>
5:13 pm - Saturday April 19, 6504

ለሰው ጉድጓድ አትቆፍር፣ከቆፈርክም አታርቀው … (አምባቸው ደጀኔ - ከወልዲያ)

ለሰው ጉድጓድ አትቆፍር፣ከቆፈርክም አታርቀው …

አምባቸው ደጀኔ (ከወልዲያ)


“ብትችል ለሰው ጉድጓድ አትቆፍር፣ ከቆፈርክም አታርቀው፡፡ ምክንያቱም ቀድሞ የሚገባበትን አታውቀውምና፡፡” ምንጫቸው ከየትኛውም ቋንቋና ባህል ይሁን እነዚህን መሰል አባባሎች የሚያስተላልፉት ገምቢ መልአክት ግን ከሽህ ቃላት የዝርው ንግግር የበለጠ ፍሬያማ ነው፡፡ ችግራችን ነገርን በጊዜው ያለማስተዋል የሚፈጥርብን ብዥታ ነው፡፡

የቱን አንስቼ የቱን እንደምጥል በመጨነቅ መጻፌን ለጊዜውም ቢሆን ማቆም ፈልጌ ነበር፡፡ ግን ራሴው ታፍኜ ልሞት ያህል ተሰማኝና ስለወቅቱ የሀገራችን የፖለቲካ ትኩሣት ትንሽ መተንፈስ ፈለግሁ፡፡ ይሞታል እንዴ!

 በቅድሚያ ስለሽመልስ አብዲሣ፡፡ ነገር በምሣሌ ሲሆን ጆሮ ግቡ ይሆናል፡፡ አንድ ሙሽራ እንደሽመልስ ዘርፍጥ ኖሮ ከማንም ጋር ሲቀላቀል አንዳችም ቃል ትንፍሽ እንዳይል “ልጄ ንግግርህ አር አር ስለሚል አደራህን እንዳታዋርደኝ ዝም በል፤ ምንም ነገር እንዳትናገር” በማለት እናቱ ታስጠነቅቀዋለች፡፡ “ባለጌ፣ ስድ … ምናምን” እያልክ ስድብህን አታባክን ታዲያ – እንደዘመዴ ነጭ ነጯን ነው የማወራልህ፡፡ ያሻህን ብትለኝም ምንም አይመስለኝ – ከፈለግህ፡፡ ይህ ጅል ልጅ ታዲያልህ ወግ አይቀርምና ምሽት ያገባል፡፡ አግብቶም ለመልስ ይሁን ለቅልቅል ወደ አማቾቹ ቤት ይጠራል፡፡ ቤተሰብ እየበላ እየጠጣ ሲጫወት እርሱ አንዴውን ተመክሯልና ፀጥ ረጭ ይላል፡፡ ያ ዝምታው ያሳሰባቸው የሙሽራይቱ እናት “ምነው ልጄ ተጫወት እንጂ! በደስታችን ቀን የምን ዝምታ ነው?” በማለት ደጋግመው ይወተውቱታል፡፡ እርሱ ግን ያው “ሞኝ የነገሩትን፣ ብልኅ የመከሩትን” እንዲሉ ነውና ዝም ይላቸዋል፡፡ ሴትዮዋ አልለቀቁትም፤ እንዲናገር ነዘነዙት፡፡ እርሱም “አይ፣ እናቴ ‹ንግግርህ አር አር ይላልና የትም ቦታ ስትሄድ ዝም በል› ብላኛለችና አልናገርም” በማለት ይመልስላቸዋል፡፡ እርሳቸውም “ውይ በሞትኩት! ኧረ ለኔ ማር ነው ልጄ፤ በል ተጫወት፤ ዝም አትበል” በማለት ከአፉ ማር ጠብ እንዲል ጠብቀው በሞራል ያበረታቱታል፡፡ አያ ሞኞ ጨዋታውን ይቀጥላል “እሽ፣ እንደሱ ካሉኝማ እናገራለሁ…” ይልና ጨዋታ ይጀምራል፡፡ በልጁ ዝምታ ተገርሞ የነበረው ቤተሰብም የየግል ጨዋታውን አቋርጦ በጉጉት ማዳመጡን ይቀጥላል፤ ጉድ ሊፈላ ነው፡፡

(ጅል) አማች፡- ይሄ ልጅ የማነው?

(ቀበጥ) አማት፡- የኔ

አማች፡- ያኛውስ?

አማት፡- አዎ፣ እንደሱ ነው መጫወት – እሱም የኔ ነው ልጄ!

አማች፡- እነዚያ እዚያ ወዲያ ያሉትስ የርስዎ ልጆች ናቸው?

አማት፡- እንዴታ! ሁሉም የኔ ናቸው

አማች፡- ሆ! እነዚህ እያ ታች ያሉትስ?

አማት፡- አፌ ቁርጥ ይበልልልህ! አዎ፣ እነሱም የኔ ናቸው

አማች፡- የሆነስ ሆነና ይህን ሁሉ ውጫጭ የወለዱበት “ሆድዎ” እንዴት ይሰፋ!

አማት፡- እ? ምን አልከኝ? እውነትም ከአርም አር!

 

ሽመልስን ለመግለጽ ምሣሌ አጥቼ ከፍ ሲል የተጠቀስውን ሥነ ቃል በመጠቀሜ ይቅርታ መጠየቅ ካለብኝ አይከፈልበትምና ይሄው ጠየቅሁ፡፡ እንደዚህ ያለ ነፍጫላ ሰው ሲያጋጥም የምንገልጸው በዚህ ዓይነቱ ሥነ ቃል ነው፡፡ አፉን በከፈተ ቁጥር እንዳንዳች ነገር የሚቆንስ ነገር የሚያወጣ ብቸኛው ለፍዳዳና አስተዳደግ የበደለው “ሰው” ሽመልስ አብዲሣ ነው፡፡ እርግጥ ነው – ጃዝ ብሎ የለቀቀው ኦሮሙማው ግራኝ አህመድ አቢይ ለዚህ ተጠያቂ ነው፡፡

ሀገራችን በምን ዓይነት ቆሻሻ እጆች ውስጥ እንደገባች በተለይ በፋሲል ከነማ አሸናፊነት ምክንያት በተደረገው የሰይጣኖች ስብሰባና የገቢ ማሰባሰብ ፕሮግራም ይበልጥ እየተረዳን ነው፡፡ ከዕድሜ ነው እንዳንል ደመቀ መኮንንን የመሰለ አንጋፋ ሰው አለ፤ ከትምህርት እንዳንል የግዥና የለብለብም ቢሆን ብዙ ዶክተር ተብዬዎች አሉ፤ እንግዲያው ከእርግማን መሆን አለበት፡፡ በድንቁርና፣ በሆዳምነትና በተረኝነት አባዜ የተለከፈው የጎሣ ፖለቲካ በዓለም ፊት እጅጉን እያዋረደን ነው፡፡ ከዚህም በላይ ብዙ አሣር እንደሚያስከትል ደግሞ ከግምት ባለፈ መናገር እንችላለን፡፡

የብአዴን ነገር እየፈጩ ጥሬ ነው፤ መቼም የማይበስሉና በአማራ ደም ሽያጭ እየከበሩ ያሉ ደነዞች ናቸው – ብአዴን ክርስቶስን በ30 አላድ ከሸጠው ይሁዳ ቢከፋ እንጂ አያንስም፡፡ የዚህ በአማራ ደም የሚሳለቅ ድርጅት አባላት ነገ ከማንም በፊት እንደሂትለርና ሙሶሊኒ ተዘቅዝቀው ሲሰቀሉ ይታዩኛል፡፡ በተለይ ይሄ አገኘሁ ተሻገር የተባለ ግዑዝ “ሞሮን” – ሌላ ቃል አጥቼ ነው ይቅርታ – ይሄ ሁለመናው አስጠሊታ ሞሮን እያለ አማራ ይቅርና ኢትዮጵያ ትልቅ አደጋ ላይ ናት፡፡ ሰውዬው ዋናው የኃጢኣታችን ዋጋ ነው፡፡ በሃይማኖቱም በፖለቲካውም የተጣባን የአጋንንት መንጋ ትልቁ መገለጫ አገኘሁ ተሻገር ነው – የአቢይ ቀድሞ የተነገረለት ስለሆነ ይታወቃል፡፡ የዚህ አጋሰስ ደንቆሮ ግን ለዬት ይላል – ስለርሱም ቀድሜ የሰማሁት ነገር የለም፡፡ ደግሞ እኮ አገኘሁም ሆነ ጅላንፎው ሽመልስ ሲናገሩ የሚደመጠው ጭብጨባ ለጉድ ነው፡፡ እንዴት አንድ በሳል ሰው እንኳን ይጠፋል? እንዴት ሁሉም ተያይዞ ቁልቁል ይነጉዳል?

በአንድ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ነው፡፡ የደብር አለቃው ዐውደ ምሕረቱ ላይ ቆመው አንድ ተማጽኖ ለምዕመናን እያቀረቡ ነው፡፡ “ውድ ምዕመናን! ባለፈው ወር ብቻ ለመብራት፣ ለስልክና ለውኃ ብቻ አራት ሽህ ብር እንድንከፍል ተጠይቀ…” ብለው ማሰሪያ አንቀጹን በ“-ናል” ከመዝጋታቸው ምዕመኑ ከዳር እስከዳር እልልታውን አቀለጠው፡፡ “ኧረ በኅያው እግዚአብሔር ይሁንባችሁ! የሚጨበጨብበትንና የማይጨበጨብበትን ለዩ!” በማለት በቁጣ አስገነዘቡ፡፡ ማን ሊሰማ! ትልቅ የዕውቀት ኪሣራ ውስጥ ነን፡፡ የሀገራችን የንቃተ ኅሊና ሁኔታና ያለበት ደረጃ ክፉኛ ያስፈራኛል፡፡ በንቃተ ኅሊና የወረደ ሕዝብ ደግሞ ለማንኛውም የክፋት፣ የተንኮልና የምቀኝነት ሥራ በእጅጉ የቀረበ ነው፡፡

ለማንኛውም ካህኑ ስብከታቸውንና የገንዘብ ልማኖ ተማጽኗቸውን ቀጠሉ፡፡ ከደቂቃዎች በኋላም ለአንድ ንግግራቸው ምሣሌ እንዲሆናቸው  “ውድ ምዕመናን! እባካችሁ ለራሳችን እንጠንቀቅ፡፡ ሀገራችን ኢትዮጵያ ከሰሃራ በታች ካሉ ሀገሮች በኮሮና ወይም ኮቪድ 19 በሚሉት በሽታ አንደኛ ሆናለ …” ብለው ሊያስረዱ “-ች” ስትቀራቸው እልልታው አቋረጣቸው፡፡፡ “እልልልልልል …..” ደብሩ በእልልታ ተናጠ፡፡ ይሄኔ ቄሱ ተናደዱ፡፡ ከዚያ በኋላ ለዚህ ሕዝብ ዕውቀትንና ጥበብን መራብ ሌላ ምስክር ሳያስፈልጋቸው በዚያ መድረክ ብቻ በመገንዘባቸው ዳግመኛ ዐውደ ምሕረት ላይ ተገኝተው ላለመስበክ ለራሳቸውና ለፈጣሪ ቃል ገቡ፡፡ ምናልባትም ሳይገድሙ አልቀሩም፡፡ እላይ እሳት፤ እታች እሳት፡፡ ኢትዮጵያን ምን ይዋጣት እንግዲህ? ከዚህ ሕዝብ የተገኘ ሕዝብ ቢታረድ ተጠያቂው ማን ነው? ከዚህ ህዝብ የተገኘ ሕዝብ ለዲፕሎማሲ ሥራ ተመድቦ ሀገሩን እንዲወክል ቢላክና ከዚያ የተከበረ ሥራ ይልቅ ሸቀጥ እያስገባና እያወጣ ከመሸጥና በገንዘብ ከመክበር ውጪ ሌላ ትርጉም ያለው ተግባር ባያከናውን ኃላፊነቱ የማን ነው?

ይህች መርከብ ልትቃጠል ነው፡፡ ይህች ግዙፍ አውሮፕላን ልትከሰከስ ነው፡፡ ይህች ከአፍ እስከ ገደፏ በሰው ጢም ብላ የተሞላች የከተማ አውቶቡስ ከቋጥኝ ጋር ተላትማ በጢምቢራዋ ልትደፋ ሩብ ያህል ሐሙስ ብቻ ቢቀሯት ነው፡፡ ሹዋሚው ደንቆሮ፣ ተሹዋሚው ደንቆሮ፣ ቢሮክራሲው ደንቆሮ፣ ትልቁም ትንሹ ማይም፡፡ እውነተኛው ልጅ እየተቀበረ እንግዴ ልጁ በሚያድግባትና ሀገርን እንደ ዶሮ እየበለተ ጉሊት አውጥቶ በሚቸረችርባት ሀገር መፈጠር ያበሳጫል ብቻ ሳይሆን ያሳብዳል፡፡ ኢትዮጵያ የ”እንስሳት ዕድር” መጽሐፍ እውናዊ መገለጫ ሆናለች፡፡ (የጆርጅ ኦርዌል ‹አኒማል ፋርም› ማለቴ ነው) ከዚህ ጣር እንድትወጣ ማን ይድረስላት? መቼ? ምን እየሠራን ነው?

አንድ ደህና ዲፕሎማት እስኪ ጥሩልኝ፡፡ አንድ ደህና አስተዳዳሪ እስኪ ጥሩልኝ፡፡ እንደሚባለው በነአክሊሉ ሀ/ወልድ፣ በነፊታውራሪ ሀ/ጊዮርጊስ፣ በነራስ አሉላ ….ሀገር እንዲህ ያለ ጉድ ይፈጠር? አሁን ሱባኤ ያልተገባ መቼ ይገባ? አሁን ለኢትዮጵያ ያልተለቀሰና የቁም ተዝካር ያልወጣ መቼ ይለቀስና ተዝካርም ይደገስ? ጳጳሱና ቄሱ ሌባ፣ ሚንስትሩ ሌባ፣ ጠ/ሚንስትሩ የሰው ደም ሳይጠጣ እንቅልፍ የማይወስደው አስመሳይ ልዝብ-ሰይጣን፣ ባለሥልጣናት ሁሉ ቀበኞችና ያለ ሙስናና ያለወንጀል በሕይወት ውለው የሚያድሩ የማይመስላቸው፣ ዲፕሎማቶች ሁሉ ከዕውቀትም ከቋንቋም ከልምድም ከችሎታም ከተግባቦትም … የጸዱ ድፍን ቅሎች … ሕዝቡም በስማም የተባለበት ሰይጣን … ሆነን እስከመቼ? እንኳን ሀገር ለመምራት ለመመራትም የሚያስቸግሩ እነዚህን መሰል ደናቁርት ከየጢሻው እየለቀመ በላያችን ላይ የሚጭንብን ማን ነው? ይህ ነገር ከበደላችን ብዛት የተነሣ የአምላክ ቁጣ ነው ብንል ስህተት የለውም፡፡ ለተፈጥሮ ቁጣና መለኮታዊ መቅሰፍት አብነቱ ደግሞ አጥብቆ መጸለይና የፈጣሪን መንገድ መከተል ብቻ ነው፡፡ “አይሆንምን ትተሸ ይሆናልን ባሰብሽ” ነውና ነገሮች ከዚህም በባሰ ሳይበላሹ ይህችን ሀገር ከተደገሰላት የመጥፋት አደጋ ለመታደግ ከጸሎትና ምህላ ጀምሮ የተቻለንን ሁሉ እናድርግ፡፡ በፖለቲካ ተንታኞችና በአንዳንድ አዋልዳዊ መጻሕፍትና “ነቢዮች” እንደሚነገረው ከሆነ ለዳግም ትንሣኤ ወደሚያስቸግር ሁኔታ እየገባን ነው፡፡  

ቢሆንም ቢሆንም …. ተስፋችን አንድዬ ነውና በርሱና በርሱ ብቻ እንደሀገርና ሕዝብ የመቀጠል ተስፋችን ይለመልማል፡፡ በጀመርኩት ለመጨረስ ያህል – ብንችል “ለማንም ጉድጓድ አንቆፍር፡፡ ከቆፈርንም አናርቀው፡፡ ቀድሞ  የሚገባበትን አናውቀውምና፡፡” በቆፈሩት ጉድጓድ ያልገቡ የሉም፡፡ አምላክ “በቀልን ለኔ ተዋት” ማለቱን አንርሣ፡፡ የቀንን ማዳለጥ (መክዳት) ደግሞ ማንም አይችለውም፡፡ ወያኔ በዚያ ሁሉ ሀብት ንብረቱና በዚያ ሁሉ የጦር መሣሪያው እስትንፋሱን ከ17 ቀናት በበለጠ ሊያዘገይ አልተቻለውም፤ ፍርዱ ከላይ ነዋ! 17 ዓመታትን የፈጀበትን ሀገርን የማፍረስና አማራን የመፍጀት ዓለም አቀፍ ዘመቻ በ17 ቀናት ጦርነት ማጣት በራሱ ለተረኞች ትልቅ ትምህርት በሆነ ነበር፡፡ ማንም በጉራና ትዕቢቱ አይድንም፡፡ በበኩሌ እነሽመልስን እንደኅልውና ሥጋት አልቆጥራቸውም፡፡ ኃጢኣታችን ያመጣቸው ግን በቀናት ውስጥ እንደጤዛ የሚረግፉ ሠራዊተ ዲያቢሎስ ናቸው፡፡ መትጋት ያለብን ከአምላካችን ጋር የሚያገናኘንን ሰባራ ድልድይ እመጠገኑ ላይ ነው፡፡ በመጨረሻው መጨረሻ ቤተ ክርስቲያንም ትታጠባለች – እንደተፌዘባት አትቀርም፡፡ ቤተ መንግሥታችንም ይጸዳል – የሰው መታረጃ ቄራ እንደሆነ አይቀርም፡፡ ጥጋበኞች ምንዳቸው ይከፈላቸዋል – የምለው ነገር የኔ የግል እውነት ሣይሆን የዓለማችን ነባራዊ እውነት ነውና ማንም ሊያላግጥበት የሚገባ ተራ ነገር አይደለም፡፡ ግን እንጸልይ፡፡ ለአሁን በቃኝ፡፡

Filed in: Amharic