>

የዝች አገር መንግስትማ ከሁለትም በላይ ነው! (መስከረም አበራ)

የዝች አገር መንግስትማ ከሁለትም በላይ ነው!

መስከረም አበራ
 
* ለዚህ ሁሉ ሰቆቃ የነ በቀለ ገርባ የአደባባይ ድንፋታ፣የነ ሊበንዋቆ ድፍድፍ የጥላቻ ሰበካ፣ የጃዋር መሃመድ “Ethiopia out from Oromoiya” መፈክር፣የፀጋዬ አራርሳ የጥላቻ እብደት፣የለማ መገርሳ “የህዝቤ ጥያቄ ተጠለፈ” ቁጭት፣የሽመልስ አብዲሳ “ስበር በለው”ንግግር…. ሁሉ አስተዋፅኦ አለው!
—-
የታገቱ ተማሪዎችን ለማስለቀቅ የሃገሪቱ መንግስት በበቂ ሁኔታ እየሰራ እንዳልሆነይሰማኝ ነበር።  አቶ ላቀ አየለ የተባሉ የአማራ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድርም ይህንኑ ሃሳቤን ቃል በቃል ደግመውታል ቢቢሲ አማርኛ እንደዘገበው።ከልብ ያለቀሰ መንግስት እንኳን ከጀማሪ ሸማቂ  ቀርቶ አሜሪካን ሳይቀር ብርክ ከሚያስይዘው ከዝነኛው አለማቀፍ አሸባሪ ቦኮሃራም እንኳን ዜጎቹን አስለቅቋል።
ልጅ የወለደ ሰው፣ከሴት የተፈጠረ ሰው መንግስት ሲሆን፣ፖለቲከኛ ነኝ ሲል ከሰው የሚያዋስነው ባህሪ ለምን እንደሚርቀው ሳስብ  በጣም ያሳዝነኛልም ይገርመኛልም!
 ቢቢሲ በዘገባው የጃል መሮ ኦነግ ልጆቹን እንዳላገተ እንደተናገረ ዘግቧል። ሸማቂዎች እንዲህ ያለውን ነገር “ለአቴንሽን” ማግኛነት ስለሚፈልጉት ጃል መሮ ቢያግት  ኖሮ አግቻለሁ እንደሚል አስባለሁ።
 ጃል መሮ ሃላፊነቱን ካልወሰደ ልጆቹን በማገቱ ሊጠረጠር የሚችለው ሌላ ቡድን የጃዋርን እግር ተከትሎ የተመሰረተው “አባ ቶርቤ” የተባለው ገዳይ ቡድን ሊሆን ይችላል። ይህ ቡድን የአሜሪካ ፓስፖርት ባለው ትውልደ ኢትዮጵያዊ እንደተመሰረተ እና እንደሚመራ በአንድወቅት የጃዋር አጋር የነበረው አቶ ገረሱቱፋ ከትቂት ወራት በፊት የተናገረበትን ዘገባ እንዳነበብኩ አስታውሳለሁ።
 ይህ አባ ቶርቤ የተባለው ቡድን በአክራሪነቱ ከኦነግ የባሰ በመሆኑ የክረቱ መድረሻም መነሻም የአማራ ጥላቻ መሆኑን፣ ልጆቹ ደግሞ አማራ መሆናቸውን ሳስብ በልጆቹ ላይ የሚደርሰውን ሰቆቃ እገምታለሁና እጅግ የሚቀፍ ስሜት ይሰማኛል!!!!
 ለዚህ ሁሉ ሰቆቃ የነ በቀለ ገርባ የአደባባይ ድንፋታ፣የነ ሊበንዋቆ ድፍድፍ የጥላቻ ሰበካ፣ የጃዋር መሃመድ “Ethiopia out from Oromoiya” መፈክር፣የፀጋዬ አራርሳ የጥላቻ እብደት፣የለማ መገርሳ “የህዝቤ ጥያቄ ተጠለፈ” ቁጭት፣የሽመልስ አብዲሳ “ስበር በለው”ንግግር…. ሁሉ አስተዋፅኦ አለው!
 ከሁሉም በላይ ግን አስተዋፅኦ የሚያደርገው የመንግስቱን ግማሽ  ለሸማቂ አስረክቦ “እዛ መሄድማ እኔንም ያስፈራኛል” እያለ  ኢትዮጵያን እንደሚያስተዳድር የሚሰማው የዶ/ር አብይ አስተዳደር ነው። “እኔ የሰፈር ሚሊሻ አይደለሁም” የሚሉት አብይ ምን እየሸሹ እንደሆነ ግልፅ ነው። የሰፈር ሚሊሻ ባይሆኑም ጠንካራ የሰፈር ሚሊሻ እንዲኖር የማድረግ ግዴታ እንዳለባቸው መንገር ያስፈልግ ይሆን?
 ለራሱም እየፈራ እንደሆነ ሲናገር የማያፍረው የአብይ አስተዳደር   ቀስ በቀስ አንድ ሰሞን ሞቃድሾ ኮሽ ሲል ወደ  አንጋሹ  መለስ ቤተ-መንግስት እያለከለከ የሚሮጠውን የሱማሌ መንግስት እንዳይሆን ስጋት አለኝ።ለዛውም የሚሮጥበት ከተገኘ ነው!
 ይህ አስተዳደር  የሚያስተዳድረው ከጃል መሮ፣ ከአባቶርቤ፣ከህወሃት፣ ከጃ-war እና ቄሮዎቹ የተረፈውን ሃገር ነው። ሁለት መንግስት አለ ሲባል የገረመን ለዛውም  አሳንሶ የነገረንን ነው ለካ!
Filed in: Amharic