>

እንኳን ለኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል አደረሳችሁ......!!! ዶ/ር አብይ አህመድ

እንኳን ለኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል አደረሳችሁ……!!!

ዶ/ር አብይ አህመድ

የዘንድሮውን የልደት በዓል የምናከብረው የመከራችን ዘመን እያከተመ፣ የችግራችን ቋጠሮ እየተፈታ፣ የሰቆቃችን ምንጭ ላይመለስ እየደረቀ ባለበት ወቅት ነው። መከራችንን ከኋላችን ጥለን ተስፋችንን አሻግረን እያየን የምናከብረው በዓል ነው።
የክርስቶስ ልደት የአዲስ ተስፋ ጅማሬ የብሩህ ዘመን ማብሠሪያ ነው። የጭንቁ ጊዜ እያለፈ መሆኑ፣ የመከራው ዘመን እየተገባደደ መምጣቱ፣ ጨለማው በብርሃን መሸነፉ፣ የኃጢአት እሥር አብቅቶ ነጻነት መቅረቡ የተበሠረበት ነው። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከመወለዱ በፊት የነበረው ዘመን ዓመተ ፍዳ ነበር። ሰው የፈጣሪውን መመሪያ ተላልፎ የተከለከለውን በመፈጸሙ ምክንያት፣ ርግማን ወርዶበት ከገነት ተባርሮ የኖራቸው እነዚያ ዘመናት፣ በድቅድቅ ጨለማ የተሞሉ ነበሩ። ጊዜው ደርሶ ክርስቶስ በቤተልሔም ሲወለድ፣ የኩነኔው ዘመን በሥርየት ተለውጦ የምሕረት ዘመን ተብሏል።
የሰው ልጅ ድኅነት በጽንሰት ተጀመረ፣ በልደት ተበሠረ፣ በስቅለት ተፈጸመ፤ በትንሣኤ ተደመደመ። እያንዳንዱ ምእራፍ በፈተናና በደስታ ነበር የታለፈው። የክርስቶስ ልደት የምሕረት ጊዜ መቅረቡን እንጂ ሁሉም ነገር መጠናቀቁን አላበሠረንም። ዕለተ ስቅለቱ ደርሶ አዳም ከዲያብሎስ ባርነት፣ ከኃጢአት ቀንበር ነጻ እስከወጣበት ጊዜ ድረስ፣ በመንገዱ ብዙ ውጣ ውረዶች አጋጥመዋል። የሄሮድስ የሞት ዐዋጅ፣ ስደት፣ እንግልት፣ ረሃብ፣ ጥማት፣ ነበረ።
ጠላታችን ዲያብሎስ በማይታክት ተንኮሉ አዳምን እስከ መጨረሻው ከፈጣሪው አቆራርጦ ለማኖር ከጽንሰቱ እስከ ስቅለቱ ያልፈነቀለው ድንጋይ፣ ያልፈጸመው ሤራ አልነበረም። ጭፍራዎቹን አሠማርቶ ብዙዎች ከእውነት ጋር እንዳይቆሙ አድርጓል። ሐሰትን እየፈበረከ የክርስቶስን ስም እንዲያጠፉ አድርጓል። ብዙዎች ወደ ክርስቶስ እንዳይሄዱ ተከታዮቹን አስፈራርተዋል። ወደ ክርስቶስ የመጡትን ትታችሁ ውጡ ብለዋል። ሐዋርያትን ጭምር በገንዘብ አስክደዋል። የውጭ ጠላቶች ሮማውያን፣ ከውስጥ ባንዳዎች አይሁድ ጋር አንድ ሆነው ክርስቶስን አሳድደዋል።
የኢትዮጵያ ጠላቶችም ሊወለድ ያለውን ተስፋችንን ሊያጨነግፉ ለዓመታት ታግለዋል። ሲጸነስ ሊያጨናግፉት ሞክረው ነበር። መወለዱን ሲያውቁ ያልፈጸሙት የግፍ ዓይነት የለም። ግጭቶችን እየጠመቁ ሕዝብን ከሕዝብ ሲያጋጩ፣ በየደረሱበት ንጹሐንን ሲያፈናቅሉና ከሕጻናት እስከ አዛውንት ያገኙትን ሲያሰቃዩና በጭካኔ ሲገድሉ ነበር። የሀገራችን የመዳንዋ ጊዜ የማይመጣ እስኪመስል ድረስ መከራችን በዝቶ ታይቷል። እንደ ሄሮድስ ያሉ አበጋዞች ብሩህ ተስፋችንን ሊያጨልሙ ባለ በሌለ ጉልበታቸው ታግለዋል። አንድነታችንን ሊንዱ ተባብረዋል፤ ሀገራችንን ሊያፈርሱ እስከ ሲኦል ለመውረድ ምለዋል። ኢትዮጵያ በዚያ ሁሉ መከራ ውስጥ አልፋ እዚህ ደርሳለች። የተረገዘው የለውጥ ጽንስ ተወልዶ እያደገ ነው። ኢትዮጵያም በሚወረወሩባት ፍላጻዎች ድልድዮችን እየገነባች፣ ተስፋዋን ለመፈጸም ከመጓዝ ያገዳት የለም።
ውድ ወገኖቼ፣
ሰው በሕይወቱ እጅግ ወሳኝ ከሆኑ ቀናት መካከል ሁለቱ፣ የተወለደበትና ለምን እንደተወለደ ያወቀበት ቀናት ናቸው ይባላል። ሁላችንም ያለ አንድ ዓላማ አልተፈጠርንም። አንቱ የምንላቸው ቀደምቶቻችን አንቱ ያስባላቸው ጉዳይ ለምን እንደተወለዱ ማወቃቸው ነው። ኢትዮጵያዊ ሆነን መወለዳችን ያለ ምክንያት እንዳልሆነ አስበን ሀገራችንን ከጥገኝነት የሚያላቅቅ፣ ወገናችንን ከድህነት አዙሪት የሚገላግል፣ ኢትዮጵያን ወደ ብልጽግና ጎዳና የሚያስገባ፣ ኢትዮጵያ ራሷን በሁሉም ነገር ችላ እንድትቆም የሚያደርግ፣ አንድ ቁም ነገር ሠርተን ማለፍ አለብን።
ለዚህ ደግሞ ከአሁን የተሻለ ጊዜ የለም። አሁን የምንገኝበት ወቅት ከትውልድ ወደ ትውልድ ሊሸጋገር የሚችል አንጸባራቂ ገድል የሚሠራበት፣ በኩራት የሚነገር ታሪክ የሚጻፍበት ወሳኝ ወቅት ነው።
የኢትዮጵያ ቀን ሊነጋ ጽልመቱን ሰንጥቆ ጉዞ ጀምሯል፣ ጀንበሯ ደምቃ ልትወጣ ከጨለማው ጋር ትግል ላይ ናት። በዚህ ወሳኝ ወቅት ሁላችንም ዐቅማችን የፈቀደውን መሥራት ከቻልን፣ ያለ ጥርጥር የኢትዮጵያ ነገ ብሩህ ይሆናል፤ የመከራ ዘመንዋ እስከ ወዲያኛው ይሸኛል። ኢትዮጵያም የማትደፈር፣ የምትታፈር ሀገር ሆና በዐለት ላይ ትቆማለች።
ኢትዮጵያን ለማገልገል ስንነሣ ልብ ማለት የሚገባን ነገር አለ። የሰነቅነው ዓላማ የቱንም ያህል የገዘፈና የተቀደሰ ቢሆን፣ ትኅትና ካልታከለበት ትርጉም የለውም። ታላላቅ ግቦች ፍጻሜያቸው ብቻ ሳይሆን አፈጻጸማቸውም ታላቅና አስደናቂ ነው። የክርስቶስ ልደትም የሚያስተምረን ይሄን ነው። ዓለምን ለማዳን እግዚአብሔር አንድያ ልጁን ለታላቅ ዓላማ ሲልከው፣ ከታላላቅ ሰዎች ይልቅ እረኞችን፤ ከታዋቂዎች ይልቅ ከብቶችን፤ በጌጣጌጥ ከተንቆጠቆጡ እልፍኞችና ቤተ መንግሥቶች ይልቅ በረትን መረጠ። ዓለምን ማዳንን ያህል ታላቅ ሥራ በትኅትና ነው የተፈጸመው። ታላላቅ ግቦች በትኅትና ተጀምረው፣ በትኅትና የሚጠናቀቁ መሆናቸውን መድኃኔዓለም ክርስቶስ አስተምሮናል።
ዛሬ በኃይልና በትዕቢት ተወጥረን የምንጀምራቸውና “በእኔ ዐውቅልሃለሁ” ስሜት ተኮፍሰን የምንሠራቸው ሥራዎች ዘላቂ እድሜ ሊኖራቸው አይችልም። ከድሃው ሕዝብ ርቀን፣ በጌጣጌጥ በተንቆጠቆጡ ቢሮዎች ውስጥ ተቆልፈን፣ በዘመናዊ መኪኖች ተንፈላስሰን የምንወጥናቸው ዕቅዶች ቢተገበሩም ቆይተው ይፈርሳሉ። በተቃራኒው ወደ ታች ወርደን ከሕዝቡ ጋር የነደፍናቸው ግቦች፣ ጀምረን ባንጨርሳቸው እንኳን፣ ትውልድ ተረክቦ ከዳር ያደርሳቸዋል።
ሌላው የልደት በዓል በሕዝበ ክርስቲያኑ ዘንድ የእርቅ ምልክት ተደርጎም ይታሰባል። በፈጣሪና በአዳም መካከል የጸብ ግድግዳ የፈረሰው መጀመሪያ በቃሉ ነበር፤ “ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ” በሚል ቃል። የክርስቶስ መወለድ ቃሉ ወደ ተግባር መለወጡን፣ የእርቁን አይቀሬነት አሳይቷል። በዲያቢሎስ ገፋፊነት ሕግ የጣሰው፣ በደል የፈጸመው አዳም ሆኖ ሳለ ለእርቅ ልጁን አሳልፎ የሰጠው ግን ፈጣሪ ነው። አዳምን ለማዳን፣ ከሐጥያት ቀንበር ለማላቀቅ ክርስቶስ ሰው ሆኖ በሥጋ በመወለዱ ክብሩ ጨመረ እንጂ አልቀነሰም።
በየዘመናቱ በሚነሱ የዲያቢሎስ ጭፍሮች አሳሳችነት በሀገራችን ግጭቶች ተፈጥረው ያውቃሉ። ግጭቱን ተከትሎ የሚወረወረው የበደል ሥለት አብረው የሚያኖሩ እሴቶቻችንን ሊበጥስ ታግሏል። ነገር ግን ጨርሶ አልቆረጣቸውም። ማህበራዊ እሴቶቻችን በይቅርታ እየታሹ፣ በእርቀ ሰላም ተጠግነው ወደ ቦታቸው ይመለሳሉ። እስከ አሁንም ሀገር አድርጎ ያቆየን ይሄ ሂደት ነው።
ጁንታው መከላከያ ሠራዊታችን ላይ የፈጸመውን ጥቃት ተከትሎ ባለፈው አንድ ዓመት ውስጥ የተፈጠረውን ግጭት ጨምሮ በሌሎች ምክንያቶች በሀገራችን የተፈጸሙ መበዳደሎችን ለመሻር በዚህ ሰዓት ሀገራዊ እርቀ ሰላም ያስፈልገናል። አንድነታችንን ለማስጠበቅ ስለሚያስችለን፣ በእርቀ ሰላሙ ኢትዮጵያ አትራፊ እንደምትሆን እሙን ነው። በሰውና በፈጣሪ እርቅ ምክንያት የከሠረው አሳሳቹ ዲያብሎስ እንደሆነው ሁሉ፣ በሀገራችን እርቀ ሰላም ምክንያት የሽብር ቡድኖቹ የሕወሃትና የሸኔ እኩይ ዓላማ፣ እንዲሁም የታሪካዊ ጠላቶቻችን ሕልም ይከሽፋል።
በድጋሚ መልካም የልደት በዓል ይሁንልን።
ኢትዮጵያ በልጆቿ ጥረት ታፍራና ተከብራ ለዘላለም ትኑር!! ፈጣሪ ኢትዮጵያና ሕዝቦቿን ይባርክ!
ታኅሣሥ 28 ቀን 2014 ዓ.ም.
Filed in: Amharic