ዶር አበበ ገላጋይ
አቶ ዘነበ ዓለማየሁ
ወይዘሮ ወሰንየለሽ ደበላ
አቶ ስዮም ገላጋይ
አቶ ወርቁ አደራጀው
ፕሮፌሰር አቻምየለህ ደበላ
አቶ ጌታቸው ዋና
አቶ ተክሌ የሻው
አቶ ነብያት ደምሴ
አቶ ኪዳኔ ዓለማየሁ
Filed in: Amharic