>

የ«አያቶላህ»  ጃዋር መሐመድ  ቴሌቭዥን የማይዘግባቸው የኦሮሞ ግድያዎች !!! (አቻምየለህ ታምሩ)

የ«አያቶላህ»  ጃዋር መሐመድ  ቴሌቭዥን የማይዘግባቸው የኦሮሞ ግድያዎች !!!

አቻምየለህ ታምሩ
የ«አያቶላህ» ጃዋር ቴሌቭዥን ከወር በፊት በወልድያ ዩኒቨርሲቲ ተገደሉ የተባሉ የኦሮሞ ተማሪዎች  ጉዳይ  እስካሁን ድረስ በዜና እወጃ ሳይቀር  ያስተጋባዋል፤ የብዙ ኦነጋውያን ዶክተሮችና ፕሮፌሰሮች የትንታኔ አጀንዳ አድርጎ እያስተነተነበት ይገኛል።
በዳግማዊ ምኒልክ ዘመን ተገደሉ ለሚላቸው ኦሮሞዎች ስም ሳይቀር  እየሰጠ ያልኖረበትን ዘመን የትርክት ግድያ ሲዘግብ የሚውለው የጃዋር ቴሌቭዥን፤   ወልድያ ዩኒቨርሲቲ ተገደሉ ስለተባሉት የኦሮሞ ተማሪዎች እስካሁን ድረስ ሽፋን እየሰጠ ያለው ኦ.ኤም.ኤን፤ አፍንጫው ስር፣ ዐይኑ እያየ  በዚህ ወር ብቻ  ቁጥራቸው ቢያንስ ስድስት የሚሆን የኦሮሞ ባለሥልጣናትን ግድያ በሚመለከት ግን ትንፍሽ እንኳ አላለም።
«ምዕራብ ኦሮምያ» በሚባለው ዞን ኦነግ እያካሄደው ያለው የኦሮሞ ባለሥልጣናት ግድያ አማራ ክልል በሚባለው ቢሆን ኖሮ  ሰበር ዜና ለመስራት የጃዋርን  ቴሌቭዥን  የሚቀድለው አልነበረም።
የጃዋር ቴሌቭዥን ብቻ ሳይሆን  «በወልድያ የኦሮሞ ተማሪዎች ተገደሉ»  ብሎ  ሳይውል ሳያድር የውግዘት መግለጫ ያወጣው ኦቦ ሺመልስ አብዲሳም እሱ የሾማቸው ባላሥልጣናት  በሚገዛቅ ክልል ውስጥ በኦነግ ሲረሸኑ ስላንዳቸውም እንኳ ግድያውን የሚያወግዝ መግለጫ አላወጣም።
ለነ ሺመልስና ጃዋር በኦነግ የሚገደል የኦሮሞ ባለሥልጣን በግፍ እንደተገደለ አይቆጠርም፤ ወይም  ነፍሱን  የድመት ነፍስ  አድርገው ይቆጥሯታል። ምንም ይሁን ምን ለነ ጃዋር በኦነግ የሚረሸኑ ኦሮሞዎች ነፍስ ወልድያ ተገደሉ ከተባሉ የኦሮሞ ተማሪዎች ነፍስ ያነሰ ነው።
ጃዋርና ሺመልስ ብቻ ሳይሆኑ አንድም የኦሮሞ ብሔርተኛ  በኦነግ የሚገደሉትን የኦሮሞ ባለሥልጣናት ነፍስ ጉዳይ ጉዳይ ብሎ  ሲያዝንና ኦነግ የሚፈጽመውን የሽብር ድርጊት ሲያወግዝ አላየሁም። በባሕር ዳሩ ግድያ  ከአማራ በላይ እየየ ያሉት እነ ጃዋርና ሺመልስ ነበሩ። አሳምነው ጽጌን ለማውገዝና በመገደሉ ጉዳዩ በቀጥታ ከሚመለከተው ከአማራው በላይ የተደሰቱት የኦሮሞ ብሔርተኞች ናቸው። ሆኖም ግን ባሕር ዳር ከተገደሉ «የአማራ ክልል ባለሥልጣናት» ቁጥር  በእጥፍ የሚበልጡ የኦሮሞ ባለሥልጣናት ምዕራብ ኦሮምያ በሚባለው አካባቢ በኦነግ ሲገደሉ መገደላቸውን እንኳ በዜና መልክ አላስነገሩላቸውም።
በመካከላቸው ችግር በተፈጠረ ቁጥር  ለኛ አጀንዳ  እየሰጡ  ስለ ባሕር ዳሩ ግድያ መግለጫ ሲሰጡና  የምርመራ ውጤት የሚሉትን እያቀረቡ  በሚገዙት ጊዜና በሚያገኙት ትንፋሽ  ይዞታቸውን ሲያጠናክሩ የሚውሉት እነ ጃዋር፣ ሺመልስ፣ ዐቢይና ለማ  ባሕር ዳር ከተገደሉት ሹሞት በቁጥር በእጥፍ የሚበልጡ የኦሮሞ ባለሥልጣናት በኦነግ ሲገደሉ ግን ወልድያ ዩኒቨርሲቲ ተገደሉ ለተባሉት የኦሮሞ ተማሪዎች  የሰጡትን ያህል መግለጫ መስጠት ቀርቶ በሚቆጣጠሯቸው ሚዲያዎች እንኳ  በጋዜጠኛ መገደላቸውን እንዲዘገብ የማይፈቅዱት የዛሬዎቹ የኦሮሞ መኳንንት ቤታቸው ድስት ሳይጥዱ ከሰው ቤት ሲሆን ግን ጋን ይጥዳሉ።
ለማንኛውም የጃዋር ቴሌቭዥንና የነሺመልስ አብዲሳ ልሳኖች የማይዘግቧቸው በኦነግ የተገደሉ የኦሮሞ ባለሥልጣናት ስምና የሥራ ኃላጊነት የሚከተለውን ይመስላል፤
በኅዳር ወር  2012 ዓ.ም የተገደሉ
1. አቶ ረጋኔ ከበበ  [በምዕራብ “ኦሮሚያ” የጀልዱ ወረዳ ምክትል አስተዳዳሪ ]
2. አቶ ተስፋዬ ገረመው [ በምዕራብ “ኦሮምያ” የጎጆ ከተማ  የፖለቲካ ዘረፍ ኃላፊ]
3. ኮማንደር ጫላ ደጋጋ [ የነቀምቴ ከተማ ፖሊስ የወንጀል ምርመራ ኃላፊ]
4. አቶ ቶላ ገዳ  [ “የኦሮሚያ” ክልል መስተዳደር የመንገዶች ባለስልጣን ኮምዩኒኬሽን ኃላፊ]
5. አንድ ስሙን ለጊዜው ያላጣራሁት የምዕራብ ሸዋ ዞን ባለስልጣን፣
6. ሌላ ስሙን ያላረጋገግጥሁት የምዕራብ ሸዋ ዞን ባለስልጣን፣
በጥቅምት ወር 2012 ዓ.ም.  የተገደለ
7. አቶ ገመቺስ ደስታ [የኢትዮ ቴሌኮም የምዕራብ ዞን ኃላፊ]
በመስከረም 2012 ዓ.ም የተገደልለ
8. አቶ አበበ ተካልኝ  [የጉሊሶ ከተማ ከንቲባ ]
በግንቦት 2011 ዓ.ም.
9. ስሙ ለጊዜው ይፋ ያልሆነና ከአርሲ ወደ ወለጋ ለወረዳ አስተዳድርነት ተመድቦ  በመጓዝ ላይ ሳለ ኦነግ  መንገድ ላይ አስቁሞ መጀመሪያ ምላሱን ቆረጡት፤ ከዚያ አይኑን አወጡት ከዚያ እጁን ቆረጡት፤ በመጨረሻ ሊያቃጥሉት ሲሉ ልዩ ኃይል ደረሶ ከመቃጠል አድኖት ሆስፒታል ውስጥ ይገኛል።
በሰኔ 2011 ዓ.ም በጥይት የተደበደበ
10. አቶ ታደለ ገመቹ  [የደምቢዶሎ ከተማ ከንቲባ፤  በጥይት ተመትቶ  ሆስፒታል ውስጥ የሚገኝ]
በመጋቢት 2011 ዓ.ም.  የተገደሉ፤
11. በምዕራብ ወለጋ ዞን ነጆ ወረዳ ሁምነ ዋቀዮ በተባለ ቀበሌ ሦስት ኢትዮጵያውያን፣ አንድ ጃፓናዊ እና አንድ የሕንድ ዜግነት ያላቸው ሰንራይዝ ለሚባል የማዕድን አውጪ ተቋም ይሰሩ የነበሩ ሰዎች ተገድለዋል
ታኅሳስ 2011 ዓ.ም
12. ሁለት የፌደራል ፖሊስ አባላት  ሆሮ ጉዱሩ ወለጋ ዞን ውስጥ መነ ቤኛ ተብሎ በሚጠራ ስፍራ ላይ በጥይት ተመተው ተገድለዋል።
ባጭሩ ባለፈው አንድ አመት ውስጥ በምዕራብ ኦሮሚያ በሚባለው አካባቢ 8 የአከባቢው ባለስልጣናት ሲገደሉ በምዕራብ ሸዋ ደግሞ ቢያንስ ስድስት ባለሥልጣናት ተገድለዋል።  ይህ ሁሉ የኦሮሞ ባለሥልጣን ግድያ  በኦነግ  ሲካሄድ ያልኖሩበትን ዘመን በዳግማዊ ምኒልክ  ተገደሉ ስለሚሏቸው የማያውቋቸው ኦሮሞዎች  ተስፋዬ ገብረ አብን ስም እያስወጡ  የትርክት ግድያ እየፈጠሩ  ዜና ሲዘግቡና ዶክመንተሪ ሲያቀርቡ  የሚውሉት እነ ጃዋር  አይናቸው እያየ አፍንጫቸው ስር የሚያውቋቸው ኦሮሞዎች በኦነግ ሲገደሉ ግን የአንዱንም ሞት ዘግበውት አያውቅም!
Filed in: Amharic