>

የሕወሓቱ ጆሴፍ ጎብልስ፤ የኢሕአፓው አንበርብርና የሻዕብያው በረከት  ሰምዖን!!! (አቻምየለህ ታምሩ)

የሕወሓቱ ጆሴፍ ጎብልስ፤ የኢሕአፓው አንበርብርና የሻዕብያው በረከት  ሰምዖን!!!

አቻምየለህ ታምሩ
ዘመኑ  በኢትዮጵያ አቆጣጠር በ1973 ዓ.ም. ነው። ኢትዮጵያን ለማፍረስ  የተነሱ ባዕዳን ኃይሎች  ቀዳሚ ሀገር በቀል ወኪል  የሆነው ኢሕአፓ በሻዕብያ መሪነት ከወያኔ  ጋር  መረብን ተሻግሮ  አሲምባ ከመሸገ በኋላ በወያኔ  ተመትቶ   ከትግራይ እንደለቀቀ  የከተማ የትጥቅ ትግሉም ሳይሳካለት ቀርቶ እንደገና ጫካ  በመግባት  የትጥቅ ትግሉን ለመቀጠል የተከዘ ማዶዎቹ እነ ቢንያም አዳነ ኢሕአሰ [የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ሰራዊት] በሚል ስያሜ የመሰረቱትን  ወታደራዊ ክንፍ ይዞ  በድጋሚ አሲምባ ቢከትም፤በጫካ ትግሉ ብዙም ሳይገፋ  ድርጅቱ በውስጥ ክፍፍል መታመስ ጀመረ።
ድርጅቱ የተተራመሰው አፈ ጮሌ የድርጅቱ ታጋዮች ከድርጅቱ መርህ ውጭ የሆነ ጽሁፍ በመበተናቸው ነው ተብሎ አራት ፋኖዎች ለጊዜው በቁጥጥር ስር ዋሉ። የነዚህ አራት ፋኖ ጽሁፍ በታኞች ቡድን አስተባባሪ በበረሀ ስሙ «አንበርብር» እየተባለ ይታወቅ የነበረው የመረብ ማዶው ሰው  የድርጅቱ አስኳድ ነበር። «አንበርብር» ከኢሕአፓ ስነስርዓት ውጪ ድርጅቱን የሚጎዳ ጽሁፍ የበተነው ከወያኔና ከሻብያ በተሰጠው ድርጅቱን የማፍረስ ተልዕኮ እንደሆነ የትግል አጋር ፋኖዎቹ ይናገራሉ። በመጨረሻም የአንበርብር ቡድን ከህዳር 7 ቀን እስከ ህዳር አስራ አንድ ቀን 1973 ዓመተ ምህረት በትግራይ ውስጥ በተምቤን አውራጃ አምበራ ወረዳ ሽልም እምኒ ቀበሌ ተክራርዋ በተባለች መንደር ከኢሕአፓ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ የአፈነገጡ ተጨማሪ ፋኖዎችን በመያዝ ቀደም ብሎ ወያኔ ወዳዘጋጀላቸው ቦታ ተወስደው በወያኔና ሻዕብያ  አጋፋሪነት «ጉባኤ» ዘርግተው አዲስ ፓርቲ ለመመስረት «መከሩ»።
በነአንበርበር ስብሰባ ላይ የነበሩ የወያኔ  ሰዎች እነአንበርብርን በነፍስ አባታቸው በሻዕብያ  ሕግ መሰረት አግባብተው በስብሰባው መጨረሻ በህዳር 11 ቀን 1973 ዓመተ ምህረት ከኢሕአፓ አፈንግጦ የወጣውን የነአንበርብርን  ቡድን በሕወሓት አዋላጀት የኢትዮጵያ ሕዝቦች ዲሞክራሲያዊ ንቅናቄ [ኢሕዴን] የሚባል ፓርቲ ተመሰረተ። ሕወሓት ከኢሕአፓ የውስጥ ደንብ ውጭ ኢሕአፓን የሚያፈርስ ጽሁፍ እንዲጽፍና እንዲያሰራጭ በኋላም በሕወሓት ፕሮግራም ኢሕዴንን እንዲቋቋም በማድረግ ትልቅ ሚና የነበረውና «ድርጅቴን አዳክሞ አባላቶቼን አስከዳብኝ» ብሎ በወቅቱ ኢሕአፓ መጀመሪያ ያሰረውና  ከእስር ካመለጠ በኋላ በይፋ ያወገዘው ከሀዲው ግለሰብ፤ በበረሀ  ስሙ አንበርብር ተብሎ ሲታወቅ የኖረው  የወያኔና የሻዕብያ ተላላኪ  ዛሬ በሚንስትር የማዕረግ ስሙ በረከት ስምዖን ተብሎ የሚጠራው ግለሰብ ነው።
ኢሕዴን እዚያው ትግራይ ውስጥ የሕወሓት «የጡት ልጅ» ሆኖ እንደተመሰረተ ለነአንበርብር ቡድን በመጀመሪያ ወታደራዊ ስልጠና የሰጣቸው የወያኔው የቀድሞው  የመከላከያ ሚንስትር የነበረው ስዬ አብርሀ ነበር። የስዬን ስልጠና እንደጨረሱ ኢሕዴኖች መሳሪያ ታደላቸውና ወያኔ «በአማራ አገር» በሚለው ምድር  ለሚደረገው የሕወሓት ትግል በመንገድ መሪነትና በአማርኛ አስተርጓሚነት ተመደቡ።
ኢሕዴን ከተመሰረተ ዘጠኝ አመት ከአምስት ወር ሲሆነው ወያኔ ኢሕዴንን አማርኛ እያስተረጎመ ጎጃምና ጎንደር፤ ወሎና ሸዋን  ተሻግሮ አዲስ አበባ ገባ። ወያኔ አዲስ አበባ እንደገባ የዐማራ ጥላቻ የወለደው ኦነግ የሚባለው ድርጀት የወያኔ የሽግግር መንግሥት  አካል ሆኖ ያገኘውን ስልጣን በመጠቀም በወለጋ፣ በአርሲ፣ በሐረርጌ፣ በባሌና በሎሎች  ከተሞች ሁሉ ለዘመናት አገር ሰላም ብለው ይኖሩ የነበሩ ዐማሮችን ያለርህራሄ ማረድና መጨፍጨፍ ጀመረ። ዐማራው በያለበት ደሙ ደመ-ከልብ መሆኑ እንቅልፍ ያሳጣቸው እጀ መድሐኒቱ ሐኪም ፕሮፌሰር አስራት ወልደየስ በየተገኘበት ይታረድ የነበረውን የዐማራ ሕይወት ለመታደግ «መአሕድ» [የመላው አማራ ሕዝብ ድርጀት] የሚባል ሕይወት አድን ድርጅት አቋቋሙ።
መአሕድ እንደተቋቋመ ባጭር ጊዜ ውስጥ እልፍ አእላፍ አባላትና ደጋፊዎችን ከጎኑ አሰለፈ። በኢትዮጵያ ሕዝብ ባጠቃላይና በተለይም በዐማራው ዘንድ የመአሕድ ተሰሚነትና የፕሮፌሰር አስራት ቅቡልነት እንቅልፍ የነሳው ወያኔ ኢሕአዴግ ውስጥ በዐማራ ስም የሚጠራ ድርጅት ስለሌለው [የኢሕአዴግ አካል የሆነው የነ አንበርብሩ ኢሕዴን የስም ሕብረ ብሔራዊ ድርጅት እንደነበር ልብ ይሏል] መአሕድ ዐማራውን ከጎኑ አሰልፎ ሳይጨርሰው ከመአሕድ የዐማራውን ውክልና ለመጫረት ሲባል የስም ሕብረ ብሔራዊው ድርጀት የነበረውን  ኢሕዴን ወደ ብሄረ አማራ ዲሞክራሲያዊ ንቅናቄ [ብአዴን] ተለውጦ የፕሮፌሰሩን መአሕድ እንዲውጥ ትዕዛዝ ሰጠ።
ኢሕዴኖች እነ አንበርብርም እነ አባዱላን፣ እነ ካሱ ኢላላን ይዞ ከነበረው ከሕብረ ብሔራዊው  ኢሕዴን ወደ ብአዴን እንዲያንሱ የተሰጣቸውን የወያኔ ትዕዛዝ ሰጥ ለጥ ብለው በመስገድ በይሁንታ አስተናግደው የሕብረ-ብሔራዊውን የኢሕዴን ድርጅት የፖለቲካ ፕሮግራም ሳይቀይሩ «ወደ ብሔረሰብ ድርጅትነት» ተለወጡ። በ1973 ዓ.ም. ኢሕአፓን ከድቶ ለወያኔ ያደረው ኢሕዴን በ1985 ዓ.ም. ደግሞ ራሱን ኢሕዴንን ከድቶ ብአዴን ሆነ። ዛሬ «ብአዴን ነን» ከሚሉን የድርጅቱ እንደራሴዎች ይልቅ የብአዴንን እውነተኛ ታሪክ ከስር መሰረቱና  ለምን አላማ ድርጅቱ እንደመሰረተው የሚያውቁት ድርጅቱን የመሰረቱት  ወያኔና ሻዕብያ  ብቻ ናቸው። ይህንን ለማየት ድርጅቱን ወያኔ እየሾማቸው ይመሩት የነበሩት ሰዎች ስለብአዴን የተናገሩትን መውሰድ በቂ ነው።
ለምሳሌ ኢሕዴን ወደ ብአዴን ከመቀየሩ በፊት የነእያሱ አለማየሁ  ኢሕአፓ «ለወያኔ ያደሩ ከዳተኞች» ብሎ ክስ  ባቀረበባቸው  ሰዓት  የወቅቱ የደርጅቱ መሪ የነበረው  የዛሬው ፓስተር ታምራት ላይኔ ኢሕአፓ በኢሕዴን ላይ ላቀረበው ነቀፌታ  በድርጅቱ ልሳን በማለዳ መጽሔት አስተያየት  ሲሰጥ  «እኛ ከኢሕአፓ ተለይተን የወጣን ትክክለኛ ኢሕአፓዎች ነን» ብሎ ነበር። ይህ የፓስተር ታምራት አባባል ተስፋየ መኮንን «ይድረስ ለባለታሪኩ» በሚለው መጽሐፉ  ከፋጸው ታሪክ አኳያ ውሃ የሚቋጥር ነው።  በተስፋየ  መኮነን ትንተና የነ አንበርብር ኢሕአፓ ከብርሀነመስቀል ረዳ  ኢሕአፓ የቀጠለ  ይመስላል።
በሌላ ጊዜ ደግሞ ሌላው የኢሕዴን ታጋይ ነኝ የሚለውና  የድርጅት መሪ የነበው  አዲሱ ለገሠ የኢሕዴንን ምስረታ  በዓል ሲያከብር ድርጅቱ  ለዐማራ ሕዝብ መብት ለመታገል  የተፈጠረ መሆኑን  ተናግሮ  ነበር። ልብ በሉ ድርጅቱኮ የተመሰረተው ሕብረ ብሔራዊ ድርጅት ሆኖ ነው።  አሁን  ለድርጅቱ መሪነት የተወከለው ደመቀ መኮነንም  ቢጠየቅ  ሌላ እንደሚመልስ እርግጠኛ ነኝ። ለዚያ ነው ስለድርጅቱ አለማ ኢሕዴን ወይም ብአዴን ነን ከሚሉ ሰዎች በላይ ድርጅቱን ለምን አላማ እንደተቋቋመ የሚያውቁት ፈጣሪዎቹ ወያኔና ሻዕብያ ብቻ ናቸው ያልሁት። የሆነው ሆኖ  ኢሕዴን/ብአዴን ይህን ሁሉ የክህደት ውል ለወያኔ እየፈረመ ሲገለባበጥ የኖረው በኢትዮጵያና በተለይም በዐማራው ውርደት፣ ድህነት፣ ባርነት፣ ስደት፣ ግድያና ሰቆቃ ላይ የወያኔን የግዛት ዘመን ለማራዘም ነው።
የወያኔን አርባኛ ዓመት  ድል ያለ የንግሥ በዓል ተከትሎ የኢሕአፓና የዐማራ ህዝብ ከሀዲዎች ማህበር የሆነው ጉደኛው ብአዴን  ሳያፍር «የ35ተኛ ዓመት ልደቴን ላከብር ነው»  በማለት  ህዝቡን በመዋጮ ከማስጨነቁም አልፎ «በአለም ላይ የመጨረሻ ድሀ ክልል» የተባለውን የዐማራ ክልል ከፍተኛ በጀት ለበዓሉ ማክበሪያ መድቦ  አክብሯል።  ብአዴን በዐማራ ገንዘብ ድል  አድርጎ  ያከበረው የ35ኛ ዓመት የንግሥ በዓሉ  ድርጅቱን የመሰረቱት ወያኔና ሻዕብያ  ዐማራን እንዲያጠፋና በተገኘበት ሁሉ እንዲያሳርድ ስላደረገው አስተዋጽኦ ነው።
የብአዴኑ በረከት ሰምዖን የልደት ስም መብራህቱ ገብረህይወት ነው። ከመብራህቱ ገብረህይወት የተምታቱ ታሪኮች ዋናው በዘሩ ኤርትራዊ ሆኖ ሳለ የዐማራ ድርጅት መሪ መሆኑ ነው። ይሄ ከሞራል አንፃር ብአዴን ውስጥ ላሉ ዐማሮች  ስድብ ነው። መብራህቱ ገብረህይወት በሕብረ ብሄራዊ ድርጅት ውስጥ ኢትዮጵያዊ ነኝ የሚል ከሆነ ኢትዮጵያንም ቢመራ ጥያቄ ባልተነሳበት ነበር። ሰው አገሬ የሚለው አገሩ መሆኑ ይታመናልና። የዘር ፖለቲካ የሚያራምድ ግን የግድ እሱም ዘሩን የሚያቅፍ የፖለቲካ ድርጅት ወስጥ መግባት ይጠበቅበታል። ወያኔ «ዐማራ በዘሩ መደራጀት አለበት» ብሎ ሲያበቃ፣ የዐማራ ድርጅት ፈጠርሁ ብሎ ዐማራውን  እንዲመሩ ያስቀመጣቸው ግን  ዐማራ ያልሆኑትንና ከልዩልዩ ዘሮች ያውጣጣቸውን ምንደኞችንና ዐማራን በመጥላት ክብረ ወሰን የተቀዳጁ ቅጥረኛ ሰው በላዎችን በመሰብሰብ ነው። ይህም በመሆኑ የተነሳ ቂም ባዘለ የጥላቻ ክፋት ውስጥ ሆነው የወያኔን ዐማራ የማጥፋት ፕሮጀክት ከግብ ለማድረስ  ባለፉት ሀያ ስድስት ዓመታት አብረውት ደፋ ቀና እያሉ ከርመዋል።
አዲሱ ለገሰ፣ ህላዬ ዮሴፍ፣ ተፈራ ዋልዋ፣ ታደሰ ካሳ፣ ታምራት ላይኔ፣ ካሳ ተክለብርሀን፣ ወዘተ እንደ መብራህቱ ገብረሕይወት ሁሉ ዐማራ ያልሆኑና ራሳቸውን ግን የዐማራ ህዝብ ወኪል እኔ ነኝ የሚሉ የዐማራ ህዝብ ጠላቶች ናቸው። እነዚህ ሁሉ ወያኔ ያበጃቸው ፍጡራን ዐማራን ለማጥፋትና ዐማራውን በማዳከም ሕወሓትን ለማጠናከር በዐማራ ሕዝብ አናት ላይ የተቀመጡ የዐማራ ቀንደኛ ጠላቶች ናቸው። የወሎ መሬት ተቆርሶ ለትግራይ ሲሰጥ፤ የጎንደር መሬት ተገምሶ ለትግራይ ሲታደል፣ ጎጃም ለጉምዝ ተላልፎ ሲሰጥ፤ ሸዋ ለአምስት  ሲከፈል፤ ዐማሮች እንደ  ፋሲካ በግ በኦነግና በወያኔ ሲታረዱ እነመብራህቱ ገብረሕይወት፣ አዲሱ ለገሰና ታምራት ላይኔ የሰጡትን ምላሽ መቼም ልንረሳው አንችልም።
ነውረኛው አዲሱ ባለፈው ሰሞን ስለወልቃይትና ሁመራ እንዲሁም ሰሜን ወሎ ወደ ትግራይ ሪፑብሊክ ስለመካለሉ በትግርኛ  ተጠይቆ በሰጠው መልስ እወልከዋለሁ በሚለው በዐማራ ወንበር እየፏለለ  ከትግራይ ወገን ሆኖ «የዐማራው ገዢ መደብ ከትግራይ ቆርሶ የወሰዳቸው መሬቶች ስለነበሩ ነው ወደ ትግራይ የተካለሉት» ያለውን መቼም የማንረሳው  የቅርብ ጊዜ ትውስታ ነው። ዛሬ ፓስተር ሆኛለሁ እያለ የሚያጭበረብረው ታምራት ላይኔም ዐማሮች አርባጉጉ፣ ሀረር፣ ወለጋ፣ አርሲ ወዘተ እንደ ፋሲካ ዶሮ ሲታረዱ ካማራ ክልል ውጭ ያለ አማራ አናቅም ብሎ ተሳልቆባቸዋል።
የወያኔው በረከት ስምኦን   ካሳሁን ገብረሕይወት  የሚባል ወንድም ነበረው። መብርሀቱ  ስሙን   «በረከት ስምዖን» ሲል የቀየረው  የሻዕብያን ተልእኮ ይዞ በረሀ ከገባ በኋላ ነው። እውነተኛው በረከት ስምዖን  አዲስ አበባ ተወልዶ ያደገ፤  ሊሴ ገብረማርያም የተማረ ኤርትራዊ ነው። እውነተኛው በረከት ሰምዖን ለኤርትራ መገንጠል ከኢሕአፓ ጋር በርሀ ወርዷል።  ከጊዜ በኋላ  ግን ባልታወቀ ምክንያት ከኢሕአፓ መካከል ጠፋና የውሀ ሽታ ሆነ። ሆኖም ግን ሰውየው  ባልታወቀ ሁኔታ  ፈረንሳይ ላይ  ፓሪስ ተከሰተ። እውነተኛው በረከት ሰምዖን  በድንገት ስለጠፋ  ሊታገል አብሯቸው በረሀ የወረደ የመሰላቸው ኢሕአፓን የማያውቁት ተነጂዎች  በረከት ስምዖን  በደርግ የተገደለ ወይንም በነሱ ቋንቋ የተሰዋ  መሰላቸውና  በሰማዕትነት አሰቡት። በዚህ ጊዜ ነበር እንግዲህ  በደርግ  የተገደለ  የመሰለውን እውነተኛውን  በረከት ሰምዖን ለማስታወስ ሲባል  ሌላኛው የኤርትራ ተወላጅ  መብራህቱ ገብረህይወት  ስሙን በረከት ስምዖን  ሲል ስሙን ከናባቱ የለወጠው። ከዚህ ጊዜ በኋላ ነበር  ኤርትራዊው መብርሀቱ ገብረሕይወት በረከት ስምዖን እየተባለ መጠራት ጀመረ።
ከፍ ሲል እንደገለጽሁት  እውነተኛው በረከት ስምዖን በደርግ አልተገደለም ነበር።  በኢሕአፓ ውስጥ ሻዕብያ የሰጠውን ስራ ጨርሶ  በሌላ ምድብ ወደ ፓሪስ ተዛውሮ እንጂ። ይህ  እውነተኛው በረከት  አሁንም ድረስ  በሕይወት ፓሪስ ውስጥ ከእህቱ ጋር ይኖራል። እውነተኛው በረከት ሰምዖን ሩት ሰምዖንና  እና ሃና ሰምዖን  የተባሉ የሻዕብያ ታፋዮች የነበሩ  ሁለት እህቶች አሉት። እውነተኛው በረከት ሰምዖን  አሁንም ድረስ  በሕይወት ያለና   ሃና ስምዖን  ከምትባለው  እህቱ  ጋር በፓሪስ  ይኖራል።  በረከት ሰምዖን አብሯት የምትኖትረው  ታናሽ እህቱ ሃና አምዖን በፓሪስ  የኤርትራ አምባሳደር  ናት። ሩት ሰምዖን  ደግሞ በኤርትራ ማስታወቂያ ሚንስትር  መስሪያ ቤት ውስጥ በጋዜጠኛነት  የምትሰራና አሁንም ድረስ  አስመራ ውስጥ በስራ ላይ የምትገኝ ወይዘሮ ናት።
 ከብአዴኑ በረከት ሰምዖን ሌላኛው  የተምታታ ታሪኩ «የሁለት ምርጫዎች ወግ» ሲል የደረተውን የወያኔ ማኒፌስቶ በመታሰቢያ ገጸ በረከትነት እንዲውል ያደረገበት ጉዳይ ነው። የብአዴኑ በረከት በመጽሐፉ መግቢያ ላይ መጽሐፉን «መታሰቢያነቱ ለወንድሜ ለካሳሁን ገብረሕይወት» ይሁን ይላል።  የኢሕአፓ ታጋይ የነበረው መንድሙ  ካሳሁን ገብረሕይወት የሞተው ወያኔና ኢሕአፓ አሲምባ ላይ ባደረጉት ጦርነት ነው። ባጭሩ የብአዴኑ በረከት ሰምዖን ወንድም ካሳሁን ገብረሕይወት የተገደለው ከወያኔ በተተኮሰ ጥይት ነው።  በረከት ግን «የሁለት ምርጫዎች ወግ» ሲል  የጻፈውን የወያኔ ማኒፌስቶ መታሰቢያ ያደረገው በወያኔ ጥይት ለተገደለው ለወንድሙ ለካሳሁን ገብረሕይወት ነው።  በረከት «የሁለት ምርጫዎች ወግ» ሲል የደረተውን የወያኔ ማኒፌስቶ በወያኔ ጥይት ለተገደለው ወንድሙ ያበረከተው  ምን ለማለት ፈልጎ እንደሆነ ባብስ ባስብ ትርጉም ላገኝለት አልቻልሁም።  ለነገሩ ትርጉሙን  በረከት ራሱ ቢጠየቅ  መግለጽ የሚችል አይመስለኝም። በረከት እንዲህ ከራሱ የተጣላ ሰው ነው።  ዐማራ ሳይሆን አማራ ነኝ፤  መብርሀቱ ገብረሕይወት ሆኖ ሳለ ሙሉ በሙሉ ስሙን ቀይሮ ባልሞተ ሰው ስም በረከት ስምዖን ነኝ የሚል በሽተኛ ነው።
በረከት እያወቀ ይሆን  ተስቶት ባላውቅም «የሁለት ምርጫዎች ወግ» በሚለው   መጽሐፉ ግን  አንድ እውነት ተናግሯል። በመጽሐፉ መግቢያ ላይ መታሰቢያ በሚለው ገጽ  «ለወንድሜ ለካሳሁን ገብረህይወት መታሰቢያ ይሁን»  ካለ  በኋላ «እነሆ በተለምክልኝ መንገድ እጓዛለሁ» ይላል። በረከት ሰምዖን «የሁለት ምርጫዎች ወግ» የሚለውን መጽሐፉን ያበረከተለት ወንድሙ ካሳሁን ገብረሕይወት የኢሕአፓ ታጋይ እንደነብረ  ከፍ ብዬ ገልጫለሁ። ኢሕአፓ  የተፈጠረውና  የታገለው «የዐማራ ማን አህሎኝነት የወለደው  የብሔር ጭቆና አለ» ብሎ ነበር። ይህ ማለት ኢሕአፓ የታገለው «ጨቋን» ያለውን  ዐማራን ለማጥፋት ነበር ማለት ነው።  በዚህ ረገድ የብአዴኑ  በረከት ሰምዖን አልተሳሳተም። ወንድሙ  ካሳሁን ከኢሕአፓ ጋር በረሃ የወረደው ዐማራን  ለማጥፋትና ኢትዮጵያን ለማፍረስ ነበርና።  የኢሕአፓው የካሳሁን ገብረሕወት ታናሽ ወንድም መብራህቱ  ገብረሕይወት ወይንም በሚንስትር ስሙ በረከት ሰምዖን በታላቅ ወንድሙ ተጽዕኖ  ይሄው  እስከዛሬ ዐማራን ለማጥፋትና ኢትዮጵያን ለመበታተን እየሰራ ይገኛል።
ስለዚህ የብአዴኑ በረከት በጻፈው መጽሐፍ  መታሰቢያ ገጽ ላይ እንዳሰፈረው  ኢሕአፓው  ካሳሁን ገብረሕይወት  የድርጅቱን የኢሕአፓንና ተልዕኮ የሰጠውን የሻዕብያን አላማ ለታናሽ  ወንድሙ  ለካሳሁን ወይንም ካሳሁን ከሞተ በኋላ በሚታወቅበት  ስሙ በረከት እየተባለ ለሚጠራው ወንድሙ  አውርሷል። ምንም እንኳ ኢሕአፓው ካሳሁን በወያኔ ጥይት ቢገደልም  አላማውንና የተከተለውን መንገድ  ግን  የናቱ ልጅ   ታናሽ ወንድሙ ከግብ አድርሶለታል። ከሳሁን ዛሬ በሕይወት ቢኖር ኖሮ እንደ እውነተኛው በረከት ሰምዖን እህት እንደ ሃና  የእናት ድርጅቱ የሻዕብያ  ማእከላዊ ኮምቴ አባልና የኤርትራ ከፍተኛ ባለስልጣን ይሆን ነበር።
ከሰሞኑ ደግሞ ሰውየው [በረከትን ማለቴ ነው] መሄጃ እየፈለገ  እንደሆነ የሚነገረው   የሚታይ ቢሆንም  ኢትዮጵያን ይዟት ገደል ሳይገባ ግን  መሄጃ የሚፈልግ አይመስለኝም። በስውር የሚሰራውን ባናይ እንኳ በረከት ባንደበቱ  የሻዕብያ ሰላይ  የነበረው ኢሕአፓው ወንድሙ በተለመለት  የሻዕብያ መንገድ እየተጓዘ እንደሆነ የነገረንን ግን  መርሳት  ያለብን  አይመስለኝም። የሆነው ሆኖ  በረከት ሰምዖን  ኢትዮጵያን ይዟት   ገደል ሳይገባ መሄጃውን  የፈለገ እንደሆነ  ሻዕብያ  ላገራችን  ትልቅ ውለታ እንደሰራተሚቆጠርለት ይመስለኛል።
Filed in: Amharic