>
5:13 pm - Saturday April 19, 9552

ኢትዮጵያ ላይ አትዶልቱ!  (አስራት ብርሀኑ)

ኢትዮጵያ ላይ አትዶልቱ! 
አስራት ብርሀኑ
 * …ድብቅ ዓላማችሁ መቼም ቢሆን ይጋለጣልና በከንቱ አትፍጨርጨሩ፡፡ በአደባባይ ኢትዮጵያዬ እያላችሁ ከመጋረጃው ጀርባ የምታሴሩም ሆነ፣ በድፍረት ተሞልታችሁ በግልጽ ኢትዮጵያን ለማፍረስ የምትባዝኑ መቼም አይሳካላችሁም
ኢትዮጵያ ከሥልጣን በላይ ናት፡፡ ኢትዮጵያ ከማናቸውም ጥቅማ ጥቅሞች በላይ ናት፡፡ ኢትዮጵያን የማያስቀድም ሥልጣን፣ ጥቅም ወይም ሌላ ነገር ተቀባይነት የለውም፡፡ ኢትዮጵያን ከራሳችሁ ሥልጣንና ጥቅማ ጥቅም በታች የምትመለከቱ የበላዮች ፣ የበታቾች፣ ፖለቲከኞች፣ አክቲቪስቶች ወይም ሌላ መጠሪያ ያላችሁ ሁሉ እጃችሁን ከኢትዮጵያ ላይ አንሱ፡፡
ያልተገራ አንደበታችሁን አደብ አስገዙ፡፡ ድብቅ ዓላማችሁ መቼም ቢሆን ይጋለጣልና በከንቱ አትፍጨርጨሩ፡፡ በአደባባይ ኢትዮጵያዬ እያላችሁ ከመጋረጃው ጀርባ የምታሴሩም ሆነ፣ በድፍረት ተሞልታችሁ በግልጽ ኢትዮጵያን ለማፍረስ የምትባዝኑ መቼም አይሳካላችሁም፡፡ ኢትዮጵያ ለዘመናት የገጠሟትን ፈተናዎች እየተሸጋገረች እዚህ የደረሰችው፣ በጀግኖች ልጆቿ ተጋድሎ መሆኑን ታሪክ ይመሰክራል፡፡ ከታሪክ መማር የማይፈልጉ ግን በተደጋጋሚ ቢያደቡም፣ ኢትዮጵያ በልጆቿ ትግል እዚህ ደርሳለች፡፡ በኢትዮጵያ ላይ መዶለት አያዋጣም፡፡ ያዋጣል የሚል ካለም የጊዜ ጉዳይ እንጂ ውርደት ተከናንቦ፣ የታሪክና የመጪው ትውልድ መሳቂያ ይሆናል፡፡
ለኢትዮጵያ መፃኢ ዕጣ ፈንታ አዎንታዊ ሚና ሊኖራቸው የማይችሉና ሰላሟን የሚፈታተኑ በሙሉ፣ ቢቻል ከገቡበት የጥፋት ጎዳና ሊመለሱ ይገባል፡፡ ይህ የማይሆንላቸው ከሆነ ደግሞ አጥፊ እጃቸውን መሰብሰብ አለባቸው፡፡ ይህ ጉዳይ ሲነሳ በመጀመሪያ በፌዴራልም ሆነ በክልል ብሔራዊ መንግሥታት ሥልጣን ይዘው፣ ኃላፊነታቸውን በሚገባ መወጣት ያልቻሉ አመራሮች ራሳቸውን ኦዲት ማድረግ ይኖርባቸዋል፡፡ አገሪቱን በብሔር እየተቧደኑ እንደ ቅርጫ መቀራመት ካሁን በኋላ መቆም አለበት፡፡ በተለይ በገዥው ፓርቲ ኢሕአዴግ አባል ድርጅቶች አመራሮች መካከል የሚስተዋለው፣ ለአገር ክብርና ህልውና ደንታ የማይሰጥ አካሄድ በፍጥነት መቆም አለበት፡፡ ሥልጣን በትምህርት፣ በተመሰከረለት ልምድ፣ ብቃትና ክህሎት መያዝ እንዳለበት ሊታወቅ ይገባል፡፡ ሥልጣን ከአገር ህልውና በላይ ስላልሆነ አደብ መግዛት የግድ ይሆናል፡፡ ሥልጣን በኮታ እየተሸነሸነ የቅራኔ ምንጭ ሆኖ አገር መበጥበጥ የለበትም፡፡ ለሥልጣንና ለሚያስገኘው ጥቅም እየተቧደኑ አገር ላይ መቆመር ሊያበቃ ይገባል፡፡ በአገር ህልውና ቀልድ የለምና፡፡
ለኢትዮጵያ በዚህ ጊዜ የሚያስፈልጋት የሕዝቧ አንድነት ነው፡፡ በአንድነት በመቆም ሰንደቋን ከፍ አድርጎ ወደ ታላቅነት ክብሯ መመለስ፣ የልጆቿ የተቀደሰ ተግባር መሆን ይኖርበታል፡፡ የኢትዮጵያ ወጣቶች ጥራት ያለው ትምህርትና አስተማማኝ ገቢ ያለው ሥራ ያስፈልጋቸዋል፡፡ የሞራልና የሥነ ምግባር ትምህርት በመስጠት አገራቸውን ከልብ እንዲወዱ ማስቻል ተገቢ ነው፡፡ ከሌብነት፣ ከሱስና ከአልባሌ ድርጊቶች ተወግደው ለነፃነት፣ ለእኩልነትና ለፍትሕ ተሟጋች እንዲሆኑ መቀረፅ አለባቸው፡፡ አገር ለማጥፋትና ለማተራመስ የሚያደቡ መሰሪዎች መሣሪያ እንዳይሆኑ፣ ከቤተሰብ ጀምሮ እያንዳንዱ አገሩን የሚወድ ዜጋ ድጋፍ ማድረግ ይጠበቅበታል፡፡ ወጣቶችን ላልተገባ ዓላማ ሊጠቀሙ የሚፈልጉ ኃላፊነት የማይሰማቸው ግለሰቦችና ቡድኖችን፣ በቁርጠኝነት በአንድነት ማስቆም ተገቢ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ወጣቶች ለአገራቸው ህልውና በፅናት መቆም የሚችሉት፣ አገር ወዳድ ኢትዮጵያውያን ከጎናቸው በቁርጠኝነት ሲቆሙ ብቻ ነው፡፡ ኢትዮጵያን ወዳልተፈለገ አቅጣጫ ሊወስዱ የሚፈልጉ ኃይሎችም ሊገቱ የሚችሉት፣ ኢትዮጵያዊያን እንደ ጥንቶቹ አባቶቻቸውና እናቶቻቸው በአንድነት ሲቆሙ ብቻ ነው፡፡
የኢትዮጵያ ሕዝብ ድህነት ከመጠን በላይ ያንገሸገሸው ነው፡፡ ከአሳፋሪውና ከአንገት አስደፊው የመረረ ድህነት ውስጥ ወጥቶ እንደ ሰው መኖር ይገባዋል፡፡ ሕዝቡ የድህነት አረንቋ ውስጥ ተዘፍቆ ወሬ፣ ሐሜት፣ አሉባልታ፣ ጥላቻ፣ ራስ ወዳድነት፣ ራዕይ አልባነት፣ ግጭትና ትርምስ ለኢትዮጵያ ፋይዳ የላቸውም፡፡ ኢትዮጵያ በተለያዩ ጊዜያት አግኝታቸው ያመለጧት ወርቃማ ዕድሎች ያስቆጫሉ፡፡ ከ40 ዓመታት በፊት በነጭና በቀይ ሽብር አንድ ትውልድ አጥታለች፡፡ ከዚያም በኋላ በርካቶች ተገድለዋል፣ ታስረዋል፣ ተሰደዋል፡፡ መንግሥታት በተለዋወጡ ቁጥር ሕዝብ የጠበቃቸው ቀርተው የማይፈልጋቸው ክፉ ነገሮች እየተጫኑበትና ልጆቹ እስር፣ ስደትና ሞት ዕጣ ፈንታቸው ነበር፡፡ ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች ታፍነው ኢትዮጵያዊያን ቁም ስቅላቸውን ዓይተዋል፡፡ ከዚያ አስመራሪ አዙሪት ውስጥ በስንት መከራ መውጣት ቢቻልም፣ አሁንም ትክክለኛውን መንገድ ለመያዝ ባለመፈለጉ ከተስፋ ይልቅ የሥጋት ደመና ያንዣብባል፡፡ አገርን ከሚፈልጉት ሥልጣን በታች የሚያዩ ራስ ወዳዶችና ጀሌዎቻቸው ኢትዮጵያን ለማጥፋት እየዶለቱ ነው፡፡ እነዚህን እኩዮች ተባብሮ ማስቆም የኢትዮጵያዊያን ኃላፊነት ነው፡፡
‹‹የምትለብሰው የላት የምትከናነበው አማራት›› እንደሚባለው፣ በአሁኑ ጊዜ በድህነትና በኋላቀርነት በምትማቅቅ አገር ውስጥ ተማርን ባዮች ማገናዘብ አቅቷቸዋል፡፡ ኢትዮጵያን ከገባችበት ማጥ ውስጥ ለማውጣት መረባረብ ሲያዋጣ፣ የጎሳ አጥር ውስጥ ሆነው በገሃድ የሚቃዡ ምሁራን ተብዬዎች እንደ እንጉዳይ ፈልተዋል፡፡ ኢትዮጵያ እጀግ በጣም ሰፊ ለም መሬት፣ አመቺ የሆነ የአየር ንብረትና ጠንካራ ወጣት የሰው ኃይል ይዛ ትራባለች፡፡ የአፍሪካ የውኃ ማማ ሆና ትጠማለች፡፡ የገዘፈ ታሪክ ባለቤት ሆና የአገሮች ጭራ ናት፡፡ አሁንም በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ሕፃናት ተመጣጣኝ ምግብ ስለማያገኙ ይቀነጭራሉ ወይም ይሞታሉ፡፡ ከድህነት ወለል በታች የሚኖሩ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያዊያን ካሉት በታች፣ ከሞቱት በላይ ሆነው ከአንገፍጋፊ ድህነት ጋር ይኖራሉ፡፡ ሚሊዮኖች መጠለያ አልባ ናቸው፡፡ በከተሞች በሚያሳፍር ሁኔታ የከተማ ነዋሪዎች የትራንስፖርት፣ የውኃ፣ የኤሌክትሪክና የማዘጋጃ ቤት አገልግሎቶችን የሚያገኙት በኋላቀር አሠራሮች ነው፡፡ አዲስ አበባን ጨምሮ ብዙዎች ከተሞች የቆሻሻ መጣያ ናቸው፡፡ የደሃ ደሃ አገር ታቅፎ እንደ ደላቸው አገሮች እዚህ ግቡ በማይባሉ ጉዳዮች በነጋ በጠባ መተራመስ ትዝብት ላይ ይጥላል፡፡ ከመጠን ያለፈ ድህነት ሕዝቡ አናት ላይ እያናጠረ በከንቱ ግብዝ መሆን አያዋጣም፡፡ ለግል ሥልጣንና ጥቅማ ጥቅም ሲባል በአገር ላይ መዶለት ነውር ነው፡፡ ስለዚህ ኢትዮጵያ ላይ አትዶልቱ መባል አለበት!
Filed in: Amharic