>

ዳግማዊ ጦርነት ታወጀ:- "አረም በደቦ ነው የሚነቀለው...!!!" (ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ አህመድ)

ዳግማዊ ጦርነት ታወጀ:-

“አረም በደቦ ነው የሚነቀለው…!!!”
ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ አህመድ

 

ጁንታው ያገኘውን የፖለቲካ ሥልጣን የገዛ ሀገሩን ለማፍረስ የተጠቀመ ምናልባት በታሪክ ብቸኛው ቡድን ነው አሉ ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ አህመድ፡፡
አብሮ የኖረ ሰይጣን በቶሎ አይነቀልም እንደሚባለው በግራ በቀኝ መፍጨርጨሩ አይቀርም ያሉት ጠቅላይ ሚንስትሩ በርግጠኝነት ግን ጁንታው መልሶ እንዳይበቅል ሆኖ ይነቀላል ብለዋል።
ይህ የሚሆነው ሁላችንም እንቦጩን ለመንቀል ከተረባረብን ነው። በሂደቱ ውስጥ እዚህና እዚያ ግለሰቦች ሊሳሳቱ ይችላሉ።
ሐሳብ የሚከፋፍሉ መረጃዎች ሊሰሙ ይችላሉ። በግብ አንድ ሆነን የአካሄድ ክርክር ይፈጠር ይሆናል።
ያም ሆነ ይህ ከግባችን አያናጥበንም። የኢትዮጵያ ልጆች ከአራቱም ማዕዘን የጁንታውን ዕቅድ ለመቀልበስ ተነሥተዋል። ይህ በራሱ ድል ነው።
የኢትዮጵያ ልጆች ጠላታቸው ማን እንደሆነ ለይተውታል። እርሱንም ምን ማድረግ እንዳለባቸው ዐውቀዋል። ያንንም ያደርጉታል። ይህ አንድነታችን ያስፈራቸው ኃይሎች የሚከፋፍል የመሰላቸውን ነገር ሁሉ ያደርጋሉ።
ዓይነ መዓታችንን ከእነርሱ ላይ አንሥተን በገዛ ወገኖቻችን ላይ እንድንተክል ያሤራሉ።
ፈጽሞ አናደርገውም።
አሁን የፈጠርነው አንድነት የጁንታውን የጥንት ሤራ ያፈረሰ፤ ቀጥሎም የሤራውን ባለቤት የሚያፈርስ፤ በመጨረሻም የተሤረባትን ሀገር በአንድነት የሚያድስ ነው።መከላከያ ኃይላችንና የክልል ኃይሎቻችን ተገቢውን ቦታ እየያዙ ነው። ያንን ለማወክ ትንኮሳ ይኖራል። ለዚያ ለራሳችን ቃል የገባነውን የተኩስ አቁም እያከበርን ተገቢውን ምላሽ ይሰጠዋል።
ምንን፣ ለምን፣ እንዴት፣ የትና መቼ ማድረግ እንዳለብን ጥብቅ ዕቅድ አለን።
ውጤቱን በጥቂት ጊዜ ውስጥ ወዳጅም ጠላትም ያየዋል። ሠራዊታችን አስፈላጊ ሲሆን እጅን በአፍ ላይ ለሚያስጭን ተልዕኮ ተዘጋጅቷል።
አረሙ እንዲነቀል አድርገን እንሠራለን ያሉት ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ አረሙን ስንነቅል ግን ስንዴውን እንዳንጎዳው የሚቻለውን ሁሉ ጥንቃቄ እናደርጋለን ነው ያሉት።
በሀገራችን አረም በደቦ ነው የሚነቀለው፤ የኢትዮጵያ ልጆችም እርሱን እያደረጉት ነው

Filed in: Amharic