>

ጥብቅ ማሳሰቢያ በተለይ ለአማራ ልሂቃንና የነፃነት ታጋዮች (ከትንቢቱ ደረሰ - አዲስ አበባ)

ጥብቅ ማሳሰቢያ በተለይ ለአማራ ልሂቃንና የነፃነት ታጋዮች

ከትንቢቱ ደረሰ  – አዲስ አበባ)

 

አማራን ከተደገሰለት ብሔራዊና ዓለም አቀፋዊ የዘር ማጥፋት ፍጅት ለመታደግ ከልባችሁ የምትንቀሳቀሱ አማሮችና የማንኛውም ጎሣና ነገድ አባላት በሙሉ ይህችን ምክሬን እንድትሰሙኝ እለምናለሁ፡፡ ምክር ከየትም አቅጣጫ ቢመጣ ቆም ብሎ ማድመጥና የሚበጅ ሆኖ ከተገኘ ተቀብሎ ተግባራዊ ማድረግ ከአስተዋይና ብልኅ ሰዎች ይጠበቃል፡፡ መታበይና ሁሉን አውቃለሁ ባይነት ይዋል ይደር እንጂ ጣጣው ብዙ ነው፡፡

በፖለቲካው ዓለም ብዙ ነገሮች በምሥጢር መያዝ አለባቸው፡፡ በምሥጢር ካልተያዙና እንደማንዘርዘሪያ ወንፊት በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ የሚነዙ ከሆነ ከጥቅማቸው ይልቅ ጉዳታቸው ያመዝናል፡፡ ለፕሮፓጋንዳ ፍጆታ ሲባል ከሚሰራጩ አንዳንድ የቅስቀሳ ወሬዎች በስተቀር ወደፊት ስለሚከናወኑ የድርጊት ዕቅዶች አስቀድሞ መናገር አካሄድን ለጠላት አሳልፎ መስጠትና ለሽንፈት መዳረግ ነው፡፡ መረጃ ወርቅ ነው፡፡ መረጃ በአግባቡ ካልተያዘ ለወገን ኪሣራ፣ ለጠላት ደግሞ የድል ወንበር ነው፡፡ አንድ ነገር ከምሥጢርነት ከወጣ መዳረሻው ብዙ ነው፡፡ “አትንገር ብዬ ብነግረው፣ አትንገር ብሎ ነገረው” እንዲሉ የትም አይደርስም ተብሎ የሚተነፈስ ምሥጢር በቅጽበት በጠላት ጎራ ደርሶ ትልቅ አደጋ ሊያስከትል ይችላል፡፡ ለጉራም ይሁን ለሌላ ጉዳይ ዕቅድንና አስፈላጊ መረጃን አውጥቶ መዘክዘክ ተዝቆ የማያልቅ ዕዳን ያስከትላል፡፡ አማራውን ያህል ታላቅ ሕዝብ ለዚህ አሁን ለሚታየው አጠቃላይ ውድቀት የዳረገው አንዱ መንስኤ በቅጡ ያልተያዘ የመረጃ ቋት ነው፡፡

አማራን በታናናሾቹ የጥቃት ዒላማ ውስጥ እንዲገባ ያደረገው ትልቁ ምክንያት የራሱ መዝረክረክና አለመደራጀት እንዲሁም በጎጥና በሸጥ መከፋፈል መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ ወደፊት የሚከናወኑና በዕቅድ የተያዙ ራስን ከጥፋትና ውድመት የመከላከያ ሥልቶች አስቀድመው በጠላት ሠፈር እየታወቁ መሆኑ ልብ ሊባል ይገባል፡፡ በዚህ አሁን በተያዘው መልክ በመጓዝ አማራን ከጭራቆች መንጋጋ ማውጣት አይቻልም፡፡ በዚያ ላይ አዴፓ የተባለ ዥንጉርጉር ቀለም የተላበሰ ጅብ አይሉት ነብር አለ፡፡ ዐፈር ሲሉት ቅጠል፣ ቅጠል ሲሉት ዐፈር እየሆነ አማራን ለሠርጎ ገቦች አሳልፎ የሰጠው ይህ እስፍኒክሳዊ ኃይል በግንቦት ሰባት ቁጥጥር ሥር ከዋለ ወዲህ ደግሞ ይህን መከረኛ ሕዝብ ለሌላኛ ዙር የመከራ ድግስ አስተላልፎት ይገኛል፡፡ ለዚህም ይመስላል አበረ አዳሙ ለተባለ የቀን ጅብ የአማራን የፖሊስ ዕዝ አስረክቦ ሲያበቃ ትልቁን ልጓም ደግሞ አማራን ከናካተው ለካዱ እነአንዳርጋቸው ጽጌን ለመሰሉ እስስቶች ለመስጠት ዳር ዳር እያለ ነው፡፡ አቢይ እስካለ ድረስ ደግሞ ገና ብዙ እናያለን፡፡ ለምሣሌ ጥሩነህ ተመስገን ማን ነው? ተሹዋሚው ሁሉ በግድ ኢንሳ ውስጥ ከአቢይ ጋር የሠራ ወይም ከአቢይ ጋር በክድርና ኢሕአዲግ ተብዬውን የብዔል ዘቡል ድርጅት ያገለገለ መሆን አለበት? ምን ዓይነት ቀልድ ነው? የሚሾመው ሁሉ ለአቢይ ቅን ታዛዥ መሆኑና እርሱ የሚያውቃቸው እንዲሆኑ እንጂ ልምድና ዕድሜ፣ ብቃትና ትምህርት ገደል ገብተዋል፡፡ እኔ እንኳን የማውቃቸው ሀገርን ቀርቶ ቤተሰባቸውን መምራት የሚሣናቸው ሚኒስትሮችና ሌሎች ሹማምንት አሉ – ለጋ ወጣቶች፡፡ በዚያ ላይ በአንዳንድ የሥልጣን ቦታዎች ላይ የሚሾማቸው ሰዎች አማራ እንዳይሆኑ የሚያደርገው ጥንቃቄ እጅግ ያስደንቃል፡፡ ‹በሀገር ይህ ነው እየቀለደ ውርጋጥ›፡፡ ያሳዝናል፡፡ ኢትዮጵያ በአዲስ የሥይጥንና ስም “ሥራሽ ብዙ” ብትባል ያንሳታል፡፡

አምባቸው መኮንን ለምን ሞተ? ብዙ ሞኝ ሰው ይህን ፖለቲካዊ የሒሣብ ቀመር አይረዳም፡፡ ሚዲያው የሚያናፍሰውን ብቻ የሚቀበል ከብት ብዙ ነው፡፡ የአቢይን ውሸታምነት ያልተረዳ ጭፍን አማኝ ሞልቷል፡፡ “አብሽ ልዋጩን አያጣምና” መለስና አቢይ በቅጥፈታቸው የሚያመልካቸው ባያጡ አይገርምም፡፡ በዚያ ላይ ጥቅምም አለ፡፡

ከአምባቸው ገዳይ ጋር ላስተዋውቅህ፡፡ ይሄውልህ – “… ምን እየሠራን እንደሆነ አትጠይቁን፤ ሁሉም ነገር አይነገርም፡፡ ‹ጅብ እስኪነክስ ያነክስ ይባል የለም?› … ስለዚህ ሁሉንም ነገር እንድንነግራችሁ አትጠብቁ….” ይህ አነጋገር በራሱ ሥልጣን ላይ የሚገኝን ተረኛ ጎሣ ይቅርና የወረደውንም ሆነ ለተረኝነት ራሱን እያጨ ያለውን ተስፈኛ ሣይቀር ክፉኛ የሚያስደነግጥ ነው፡፡ ስለዚህ ለነማኪያቬሊ ይህ ዓይነቱ አነጋገር ትልቅ የሥጋት ምንጭ እንደመሆኑ በ“ይህች ባቄላ ካደረች…” ወይም በ“ሳይቃጠል በቅጠል” ሤረኛ የፖለቲካ መርኅ መሠረት በጊዜ የጮኸን ጅብ ማስወገድ ለነገ የሚተው አይደለም፡፡ እናም እነአምባቸውን ያስገደለው ሌላ ሳይሆን የሆድን በሆድ ያለመያዝ ችግር ነው፡፡

የነአያ ጅቦን ታሪክ ላስታውስህ – ለፈገግታ ያህል፡፡ አንዲት አህያና ውርንጭላዋ በአያ ጅቦ የአትክልት ሥፍራ ሣር ይግጣሉ፡፡ ውርንጪት ጠገበች፡፡ “እማየ፣ አንዴ ፍቀጂልኝና ላናፋ!” ብላ እናቷን ትጠይቃለች፡፡ እናትም “አየ ልጄ! የት እንዳለን አታውቂምን? በይ እረፊ ይቅርብሽ” ትላታለች፡፡ ልጅት ግን ቀበጥ ነበረችና አንዴ አናፋች፡፡ እናት ደነገጠች፡፡ ጨሌ መጋጣቸውን ቀጠሉ፡፡ ትንሽ ቆየችና ልጂት “እማየ አሁንም ማናፋት አማረኝ፣ አንዴ ብቻ ልጩህ እማይዬ”፡፡ እናት ተቆጣች፡፡ “ምን ሆነሻል! የቅድሙ መጥሪያ፣ የአሁኑ መበያ ይሆናል” ብላ አስጠነቀቀቻት፡፡ ልጂት ግን አላስቻላትም፡፡ አንዴ ለቀቀችው፡፡ በፊተኛው ጩኸት የአህዮችን በአካባቢው መኖር ተረድቶ አቅጣጫው ግን ጠፍቶት የነበረው ጅብ በሁለተኛው ጩኸት አህዮቹ ያሉበትን ሥፍራ ለዬና ደርሶ እናትና ልጅን ገነጣጠላቸው፡፡ መጮህ “እዚህ አለሁ፤ ናና ብላኝ” ማለት መሆኑን ልብ ይሏል፡፡

አሣምነውን ማን አስገደለው? እርሱንም ያስገደለው – ሽፋኑ የፈለገውን ይሁን – ለአማራ ሕዝብ ቀጥ ብሎ እንደጅብራ መቆሙ ነው፡፡ አማራ እንደጦር የሚፈራ ሕዝብ መሆኑ በየጠላቶቹ አንደበትና በየማኒፌስቷቸው መረዳት አይከብድም፡፡ ለዚህም ነው ጅቦች እየተፈራረቁ ከምድረ ገጽ ሊያጠፉት እየሞከሩ ያሉት፡፡
የግዕዙ ብሂል “አፍ ይጸውዖ ለሞት” ብሎ ቀድሞ አስቀምጦታል፡፡ አፍ/አንደበት በአግባቡ ከተጠቀሙበት መልካም የመሆኑን ያህል ካልተጠነቀቁለት እጅግ መጥፎ ነው፤ አፍ በደግ ጎኑ ከተጠቀሙበት ከሰገባው የወጣን ሠይፍ ወደ ማኅደሩ ይመልሳል፡፡ እያንዳንዱ ሰው ሲናገር አስቦ ቢሆን ብዙ ውድመትን መከላከል በተቻለ፡፡ ይህ ግን እውን ሲሆን የሚታየው ከስንት አንዴ ነው፤ በተለይ በዚህ ዘመን አንደበተ ርቱዕና አስታራቂ ሰው ለማግኘት እየተቸገርን ነው፡፡ ተሳስቶ የሚያሳስተው ብዙ ነው፡፡ ከልጅነቴ የማውቀው አንድ ቋሚ እውነት አለ፡፡ ያም በቀላሉ ልናልፋቸው የምንችላቸውን ነገሮች በግልፍተኝነት አልባሌ ነገር በመናገራችን ትልቅ ጉዳት የሚደርስብን መሆናችን ነው – በዚህም ሆነ በዚያኛው ወገን፡፡ እኔ በራሴ ባለኝ ነገርን አዙሮ የማየት ልማድም በሉት የፈሪነት ጠባይ አንድ ጊዜ የደረሰብኝና መቼም የማልረሳው ነገር አለ – እንዲያውም ሁለት ናቸው፡፡ አንደኛው እንዲህ ነው፡- በወጣትነት ዘመኔ አንድ ሰካራም ወጣት አንዲት ሴት በጠራራ ፀሐይና በሰዎች ፊት ሲያንገላታት ተመልክቼ መሣሪያ ላወጣ ስል “እንትህን አትመታበትም” ቢለኝ መሣሪያየን ሳላወጣ በሌላ መልክ ጠቡ እንዲበርድ አደረግሁ – ለአብነት መጥቀሴ እንጂ በሌላ እንዳትተረጉሙብኝ አደራ፡፡ የንዴት ሰለባ ብሆን ኖሮ ልጁ ይሞታል እኔም እታሰራለሁ፡፡ ይህ በማኅበራዊ ሕይወታችን ዙሪያ የሚታይና ብዙዎች የምንጠፋፋበነት ግን በቀላሉ ልናልፈው የምንችለው ክስተት ነው፡፡ “አፍ እላፊ ያስከትላል ጥፊ”ም ይባላል፡፡

ከፍ ሲል ባስቀመጥኩት እሳቤ ትንሽ እንጓዝ፡፡ ሁጎ ሻቬዝን ማን ገደለው? ጋዳፊን ማን ገደለው? ሣዳም ሁሴንን ማን ገደለው? ቢን ላደንን ማን ገደለው? መለስን ማን ገደለው? መንግሥቱን ከሥልጣን ማን አስወገደው? ኢንጂኔር ቅጣው እጅጉን ማን ገደለው? እነዚህና ሌሎችም ግድያዎች ከመረረ የጥላቻና የጀብድ ንግግር ጋር የተያያዙ ናቸው፡፡ …

“በለፈለፉ በአፍ ይጠፉ”፡፡ “የምላስ ወለምታ በቅቤ አይታሽም”፡፡ እውነት ነው፡፡ ጠቀሙም አልጠቀሙም፣ ተግባራዊ ሆኑም አልሆኑም በሆድ መያዝ ያለባቸው አንዳንድ ዕቅዶችና ፍላጎቶች ከአፍ ከወጡ አፋፍ ናቸው፡፡ ወገንን ያስደሰትክ መስሎህ ገሃድ የምታወጣቸው አንዳንድ መረጃዎች በጠላቶችህ ዘንድ አይናቁም፡፡ መረጃ በመሠረቱ አይናቅም፤ አይካበድምም፡፡ በጠላት ዘንድ እያንዳንዷ እንቅስቃሴህ እየተፈታች እየተገጠመች ትተነተንና እንዴት እንደሚያጠቁህ ትልቅ ግብኣት ትሆናቸዋለች፡፡ አሰለጡና ጮሌው አቢይ ወደ ሥልጣን ከመጣ እንኳን አማራው እንደምን ወገቡን እንደተመታ የምናውቀው ነው፡፡ የራሱን ዘንዶ ጃዋርን እያወፈረና እያጠበደለ የአማራን ኮስማና አክቲቪስቶችና ከእስክርቢቶ ሌላ መሣሪያ የሌላቸውን የመብት ተከራካሪዎች አሥሮ እንዴት እያሰቃየ እንዳለ የአደባባይ ምሥጢር ነው፡፡ ግን የጌታየን አነጋገር ልዋስና “እውነት እውነት እላችኋለሁ” አቢይ የመጨረሻው ዘመን ‹ኢትዮጵያዊ› ኮብራ ነው፡፡ ከዚህ በኋላ ሀገራችን በእባብ አትነደፍም፡፡ ሕዝብ ይፈጠራል፤ ሀገርም ትፈጠራለች፡፡ ይቅርታ ይደረግልኝና አሁን አኀዛዊ እንጂ ጥራቱን የጠበቀ ሕዝብ አለ(ን) ማለት ያስቸግራል፡፡ ሀገር ግን በግልጽ የለችም፡፡ ማንም የሚፈነጭባት የጨረባ ተዝካር የሆነች ሀገር መኖሯ ሀገር እንዳለን አያመለከትም፡፡ ሙስናው ከጫፍ ጫፍ ነው፡፡ ድንቁርናው ከጫፍ ጫፍ ነው፡፡ የውሸት ዲግሪው ከጫፍ ጫፍ ነው፡፡ በሀሰት ዲግሪዎች የተምበሸበሹ ደናቁርት ሀገር “እያስተዳደሩ” ትክክለኛ ሀገርና ሕዝብ አለን ማለት አንችልም፡፡ በቁማችን ጠፍናል፡፡ እንደጠፋን ግን አንቀርም፡፡

ለማንኛውም የአህያ ጆሮ በሆድ እንደሚያዝ ሁሉ ምሥጢራችንን እየጠበቅን በመጓዝ ከሐሣዩ መሢሕ አቢይ አህመድ አሊ ግልጽና ሥውር አፈናና ከወያኔ ዕልቂት የተረፍን ኢትዮጵያውያን ፈጣሪ ከሚልክልን ሣተና ልጆች ጋር ተባብረን ይህን የአጋንንት መንጋ ቆራርጠን ወደ ሲዖል ለመላክ መትጋት ይኖርብናል፡፡ ቀኑ ስላልደረሰ እንጂ ብዙ ወገኖች በየሥፍራው የጌታን ጥሪ በመጠባበቅ ላይ እንደሚገኙ መገመት አያስቸግርም፡፡ ከእያንዳንዱ ድቅድቅ ጨለማ በስተጀርባ ፍንትው ያለ ብርሃን መኖሩን አንረሳም፡፡ ቸር ይግጠመን፡፡ ተስፋችን እግዚአብሔር እንጂ በዳቦና በእንጀራ መልኩን እንደ እስስት የሚለዋውጥ በዘረኝት ልክፍት የተመረዘ ፖለቲከኛ አይደለም፡፡ ሁሉን እንድናይ የፈጣሪ ፈቃድ ሆነ፡፡ ለሆነውም ለሚሆነውም ይመስገነው፡፡

Filed in: Amharic