>
5:13 pm - Friday April 19, 9529

በሀገሬ ቃል ኪዳኑን የሚጠብቅ አንድ ኃይል ብቻ መኖሩን አስተዋልኩ!? (አምባቸው ዓለሙ - ከወልዲያ)

በሀገሬ ቃል ኪዳኑን የሚጠብቅ አንድ ኃይል ብቻ መኖሩን አስተዋልኩ!?

አምባቸው ዓለሙ (ከወልዲያ)


  1. ይመሻል፤ ይነጋል፡፡ ቀናትና  ሣምንታት፣ ሣምንታትና ወራት፣ ወራትና ዓመታት ጊዜን እየተቀባበሉ ወደፊት ያስኬዱታል፡፡ በዚህ የማይቋረጥ ሂደት ውስጥ ብዙ ነገሮችን እናያለን፤ ተለዋዋጭ ክስተቶችንም እንታዘባለን፡፡ ሰዎች ይወለዳሉ፤ ያድጋሉ፤ ያረጃሉ፤ ይሞታሉ – ለዚህ ረጂም ሂደት የማይበቁ ዕድለኞች ወይም ዕድለቢሶች መኖራቸውም እንዳለ ሆኖ፡፡ መንግሥታትም እንደዚሁ ይወለዳሉ፤ አደጉም አላደጉም ያረጃሉ፤ ይሞታሉ፡፡ ሰዎችም ሆኑ መንግሥታት በምክንያት ወይም አለምክንያት ይዋሻሉ፤ ይቀጥፋሉ፤ ሕይወትን ጨምሮ ቁሣዊ ሀብትና ንብረትን ይሰርቃሉ፤ ይዘርፋሉ፤ ግድያን ጨምሮ እጅግ ዘግናኝ ወንጀሎችንም ይፈጽማሉ፡፡ ይህ ሁሉ ግን የዓለምን ተጨባጭ ሁኔታ በቅጡ ካለመገንዘብ የሚመነጭ ሞኝነት መሆኑን መረዳት አይከብድም፡፡
  2. ዐፄ ኃ/ሥላሤ በንጉሠ ነገሥትነታቸው ሽዎች ዓመታትን ለመቆየት “አስበው” አልጋቸውን ለማጽናት ሲሉ ከሰማይ በታች የነበሩ የሥልጣን ማቆያ ብልኃቶችን ተጠቀሙ፤ ከቢሾፍቱ ቆሪጥ እስከገዳም ባህታዊ ያልተማከሩትና ያላማከሩት ዐዋቂና ነቢይ አልነበረም፡፡ ቀንም ሆነ ሌትም ሆነ፡፡ ያ ሁሉ ልፋትና ድካማቸው ግን ዕድሜያቸውን ጨምሮ፣ ንግሥናቸውን አራዝሞ ንጉሡን ከመስከረም 2 ቀን 1967ዓ.ም ወዲህ እንዲዘልቁ የሚያደርግ አንድም ምድራዊም ይሁን ሰማያዊ መላ አላገኙም፡፡
  3. ኮሎኔል መንግሥቱ ኃ/ማርያም የኢትዮጵያ ሕዝባዊ ዴሞክራሲያዊት ሪፓብሊክ ፕሬዝደንት እንደሆኑ ሚሊዮን ዓመታትን ለመዝለቅ “አስበው” ወንበራቸውን ለማጽናት ሲሉ ከፀሐይ በታች የሚገኙ የግድያና የእስር ዘዴዎችን ጥቅም ላይ አዋሉ፡፡ ገናናና አስፈሪ የምሥራቅ አፍሪካ መንግሥትና ጦር መሥርተው ኬንያን መሰል ቦቅቧቃ መንግሥታትን ሳይቀር በፍርሃት አራዱ፡፡ ለወንበራቸው ሲባል በርካታ የሀገር ሰብኣዊና ቁሣዊ ሀብት ለጥይትና ለእሳት ተማገደ፡፡ ግን ቀንም ሆነ ሌትም ሆነ፡፡ ግርማ ሞገሣቸውንና አስፈሪነታቸውን ጨምሮ፣ የኢሠፓ ሊቀ መንበርነታቸውን፣ የጦር ኃይሎች ዋና አዛዥነታቸውንና የኢፌዲሪ ፕሬዝደንትነታቸውን አራዝሞ ከግንቦት 13 ቀን 1983ዓ.ም ወዲህ አንዲትም ደቂቃ እንዲዘልቁ ያደረገ ብልኃት አልተገኘም፡፡ 
  4. ጠ/ሚኒስትር መለስ ዜናዊ የፀረ-ኢትዮጵያዊቷ አዲሲቷ ኢፌዲሪ መንግሥት ዋና ቁንጮ እንደሆኑ ሽዎች ዓመታትን ለመቆየት “አስበው” የአፓርታይድ ወንበራቸውን ለማደላደል ሲሉ ከሰማይና ከፀሐይ በታች የሚገኙ ጸረ አማራና ጸረ አንድነት መርዞችን አንድም ሳያስቀሩ አሟጠው ተጠቀሙ፡፡ በመቶ ሽዎች በጦርነት ሞቱ፤ በሚሊዮኖች ተሰደዱ፤ በመቶ ሽዎች በርሀብና በበሽታ አለቁ፤ በማንነታቸውና በአንዲት ሀገር ኅልውና ጽኑ እምነታቸው ምክንያት በሚሊዮኖች ከመኖሪያና ከሥራቸው ተፈናቀሉ፤ ሁሉም ሆነ፤ ሁሉም ታዬ፡፡ ቀንም ሆነ ሌትም ሆነ፡፡ የቀን የኅሊና ዕረፍትና የሌት ዕንቅልፍ ያጡበት ያ ሁሉ ድካማቸው ግን ዕድሜያቸውንና በዘር መድሎ የተጨማለቀውን ህገ መንግሥታቸውን አሻሽሎ፣ ለሠሩት ጥፋት እንዲጸጸቱ ዕድል ሰጥቶ ሥልጣናቸውን በማራዘም ከነሐሴ 14 ቀን 2004ዓ.ም ወዲህ ስንዝር እልፍ እንዲሉ አላደረገም፡፡ አዲስ ነገር አልተናገርኩም፡፡ ለማስታወስ እንጂ፡፡ ከአሁን በፊትም ሆነ ከአሁን በኋላ ይሄው ሂደት ይቀጥላል – የሞኞች ድንቁርናም ጭምር፡፡
  5. በዚህ ሁሉ አስደማሚ የሕወትና የኹነቶች መፈራረቅ ውስጥ እኔም ምናልባትም አንተና አንቺም ነበርሽ፡፡ የጎደለብን ካለ “ጎድሎብናል” ብለን ያመንነው ነገር ብቻ እንጂ በጤናማ ሕይወት መኖራችን ብቻውን ትልቅ የፈጣሪ ስጦታ ነው፡፡ እናስበው – ስንቱ ሞተ፤ ስንቱ ታሰረ፤ ስንቱ ተገደለ፤ ስንቱ ተሰደደ፤ ስንቱ ደኸዬ፣ ስንቱ ለማኝና ዕብድ ሆነ፤ ስንትና ስንቱ በግፈኞች መከራና ስቃይ ደረሰበት፤ ስንቱ … ለምን ብትል ኢትዮጵያ ናታ! እንግዲህ መንግሥትም ውሸታምና ገዳይ ሲሆን፣ እኛም ሀሰተኞችና እንደሁኔታዎች ተለዋዋጭ ስንሆን ያልተለወጡት የፈጣሪ ፍርድና የርሱ ፍጡር የሆነችው ተፈጥሮ ብቻ ናት፡፡
  6. ምርጫው ተጠናቀቀ፡፡ አቢይ አህመድ ከፍ ሲል የተገለጹትን አያውቅም ወይም ሊያውቅ አይፈልግም ወይም እንዳያውቅና ወደትክክለኛው መንገድ እንዳይገባ የሆነ ፀረ-እውነትና ፀረ-ሰው፣ ፀረ-አምላክም የሆነ የጨለማው ኃይል ዐይኖቹን ጋርዶበታል፡፡ እንጂ በተለይ በዚህ ብዙዎቻችን በምንስማማበት የዓለም መጨረሻ ዘመን ላይ ሆኖ ለሥልጣን ሲል እየሠራው ያለውን ሁሉ ግፍና በደል እንደዚሁም ሰማይና ምድር የማይችሉት የውሸት ድርሳን ስንታዘብ በሰው ልጅ ቂልነትና ለሥልጣን ሲል በሚዘፈቅበት ኢሞራላዊ አረንቋ መደመማችን አይቀርም፡፡ ይህ ውጤቱ ቀድሞ የታወቀ ምርጫ “እከሌ አሸነፈ” ተብሎ መነገሩ ለብዙ ቂላቂሎች የምሥራች ቢመስልም ለብዙዎች ደግሞ የቧልታይ ድንቃይ ድራማ ነው፡፡ ዓለም ይስቅብናል፡፡ በዕውቀታችን ማነስ የማይስቅ ቢገኝ ራሱ ደንቆሮ መሆን አለበት፡፡ “እንኳን አሸነፍክ” ብሎ ለአቢይ የደስታ መግለጫ ደብዳቤ የሚልክ የውጭ መንግሥት ያሳዝነኛል፡፡ እንደዚያ ማድረጉ አንድም ለፖለቲካ ትርፍ አለዚያም ለደምቡ ያህል ወይም ደግሞ – ማን ያውቃል – ሊያላግጥበት መሆን አለበት እንጂ ምርጫው በትክክል ተካሂዶ ፍትሃዊ ውጤት እንደተገኘ አምኖ አይመስለኝም፡፡ 
  7. በዚህ “ምርጫ” “በሰላም መጠናቀቅ” ሳቢያ “ኢትዮጵያ አሸነፈች!” የሚለው የአሸርጋጁና የአሽቃባጩ ብዛት ደግሞ አይጣል፡፡ “ወግ ነው አሉ ሲዳሩ ማልቀስ” ማለት አሁን ነው፡፡ ይህ የፌዝ ምርጫ እንደምርጫ ተቆጥሮ እንዲህና እንዲያ ሲባል ስሰማ በእውነቱ በደረስንበት የዘቀጠ የንቃተ ኅሊና ደረጃ እደነግጣለሁ፡፡  ከራያ እስከ ወገል ጤና፣ ከደምቢዶሎ እስከ ማሻ ጋዜጠኛውም አክቲቪስቱም በአቢይ ማሸነፍ  በብልጽግና መመረጥ አንጀቱ ቅቤ ጠጥቶ በደስታ ጮቤ እየረገጠ ነው፡፡ የሚገርም የታሪክ አንጓ ላይ እንገኛለን፡፡ በዚህ ዘመን መኖር መረገም ነው፡፡ አእምሮን የሚጠቀም ሰው ሲጠፋ የራስህን ጤንነት እስከመጠራጠር ትደርሳለህ፡፡ ያ ዲዮጋን የሚባለው ፈላስፋ በጠራራ ፀሐይ ላይ ፋኖስ ጨምሮ  እውነተኛ ሰው ፍለጋ ገበያ ለገበያ የዞረው ለካንስ ወድዶ አልነበረም! የትናንት አቢይ እንዲህ ሲጫወትብን … ደግነቱ ፈጣሪን ማንም ማታለል አይችልም፡፡ ስለሆነም የቀን ጉዳይ እንጂ አንድዬ ይህን ሁሉ ግራኝ አህመዳዊ ፊንታና አፍዝ አደንግዝ በጣጥሶ ይጥልልናል፡፡ ዋናው ይልቁንስ አጥብቀን እንጸልይ፡፡ መንጌን ወደዚምባዌ ያሽቀነጠረ፣ መሌን በቁሙ ያበሰበሰ ፈጣሪ … ይህንንም በቅርብ ይገላግለናል፡፡
  8. አማራ ይጠንቀቅ እየተባለ ነው፤ እኔም ደጋግሜ ብያለሁ፡፡ በአማራው ላይ ብዙ ፍላጻዎች ተወድረዋል፤ ብዙ ጦሮች ተሰብቀውበታል፡፡ ሱዳን ኢትዮጵያን ወርራ ብዙ መሬት ይዛ ሳለ አንድም ቃል ያልተነፈሰችው አሜሪካ እሰው ጓዳ ገብታ አማራን ከይዞታው ይውጣ እያለች መሆኑ ይሰማል – የሚገርም ጉድ ነው፡፡ “ባለቤቱን ካልናቁ አጥሩን አይነቀንቁ” አትልልኝም ታዲያ? አማራ ሞኝነቱንና “ታጋሽነቱ”ን ዕልባት ካላበጀለት የኅልውና አደጋ ይገጥመዋል፤ በእስካሁኑ አካሄድ ከተራመደ የትም የሚገኝ አማራ እየታደነ የአክራሪ ኦሮሞና የሣልሳይ ወያኔ ጭዳ ይሆናል፡፡ የወያኔ መንሰራራትና ትግራይን መቆጣጠር በተለይ ለአማራው ትልቅ ራስ ምታት ነው፡፡ ወልቃይትንና ራያን ካልወሰድኩ ብለው በሽዎች የሚገመት ጦር ወደ ድንበር እያስጠጉ ናቸው፡፡ በጉልበትና በመንግሥታዊ ማጭበርበር የዘረፉትን የሰው መሬት መልሰን ካልወሰድን ብለው ያዙኝ ልቀቁኝ ማለታቸው እየተሰማ ነው፤ የሚጠበቅም ነው፡፡ ወያኔዎች የሚነዱት በምክንያት ሳይሆን እልህ በተሞላበት ዲያቢሎሳዊ የስሜት ፈረስ በመሆኑ ይህ ሁኔታቸው አይገርምም፡፡ “ካላበዱ ወይ ካልነገዱ የልብ አይገኝም” እንደሚባለው ወያኔዎች ለይቶላቸው ስላበዱ ለዓላማቸው ስኬት መላ ትግራይንና ሕዝቧን መስዋዕት አድርገውም ቢሆን መታገላቸው አይቀርም፡፡ ደግሞም የበሰበሰ ዝናብ አይፈራም፡፡ የሚጎዳው ዐርፎ ተቀምጦ የነበረው አማራ እንጂ እነሱ አይደሉም፡፡ እነሱማ ዱሮውን መዓት ወርዶባቸው አንዴ በመከላከያ ሌላ ጊዜ በኢሳይያስ ጦር፣ አንዴ በአማራ ልዩ ኃይል ሌላ ጊዜ በውስጣዊ ችግር በሠፈሩት ቁና ተሰፍረው አሁን ከምንም በታች ሆነዋልና ምን ያስፈራቸዋል? ምንም፡፡ ስለሆነም ተስፋ በመቁረጣቸውና በዚያም ምክንያት አእምሯቸውን በመሳታቸው አንዲት ጥይትና አንድ ሰው እስኪቀራቸው አማራን መፋለማቸው የማይቀር ነው፡፡
  9.  ከዕብድ ጋር የሚዋጋ ኃይል ዕዳው ብዙ ነው ወንድሜ፡፡ ዕብድን ለማሸነፍ ከዕብዱ መብለጥ አለብህ – አንድም በኃይል አንድም በጥበብ፡፡ መናቅ ግን ያስጠቃሃል እንጂ በፍጹም አይጠቅምህም፡፡ ማሰብ የሚችል ማሰብ ከማይችል ጋር ሲዋጋ፣ ተስፋ አለኝ የሚል ኃይል ተስፋቢስ ከሆነ አካል ጋር ሲፋለም ችግሩ ብዙና ግልጽም ነው፡፡ ሥራ ያስፈታሃል፤ አቅምህን ይፈታተነብሃል፤ የትኩረት አቅጣጫህን ያዛባብሃል፡፡ እርሱ እንደሆነ አንዴውኑ ተስፋ ቆርጧልና ባለ በሌለ ኃይሉ ውፈር ተበገስ ብሎ ነው የሚዘምተው – በዚያ ላይ የሀሽሹና የአእምሮ ማዛቢያው ንጥረ ነገር አይረሳም፤ የዕብድ ገላጋይ ድንጋይ አቀባዮችም ሞልተዋልና ጸረ አማራ ሁሉ የየአቅሙን አስተዋፅዖ ማድረጉም የሚጠበቅ ነው፡፡ ለዚህ ነው ከተጋሩ ይልቅ አማራው ይበልጥ የሚቸገረው በዚህ ጦርነት፡፡ አልቃኢዳና አልሻባብ ድል የሚቀናቸው መሞትንም ማሸነፍንም እንደድል ቆጥረው ወደ ጦርነት ቀጣና ስለሚገቡ ነው – ገባህ? አማራው ብዙ ዕዳ እንደሚከፍል የሚጠበቀው እንግዲህ እነዚህ ወያኔዎች ሙሉ ጊዜያቸውንና አቅማቸውን በውጊያ ላይ ለማዋል ስለቆረጡ ነው፡፡ ወያኔዎች ሕዝቡን አሳብደውታል፤ ብቻቸውን ማበዳቸው ብዙም እንደማያዋጣቸው ያወቁት ትህነጎች ከመነሻቸው ጀምሮ ትግሬን ከወያኔ ጋር ለማቆራኘት ያደረጉት ጥረት መና አልቀረም፡፡ ስለዚህ “ከጠፋን ተያይዘን እንጠፋለን እንጂ ማን ቆሞ ማን ይተኛል?” ከሚል ቀቢፀ ተስፋ አብሯቸው የሚሰለፈው ትግሬ የትዬለሌ ሆኗል፡፡ መሀል አዲስ አበባ የተንቀባረረ ኑሮውን ትቶ፣ መሀል ዋሽንግተን ዲሲ የዘነጠ ኑሮዋን ትታ ወደ ደደቢት በረሃ የሚዘምቱበት ዕንቆቅልሽ ሌላ ሳይሆን የወያኔ የትግሬ የበላይነት ተዛነፈ የሚል ስብከት ያስከተለው የሥነ ልቦና ደዌ ነው፡፡ ዘረኝነት እስከዚህ ያሳብዳል፡፡ ለኢትዮጵያና ለኢትዮጵያውያን የጋራ ሕይወት የሚሰለፍ ሃቀኛ ትግሬ ቁጠር ብባል በበኩሌ ፕሮፌሰር መስፍን ወ/ማርያም አንድ ወቅት እንዳሉት አሥር ያህል እንኳን የምቆጥር አይመስለኝም፡፡ ግዴለም ይህን ቁጥር በ“ቸርነቴ” ሰፋ ላድርገውና አንድ መቶ ትግሬዎች ምናልባት ወያኔን ተቃውመው ወይም ባይቃወሙም ገለልተኛ ሆነው ከሚያዋጣን የጋራ ኢትዮጵያዊነት ጋር በሂደት ሊሰለፉ ይችላሉ ብለን ብንገምት የተቀረውን ግን ወያኔዎች በስስ ብልቱ ገብተው ስለታላቋ ትግራይ ስለሰበኩት አለያይተውናል፤ ስለዚህም መጨረሻችን በእጅጉ አሳሳቢ ነው፡፡ ይህን ታሪካዊ  ዘግናኝ እውነት ለመቀልበስና የጥንቷን ኢትዮጵያ ለማምጣት የሚፈጀው ማገዶ ይታያችሁ፡፡ አሁን እኮ በትግራይ የኢትዮጵያ ባንዲራ አትውለበለብም፡፡ ሌላው ይቅርና ኢትዮጵያን በፍቅር የሚያወሳ ትግሬ እኮ  መሀል ግምባሩ በጥይት ይበረቀሳል፡፡ መግደልን የሁሉም ችግር መፍትሔ አድርገው የወሰዱት ወያኔዎች በትግራይ ምድር ብዙ ወንድምና እህቶቻችንን እያሳጡን ነው እኮ በዚህች ቅጽበት፡፡ 
  10. ቤተ እምነቶቻችን ጤነኛ ቢሆኑ ኖሮ አሁን ብሔራዊ ምህላ ታውጆ በጸሎትና ምህላ መጠመድ ነበረብን፡፡ ግን አጋንንቱ ቤተ መንግሥቱን ብቻ ሳይሆን ቤተ አምልኮዎቻችንንም ስለተቆጣጠሩት ለዚያ አልታደልንም፡፡ የሃይማኖት መሪዎች በዓለም ሲዋጡ፣ የሃይማኖት እረኞች በደራ የሥጋ ገበያ ሲወሰዱ የሚፈጠረውን አስጠሊታ ድራማ ማየት የሚፈልግ ሰው ቢኖር የአሁኒቷን  ኢትዮጵያ ማየት ነው፡፡ በሁሉም ጠፍተናል፡፡ ወይ መዓልቲ!
Filed in: Amharic