>
5:13 pm - Monday April 19, 9109

"ማረሚያ ቤት እነ እስክንድር ነጋን ችሎት ሳያቀርብ ቀረ...!!!   (ሰለሞን አላምኔ)

“ማረሚያ ቤት እነ እስክንድር ነጋን ችሎት ሳያቀርብ ቀረ…!!!  
ሰለሞን አላምኔ

*…. የዛሬው ችሎት ዜና 16.03.2014 ሐሙስ
 
 በመደበኛ የተቀጠረው የእነ እስክንድር ነጋ የክስ መዝገብ በዛሬው ችሎት ኅዳር 16 እና 17 ቀን 2014 ዓ.ም የከሳሽ ዐቃቤ ሕግ ምስክሮች ቀርበው ምስክርነታቸውን እንዲሰጡ አስቀድሞ የተያዘው ቀጠሮ ፤ በማረሚያ ቤተ አስተዳደር ምክንያት የፍርድ ቤቱ መዝገብ  ሳይገለጥ ችሎቱ ተነሳ።
የፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 1ኛ የጸረ ሽብርና ሕገ መንግሥታዊ ጉዳዮች ወንጀል ችሎት አስቀድሞ በያዘው ቀጠሮ መሠረት ምስክሮች መቀረባቸውን የጠየቀ ቢሆንም ፦ ዐቃቤ ሕግ በጽሁፍ ለችሎቱ አቤቱታ ያቀረበ ሲሆን ፤ ያቀረበው “አቤቱታውን ችሎቱ የሚያነበው እና ለተከሳሽ ጠበቆች የሚደርስ ከሆነ በዝግ ችሎት ይታይልኝ ” በማለት ዐቃቤ ሕግ ለፍ/ቤቱ ምላሽ ሰጥቷል ።
በተጨማሪ እነ እስክንድር በችሎት አለመገኘታቸውን በተመለከተ ፤ የማረሚያ ቤት አስተዳደር ተወካይ የሆኑት  ” ሸዋ-ሮቢት ያሉ እስረኞችን ወደ ዝዋይ ማረሚያ ቤት በመውሰድ እያደራጀን ነው። በዚህም ምክንያት የማረሚያ ቤት ፖሊሶች በግዶጅ ስምሪት ላይ በመሆናቸው እነ እስክንድርን ለችሎቱ ለማቅረብ የተቸገርን በመሆኑ እረዥም ቀጠሮ ተሰጥቶን በሌላ ጊዜ ይዘን እንቅረብ” በማለት ለፍ/ቤቱ በፅሁፍ እና በቃል ምላሽ ሰጥተዋል ።
በዐቃቤ ሕግና በማረሚያ ቤት የቀረቡ ምክንያቶችን አስመልክቶ የተከሳሾች ጠበቆች ” የማረሚያ ቤት ‘ፖሊሶችን ወደ ዝዋይ ስለወሰድኳቸው’ ረጅም ቀጠሮ ይሰጠን ብሏል። የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ዛሬ ሌሎች እስረኞችን ፍርድ ቤት አቅርቧል ። እነ  እስክንድር  ከሌሎች እስረኞች የሚለዩበት ምንም ምክንያት የለም። በሌላ በኩል  “አደራጅቼ እስክጨርስ” ብሏል። መቼ አደራጅቶ እንደሚጨርስ በአግባብ የታወቀ ነገር የለም ። በዚህ ጊዜ ብሎ ያሳወቀው ቀን የለም። እነ እስክንድር  የእረጅም ግዜ ታሳሪዎች ናቸው።  ለተጨማሪ ጊዜ መጉላላት የለባቸውም። አጃቢዎች ተመድበው እንዲመጡ እንጠይቃለን። በማረሚያ ቤት የቀረበው ምክንያት በቂ እና ሕጋዊ ባለመሆኑ ውድቅ መደረግ አለበት።” በማለት በማረሚያ ቤት ለቀረበው አቤቱታ ምላሽ ሰጥተዋል ።
 ከዚሁ ጋር በተያያዘ ዐቃቤ ሕግ በጽሁፍ ላቀረበው ” ምስክሮች በመጋረጃ ጀርባ ይሰሙ”  አቤቱታ በተመለከ በጠበቆች በኩል ” በባለፈው ችሎት ዐቃቤ ሕግ ለፖሊስ አድራሻ እንዲሰጥ እና ፓሊስ መጥሪያ አድርሶ፤ ምስክሮች በፍርድ ቤት መጥሪያ እንዲቀርቡ ታዟል። በመደበኛ የምስክር አሰማም ሂደት ከዚህ ቀደም 6 ምስክሮች ቀርበው በግልጽ ችሎት ምስክርነታቸውን ሰጥተዋል ። አሁን የተለየ ምንም ነገር የለም ፤ በዚህ ጉዳይ ከዚህ በፊት የተከራክረንበት የተዘጋ ጉዳይ ነው። ታዳሚ በተገኘበት በግልጽ ችሎት የምስክር መሰማት ሂደት መቀጠል አለበት ፤ ፍርድ ቤቱ በጀመረው አካሄድ እንዲቀጥል ” እንጠይቃለን ብለዋል ።
የግራ እና የቀኙን ክርክር የሰማው ፍርድ ቤቱ የማረሚ ቤት አስተዳደር ‘ኮማንደር አስቻለው መኮንን’ በነገው ዕለት ኅዳር 17 ቀን 2014 ዓ.ም ፍርድ ቤት በመቅረብ ከእነ እስክንድር አቀራረብ ጋር በተያያዘ ማብራሪያ እንዲሰጡ ፍ/ቤቱ ትዕዛዝ ሰጥቷል ።
ፍርድ ቤቱ በዐቃቤ ሕግ በኩል የቀረበውን  ‘የዝግ የምስክር አሰማም አቤቱታ’ን  ውድቅ በማድረግ በዛሬው ዕለት የቀረቡት የዐቃቤ ሕግ ምስክር ወደ ችሎት አዳራሽ እንዲገቡ እና ስማቸው እንዲያስመዘግቡ አድርጓል። በቀጣይ ቀጠሮ ምንም አይነት መጥሪያ ሳይደርሳቸው ወይም መጥሪያ ሳይጠብቁ ከዐቃቤ ሕግ ጋር በመነጋገር በችሎት እንዲገኙ ጥብቅ ትዕዛዝ ፍ/ቤቱ ሰጥቷል ። በዛሬ ዕለት የዐቃቤ ሕግ ምስክር ነኝ በማለት ቀረበው የነበሩት  እና ከሌሎች ምስክሮች በተለይ በዝግ እንዲመሰክሩ በዐቃቤ ሕግ ከለላ የተጠየቀላቸው ምስክር ‘አቶ  ጌትነት ተስፋዬ’ ናቸው።
በዛሬው ችሎት የባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራ ፓርቲ አባላትና ደጋፊዎች ፣ የእነ እስክንድር ወዳጆች፣ የሰብዓዊ መብት ተቋማት ተወካዮች እና ጋዜጠኞች የተገኙ ሲሆን ፤ አርቲስት እና የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ታማኝ በየነም የችሎቱ ታዳሚ ነበር።
Filed in: Amharic