>

የችሎት ክለሳ....!!! (ጌጥዬ ያለው)

የችሎት ክለሳ….!!!

ጌጥዬ ያለው

የፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 1ኛ የጸረ ሽብርና ሕገ መንግሥታዊ ጉዳዮች ወንጀል ችሎት ዛሬ ጥቅምት 9 ቀን 2014 ዓ.ም. የእነ እስክንድር ነጋን መዝገብ ቁጥር 260175 ገልጦ የይስሙላ ክርክሩ ቀጥሏል። ባለፈው ጥቅምት 5 ቀን በተቀጠረው መሰረት ዐቃቤ ሕግ በግልፅ ችሎት እንዲያቀርባቸው የታቀዱ ምስክሮች ስም ዝርዝር ለመገናኛ ብዙሃን፤ በተለይም ከሳሽ እንደ እንኩሽ በሚፈራው ፌስቡክ ይገለፅ ወይስ ድብቅ ይሁን በሚል ጭብጥ ተከራክረዋል። ባለፈው ጊዜ ከችሎት የጠፉት ዳኛ ዛሬ ተሰይመዋል። ከጧት በተደረገው ክርክር ላይ ብይን ለመስጠት ለዛሬ ከቀትር በኋላ 8:30 ችሎቱ ተመልሶ እንዲሰየምም ተቀጥሯል።
ዐቃቤ ሕግ የዘጠኝ ምስክሮችን ስም ዝርዝር ለዳኞች፣ ለጠበቆች እና ለኀሊና እስኞች እስክንድር ነጋ፣ ስንታየሁ ቸኮል፣ አስቴር ስዩም እና አስካለ ደምሌ የሰጠ ሲሆን በመገናኛ ብዙሃን ይገለፅ ወይም አይገለፅ የሚለው ጭብጥ በቀጣዩ ችሎት ይወሰናል። ዐቃቤ ሕግ ቀሪ 11ዱ ምስክሮች በግልፅ ችሎት ለመቅረብ ፈቃደኛ እንዳልሆኑለት እና እያግባባቸው እንደሆነ ተናግሯል። ፈቃደኛ ከሆኑ እንደሚያቀርብ ካልሆኑ ግን ማስመስከር እንደ ማይችልም ተናግሯል።
የእነ እስክንድር ነጋ ጠበቆች ሔኖክ አክሊሉ፣ ቤተማርያም አለማየሁ እና ሶሎሞን ገዛኸኝ በበኩላቸው ጉዳዩን በመቃወም ተከራክረዋል። በተለይም በወንጀለኛ መቅጫ ስነ ስርዓት ሕጉ ቁጥር 124 እና ቁጥር 136 መሰረት ዐቃቤ ሕግ “ምስክሮቼ ፈቃደኛ ከሆኑ አቀርባለሁ፤ ካልሆኑ ግን አላቀርብም” ማለቱ ስህተት እንደሆነ እና ባልተረጋገጠ አማራጭ ያቀረበው አቤቱታ ቅቡልነት ሊኖረው እንደ ማይገባ ገልፀዋል።
በሕጉ መሰረት ሁሉም ምስክሮች ተጠቃለው በመጀመሪያው ቀን መቅረብና በስነ ስርዓቱ መሰረት ቃለ መሀላ ፈፅመው ችሎቱ በሚሰጣቸው ቅደም ተከተል እማኝነታቸውን መስጠት እንዳለባቸው አስረድተዋል።
እያስፔድ አበጀ የተባለ ዐቃቤ ሕግ በበኩሉ የወንጀለኛ መቅጫ ስነ ስርዓት ሕጉ ያልተሟላ  መሆኑን ጠቅሶ ፍርድ ቤቱ ጥያቄውን እንዲቀበል አስረድቷል። ይህም ባልተፃፈ ሕግ እንዲፈርዱ መጠየቅ ነው። ለእነ እስክንድር ነጋ ሀሰተኛ የሽብር ክስ ሲባል አዲስ ሕግ እንዲዘጋጅ ወይም በጠበቆች የተጠቀሰው የወንጀለኛ መቅጫ ስነ ስርዓት ዐቃቤ ሕግ በእነ እስክንድር ላይ የቀረበውን ክስ ለማስረዳት በሚያመቸው መልኩ እንዲሻሻል ምክረ ሃሳብ ያቀረበበት ጥያቄም ይመስላል። ዐቃቤ ሕግ ይህንን ሲል እርሱ እራሱ ሕጉን የመፍጠርም፣ የማፅደቅም፣ የመሻርም፣ የማሻሻልም መብት እንዳለው በሚያስረዳ መንፈስ ነበር። የመገናኛ ብዙሃን የችሎት አዘጋገብን በተመለከተም በሕጉ የተቀመጠው ገደብ በቂ እንዳልሆነ ገልጿል።
በመሆኑም ከፍሬ ክርክሩ ውጭ ከካድሬ ስልጠና የሚመሳሰል ሰፊ ንግግር አድርጓል። እስክንድር ነጋ ተቃውሞ እንዳለው ጠቅሶ በመነሳት “ሌክቸር ነው እየተሰጠን ያለው” በማለት ባያስቆመው ኖሮ የእያስፔድ አበጀ ንግግር የሚቋጨው ዳኞችን እና ጋዜጠኞችን ‘ሂሳችሁን ዋጡ!’ በማለት ሳይሆን አይቀርም ነበር።
በዚህ ችሎት አመቱን ሙሉ እስከ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት ድረስ ሲያከራክር ከርሞ ለዚህ መዝገብ ጥቅም ላይ አይውልም ተብሎ የተዘጋው የምስክሮችና ጠቋሚዎች ጥበቃ አዋጅ ቁጥር 699/2003 በድጋሜ  ተመልሶ ለክርክር ቀርቧል። ነሐሴ 10 ቀን 2013 ዓ.ም. ሰበር ሰሚ ችሎቱ በሰጠው ብይን መሰረት ለምስክሮች በችሎቱ የሚደረግ ጥበቃ እንደሌለ መወሰኑን ያስታወሱት ዳኞች ዐቃቤ ሕግ ተመልሶ እንደ አዲስ ለክርክር እንዲያቀርበው ግን ፈቅደውለታል።  በመሆኑም የክርክር ሂደቱ እየተከለሰ ይገኛል።
በወንጀለኛ መቅጫ ስነ ስርዓት ሕጉ ቁጥር 184 መሰረት ይግባኝ የሚጠየቀው ተጠቃሎ ብይን ከተሰጠ በኋላ ቢሆንም ሕገ ወጡ ዐቃቤ ሕግ ለጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት እና ሰበር ሰሚ ችሎት አቤት እንዲል ተፈቅዶለት የፍርድ አሰጣጥ ሂደቱን ከአንድ ዓመት በላይ ሲያንቀራፍፍ ከርሟል። አሁን ደግሞ በአዲስ ዳኞች ችሎቱን እየደገመው ይገኛል።
እንደ ሌሎች ችሎቶች ሁሉ የዛሬው ችሎትም ወታደራዊ ነበር። ታዳሚው ተወደረ ስናይፐር እና በአስለቃሽ ጭስ ጭምር አዳራሽ ውስጥ እየተጠበቀ ታድሟል።
ስንታየሁ ቸኮል በፖሊስ ታጅቦ ከእስር ቤት ውጭ በሚገኝ ሆስፒታል በግሉ ወጭ እንዲታከም ባቀረበው ጥያቄ ላይ ምላሹን እንዲሰጥ ቂሊንጦ ወህኒ ቤት ችሎት የተጠራ ቢሆንም ሳይቀርብ ቀርቷል።
Filed in: Amharic