>

አሜሪካና አውሮፓ ሲፈልጉ እንጂ ስንፈልግ ረድተውን አያውቁም!!!  (ዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ)

አሜሪካና አውሮፓ ሲፈልጉ እንጂ ስንፈልግ ረድተውን አያውቁም!!!

 ዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ

.
ሀገራችን በጣልያን ስትወረር የአለም መንግስታት በኢትዮጵያ ላይ የጦር መሳርያ ግዢ ማእቀብ ጥለዋል፡፡ የሚፈልጉት ኢትዮጵያም እንደመላው አፍሪካ በቅኝ ግዛት ስር እንድትወድቅ ነበር፡፡ የእኛ ነጻነት ፍላጎታቸው አልነበረም፡፡ እንደፍላጎታቸው አደረጉ፡፡ አሸንፈን ነጻነታችንን አስጠበቅን፡፡ ጥርሳቸውን ነከሱብን፡፡
.
ኢትዮጵያ ላለፉት 15 አመታት በአመት ከሰባት መቶ ሺህ ቶን በላይ የምግብ እህል እርዳታ ተቀብላለች፡፡ አብዛኛው ከምእራባውያን የተገኘ ነው፡፡ እነዚህ ሀገራት አባይን ለመገደብ ሳንቲም ለመስጠት ፍቃደኛ አልነበሩም፡፡ ፍላጎታቸው በእለት ጉርስ ሊለጉሙን ነው፤ ትልልቅ ፕሮጀክቶችን ተግብረን ከልጓማቸው እንድናመልጥ አይፈልጉም፡፡ ከሌለን ቆንጥረን አባይን ገደብን፡፡ የስንዴ ልጓማቸው ሲላላ – ሲወልቅ ታያቸው፤ ዛሬም ማእቀብ ጣሉብን (በነገራችን ላይ የአውሮፓ ህብረትም አሜሪካን እንደሚከተል አዝማሚያው ያመላክታል)፡፡ ከቅኝ ግዛት ቀንበራቸው አምልጣ የነጻነት ምሳሌ የሆነችው ሀገራችን፣ ከድህነት ወጥታ እራስን የመቻልና የ‹‹እንቢባይነት›› ምሳሌ እንድትሆን አይፈልጉም፡፡
.
በ1969 አ.ም. ሱማልያ ስትወረንም አሜሪካ ከወራሪዎቻችን ጋር ነበረች፡፡ በሶቭየት ህብረት  እና ኩባ እርዳታ በድል ተወጣነው፡፡
.
አሜሪካ በሱማልያ ታላቅ ውርደት ከገጠማት በኋላ፣ ጦርነቷን እኛ እንድንዋጋላት ፈለገች፡፡ ስለፈለገች ዶላር ሰጠችን፤ መሳሪያ አስታጠቀችን፤ መድሀኒትና ስንዴ አፈሰሰችብን፡፡ ከሩብ ምእተአመት በላይ ጦርነቷን ተዋጋንላት፡፡ ሞቷን ሞትንላት፡፡ ዛሬ ‹‹አፍሪካውያን ተገቢ ቦታችን ያለንበት አይደለም፤ አፍሪካውያን መተባበር አለባቸው፤ እራሳቸውን መቻል አለባቸው፤›› እያለ የሚፎክር መሪ በኢትዮጵያ መጣ፡፡ ዛሬ ‹‹ተላላኪ መንግስት በኢትዮጵያ ከእንግዲህ አይኖርም፤ ለሀገሬ ጥቅም ግንባሬን እሰጣለሁ›› የሚል መሪ መጣ፡፡ ይህ የምእራባውያን ፍላጎት አይደለምና ያሳስባቸዋል፤ እንቅልፍ ይነሳቸዋል፡፡ እንቅልፍ የሚነሳቸው የመሪዎች አንባገነንነትና ዲሞክራትነት አይደለም፤ ይህ ለእነሱ የመጫወቻ ካርድ ነው፡፡
.
ዛሬ እውን በትግራይ ህዝብ ላይ የደረሰውና እየደረሰ ያለው አስከፊ ችግር አሳስቧቸው ቢሆን ኖሮ፣ በየመግለጫቸው ለዚህ ጥፋት ከዳረገው ህውሀት ጋር ጎን ለጎን አይጠቅሱትም ነበር፡፡ ህወሀት በሰሜን እዝ ላይ ያደረሰውን ጥቃት፣ በማይካድራ የጨፈጨፋቸውን ንጹሀን ዜጎች አያስታውሱን፡፡ ምክንያቱም ፍላጎታቸው የሰብአዊ መብት መከበር፣ የፍትህና ሰላም መጠበቅ አይደለም፡፡ ፍላጎታቸው ታዛዥ መንግስት እንዳለ ማረጋገጥ፣ ኢትዮጵያን በስንዴ ልጓማቸው እስከዘለአለም መጎተት ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ እውነት፣ ፍትህና ሰብአዊነት ቢንኮታኮት ደንታቸው አይደለም፡፡ ከድሀ ሀገራት ጋር ያላቻው ታሪክ የሚመሰክረውም ይህን ነው፡፡
.
ኢትዮጵያውያን ድሆች ነን፡፡ የምእራባውያን ፍላጎት ፍላጎታችን እስካልሆነ ድረስ የእኛ ፍላጎት ፍላጎታቸው እንደማይሆን ማወቅ አለብን፡፡ ፍላጎታችንን ፍላጎታቸው ማድረጉ አይደለም ትልቁ ቁምነገር፡፡ ትልቁ ቁምነገር ለፍላጎታችን እውን መሆን አንድ ሆነን መነሳት፣ መስራት ነው፡፡ አባቶቻችን መስዋእትነት ከፍለው ነጻ ሀገር ሰጥተውናል፡፡ እኛ ልዩነታችንን መፍታት ቢያቅተን እንኳ አጥበን፣(ያም ካቃተን ለጊዜው ችላ ብለን)፣ ሬትን ተጎንጭተን፣ ተግተንና ተባብረን ለልጆቻችን በነጻነት ላይ እራስን መቻል ጨምረን ሀገራችንን ለማስተላለፍ እንጀግን ዘንድ ጊዜው ዛሬ ነው፡፡ ሀገራችን በአሜሪካና ሌሎች ጣልቃ ገብነት እንድትጨልም አንፈቅድም፤ ኢትዮጵያ ለልጆቻችን፣ ለልጆቻቸው፣ ለልጅ ልጆቻቸው . . . ለዘለአለም መንጋት አለባት፡፡
Filed in: Amharic