>

 የእምቧይ ካብ (አገሬ አዲስ)

 የእምቧይ ካብ

    አገሬ አዲስ      


                        

እምቧይ ሳይዘሩት የሚበቅል ሲያዩት እንደሌሎቹ ወፍ ዘራሽ ፍራፍሬዎች እራብ የሚያስታግስ ፣ሰውነትን የሚጠግን ከበሽታም የሚከላከል ንጥረነገር ያለው የምግብ ዘር፣ ቲማቲም ወይም ኮክና ሌሎቹን  ጣፋጭና ጠቃሚ የሆኑትን ፍራፍሬዎች ይመስላል።ቀርበው ሲፈትሹት ግን  ከተጠቀጠቀበት ጎምዛዛ ፈሳሽ በቀር እርባና የሌለው፣ቢበሉት ለጤና ጠንክ የሆነ አሳሳች እጽዋት ነው።እምቧይ ሊበሉት ቀርቶ አንድ ላይ አስቀምጠው፣ወይም ቆልለው እንደ ግንብ ወይም አጥር ነፋስ ልከላከልብህ ቢሉት የማይቀመጥና ባለበት የማይረጋ፣በትንሽ እንቅስቃሴ ወይም ንፋስና ንክኪ የሚናድና የሚንከባለል ፣ለክፉ ቀን የማይሆን መልኬ በቃኝ ድቡልቡል ፍሬ ነው።ለዚያም ነው እምቧይ ለዘለቄታ ላለው ተግባር እንደማይሆንና ዋጋ ቢስ መሆኑ በተረትም በምሳሌም እምቧይን ያመነና ጉም የዘገነ አንድ ነው ወይም ጠንካራና አስተማማኝ ያልሆነን ነገር ለመግለጽ የእምቧይ ካብ ተብሎ የሚነገረው።ቢቆልሉትም አስተማማኝ ከለላና ምሽግ ሊሆን የማይችል ልፍስፍስ፣በጥቂቱ የሚናድ ለማለት ነው።

የሰው ልጅ ለሚፈልገው ዓላማ መዳረሻ የሚሆን ጠንካራ አቋምና  መሰናዶ ብሎም ድርጅት ካልፈጠረ ምኞቱ የሚሳካ ሳይሆን በከንቱ ደክሞ ባክኖ መቅረት ይሆናል።ጥረቱ ሁሉ የእምቧይ ካብ ይሆናል።

በአገርም ደረጃ እንቧይን የመሰለ የሚያብለጨልጭ፣አሳሳች  የማይጠቅምና ፣ዓላማ ቢስ፣ለሆዱ ብቻ ያደረ ተቋም፣የመከላከያና የፖሊስ ሃይል፣የፖለቲካና የኤኮኖሚ እንዲሁም የማህበረሰብ ተቋም፣መንግሥትና ሥርዓት ካለ ለመከራ የሚዳርግና እንደ እምቧዩ ካብ የሚናድ ፣ በክፉ ቀን አጋልጦ እንደሚሸሽ፣ በአገራችን አይተናል ፤አሁንም እያዬን ነው።ለዚያም ነው ብልሆች ምክራቸውንና ስጋታቸውን በሚከተለው ስንኝ የገለጹት።

አገሬ ተባብራ ካረገጠች እርካብ፣

ነገራችን ሁሉ የእምቧይ ካብ የእምቧይ ካብ።

እርካብ ለእረጅም መንገድ ጉዞ የሚጋልቡት ፈረስ ላይ ለመውጣትና ለመውረድ፣ ተደላድሎ ለመቀመጥና ሳይወድቁ ወይም ፈረሱ መንገዱን ሳይስት ወይም ሳይንቀረፈፍ እንዲሄድ የሚኮለኩሉበት የኮርቻው አካል ነው።እርካብ የሌለው ኮርቻ የተጫነ ፈረስና የሚገራ ጠንካራ ሕዝባዊ ሃይል የሌለው አገርና መንግሥት ካሰበው ቦታና ደረጃ አይደርስም። በሆድ አደሮችና በዓላማ ቢስ ወታደሮች የታጀበ ስርዓትና መንግሥት እንደ እርካብ የሚረዳው ሕዝብ ስለማይኖረው አወዳደቁ የከፋ ይሆናል።በዚህ መልክ የተመሠረተ ሃይል የማታ ማታ ችግር ሲፈጠር እንደ እምቧይ ካብ መናዱና መበታተኑ እንደማይቀር በአገራችን የቅርብ ጊዜ ታሪክ ታዝበናል።በደርግ አገዛዝ ጊዜ የተገነባው ሠራዊት በብዛትም በትጥቅም በስልትም ከሌሎቹ የነገሥታት ዘመን የተለዬ ነበር።ደርግ በዘመኑ የሚኮራበትና የሚመካበትም ነበር።ሆኖም ግን ሕዝቡ በስርዓቱ ላይ ሲያምጽና፣ሲቃወም ጦሩ ከጎኑ ስላልቆመ፣ሊቆሙ የሞከሩትንም የጦር አባላትና ሹማምንት  አሳዶ በመረሸን የሥርዓቱ አገልጋይ በመሆኑ ሥርዓቱ ሲደመሰስ፣መሪው ሲፈረጥጥ በሚሊዮን የሚቆጠረው የጦር ሃይል በጥቂት የወንበዴ ታጣቂዎች ብትንትኑ ወጣ።የእምቧይ ካብ ሆኖ አረፈው።ይህ እንደሚሆንም ከወራቶች ቀደም ሲል የዛሬ 32 ዓመት በሆላንድ ውስጥ ድሪበርገን በተባለው ቦታ ባቋቋምነው በሆላንድ የኢትዮጵያውያን ማህበር አዘጋጅነት ከአውሮፓ አገሮች መጥተው ከሁለት መቶ በላይ የሚሆኑ  በተሰበሰቡበት ስብሰባ ላይ እንደ አንድ ተናጋሪ ሆኜ ባቀረብኩት ጽሑፍ ላይ ወታደራዊው  አምባ ገነኑ መንግሥት ሥልጣኑን ለሕዝባዊ መንግሥት ካላስረከበ ጦሩ እንደ ዱቄት እንደሚበተንና ተገንጣዮች አገራችንን ሊበታትኑ እንደሚችሉ ተናግሬ ነበር።በቦታው የነበሩትም ያስታውሱታል።ያልኩት አልቀረም ዓመት ባልሞላ ጊዜ ጦሩም ተበትኖ የተገንጣዮች ቡድን ሥልጣኑን ለመቆጣጠር በቃ። አገራችንም ላለፉት 31 ዓመታት በሥልጣን ላይ ለተቀመጡት አገር ጠል በሆኑ ወንበዴዎች መዳፍ ሥር ወደቀች።ለአሁን ላለችበትም የመፈራረስ አደጋ ተጋለጠች

አሁንም በሥልጣን ላይ ያለው ተረኛ መንግሥት ነኝ ባይ የጎሰኞች ስብስብ እራሱን የሚመስል የጦር ሃይልና የፖሊስ ሠራዊት በመገንባት ላይ ነው።እስከአሁን ድረስ ሰልጥኖ በስራ ላይ የዋለው ሠራዊት የአገራችንን ዳር ድንበር ለማስከበር አልቻለም።ሱዳን ድንበር ጥሳ ሠፊ መሬት ይዛ ሌላውን ለመያዝ ዝግጅትና ጥቃት ስታደርስ መከላከልና ማባረር ቀርቶ በቦታው ዝር ለማለት አልደፈረም።የተገነባው በጎሳ ህሳቤ ስለሆነ አገራዊ ፍቅር የለውም። በጎሰኝነት መመዘኛ ስሌት በተሾሙ መሪዎች የሚመራ በመሆኑም ከጎሳው ጥቅም በላይ አገራዊ ጥቅም አያሳስበውም።ለአገር አንድነትና ለሕዝቡ አብሮነት የሚታገሉና የሚጮሁት  ከባዕድ ወራሪዎች በላይ የሚጠላቸውና የሚፈራቸው ሆነዋል።ለዚያም በአገር ወዳዱ የአማራው ማህበረሰብ ተወላጆችና በሌሎቹ ኢትዮጵያውያን ላይ የሚያደርሰው ጥቃትና ወረራ ማስረጃ ነው።ወያኔ ከወደቀበት የተምቤን በረሃ ትቢያ ላይ አንሰራርቶና ፣ነፍስ ዘርቶበት ጥቃቱን እንዲያካሂድ የመሳሪያ ሳይቀር ድጋፍ የሰጠው፣ዳግም ወረራ ባካሄደበት ወቅት እዬሸሸ የአማራውን ማህበረሰብ ያስጠቃው ይኸው በጎሳ ተዋረድ የተዘጋጀ ጦር ሃይል ነበር።አሁንም ክተት ብሎ  ሃይሉን ለማሳዬት የሚሞክረው በአገር ወዳዱ፣ጎሰኝነትን በሚጠዬፈው ዜጋ ላይ ነው።ለአገር ሰላምና አንድነት ሕግን በማስከበር በሚል ሽፋን የሚዘምተውም በዚሁ አገር ወዳድ በሆነው በአማራው ማህበረሰብ በተለይም መብቱንና የአገሩን አንድነት ለማስከበር በተሰለፈው በፋኖ ላይ ነው።ፋኖ ይኖርበታል የሚለውን አካባቢ እዬወረረ ሕዝቡን ያሰቃያል፣ይዘርፋል፣ያፍናል፤ይገላል።የፋኖ ቤተሰብ የሆነ ሁሉ መኖሪያ ቤቱ ሳይቀር  ይመዘበራል፣በሳት ይቃጠላል፤በቦምብ ይጋያል፤በጥይት ይደበደባል።ህጻን ሽማግሌና አሮጊት ቤተሰብና ጎረቤት ሳይቀር መከራውን ያያል።ሰው መስሎ እንደሰው የማያስብ በአውሬ መንፈስ የሚነዳ የታጠቀ የመንግሥት ተላላኪ ጦር ለደመወዙና ለትጥቁ ግብር በሚከፍለው  በራሱ ሕዝብ ላይ የሚፈጽመውን ግፍና በደል ለመግለጽ ቃላት አይገኝለትም። 

በሥልጣን ላይ ያለው ቡድን በዚህ የጎሰኝነት ህሳቤና መርህ የሚነዳ በዬክልሉ ብዙ ሠራዊት በማሰልጠን የአገሪቱን ሃብትና ንብረት በማባከን ላይ ተጠምዷል።እርስ በርስ የሚጫረስበትን የቀበሮ ጉድጓድ ከቆፈረ ውሎ አድሯል፣ይበልጥም ጥልቀት እንዲኖረው በማድረግ ላይ ነው።ሥርዓቱ በጎሳ ጥምረት ወይም ፌዴራሊዝም የተዋቀረ ስለሆነ የመንግሥት ተቋማትም በዚያው መሰረት የተቋቋሙ ናቸው።ጦሩም ፍዴራል፣ፖሊሱም ፍዴራል፣ፍርድቤቱም ፌዴራል ሌላውም ሁሉ ፌዴራል የሚል አወቃቀር ዬያዘ ነው፣ኢትዮጵያዊ የሆነ ማንነት አልተላበሰም።የኢትዮጵያ መከላከያ፣የኢትዮጵያ ፖሊስ፣የኢትዮጵያ ከፍተኛ ፍርድ ቤት —ወዘተ የሚል መጠሪያ የለውም። የፌዴራል ገመዱ ሲበጠስና ሁሉም በዬጎሳ ጉድጓዱ ሲገባ በቀጭን ክር ላይ የተንጠለጠለው አገራዊ ገጹ ይፈርሳል ማለት ነው።የምቧይ ካብ የሆነው ሠራዊት ኢትዮጵያንም የእምቧይ ካብ ያደርጋታል ማለት ነው።

የሥርዓቱ ሌላው አስገራሚና ትዕቢተኛ ነገር የፌዴራል ፖሊስ ብሎ ባስመረቀበት በአዲስ አበባ ከተማ ላይ ፈላጭ ቆራጭ የሆነ ፣ከአንድ ጎሳ ፣ከተረኛው የኦሮሞ ጎሳ የተውጣጣ ከ50 ሽህ በላይ የፖሊስ ሃይል ሰብስቦ ማሰልጠኑንና ማሰማራቱን እንደ ትልቅ ስኬት ይፋ ማድረጉ ነው።የዚህ የፖሊስ ሃይል ተግባርም በከተማዋ የሚኖረውን ኦሮሞ ያልሆነ ሕዝብ በታሰበው ዕቅድ ለማፈናቀልና ለማባረር የሚረዳ በመሆኑ ነው። ታዲያማ ለምን አስፈለገ? ብሎ መጠዬቅ ተገቢ ነው።

 ርሃብና በሽታ እንዲሁም የኑሮ ውድነት፣የቤትና የሥራ  እጦት፣ሰላምና ፍትሕ በተነፈገው ሕዝብ ኪሳራ  የጥቂት አምባገነኖችን ሥልጣን የሚንከባከብ ሠራዊትና የፖሊስ ሃይል ማሰልጠኑን ዋስትና አድርጎ ይዞታል።ይህ ግን ለአገርም ሆነ ለአደራጁ የሚሰጠው ፋይዳ የለውም።የማታ ማታ ልክ በአሸዋ ላይ እንደተሰራው ቤት ወይም እንደተደረደረው የእምቧይ ክምር ሲነኩት ይናዳል።በእርስ በርስ በሚነሳው የጎሰኞች ትርምስና የሥልጣን ሽኩቻ አገር እንዳይፈርስ፣ሕዝብም ለእልቂት ሳይዳረግ የአገር ወዳዱ ሕዝባዊ ሃይል በጠንካራ ድርጅታዊ ተቋም ላይ መገኘት አለበት። 

የሚያኮራውና የሚያስተማምነው ትልቁ ሃይል የሕዝብን ፍቅርና ተቀባይነት ማግኘት ነው።ሕዝብ የተቀበለው ስርዓት በጦር ሃይልና በፖሊስ ሃይል ግንባታ ጊዜና ሃብት አያባክንም።ሕዝቡ እራሱ ሰላሙንና ሃገሩን ይጠብቃል።ለዘመናት ያገራችን አንድነትና ነጻነት የሕዝቡም ሰላም የተጠበቀው አገር ወዳዱ ሕዝብ በፋኖነትና በነጭ ለባሽነት ባደረገው ተጋድሎ ነው። አሁንም ለአገሩ አንድነት የሚዋደቀው፣ከጎሰኞች ስርዓት መዳፍ ለማላቀቅ የሚታገለው ይኸው ሕዝባዊ የፋኖ ጦር ነው። ለተዋጊ ትልቁ መሣሪያ የዓላማ ጽናትና ቆራጥነት ነው።የዓላማ ጽናት ያለው ሕዝብ፣ዓላማ ቢስ  የሆነውን በዘመናዊ የጦር መሣሪያ የታገዘን ደመወዝተኛ ብዙ ጦር ያሸንፋል።በአገራችን በተካሄዱት የአድዋና የሌሎቹም ጦርነቶች በውጭ አገርም የቬትናምና የሌሎቹም አገሮች ታሪክ የሚመሰክረው ይህንኑ ነው። በቅርቡም በአፍጋኒስታን የታሊባኖች ድል ይህንኑ አረጋግጧል።የእኛም የነገው የድል ውጤት ከዚህ የሚለይ አይሆንም። ኢትዮጵያን ለመበታተን የተሰለፉትን የውጭና የውስጥ ሃይሎችን ጥምረት ለማክሸፍ  በአገር ወዳዱ ጎራ የሚታዮትን ክፍተቶች መሙላት፣የላላውን መወጠር፣የተዝረከረከውን መሰብሰብ ከተቻለ ጠላትን እንደ ዱቄት መበተን ወይም እንደ እምቧይ ካብ መናድና ማንከባለል የሚያዳግት አይሆንም።

መንግሥት ተብዬው ቡድን ድግስና ሽርጉዱን ማብዛቱ የውስጡን ፍርሃትና ጭንቀት ለመሸፋፈን እንጂ እውነትስ የሕዝብን ይውንታ አገኝቼ ወይም  አሸንፌ በሥልጣን ላይ እኖራለሁ ብሎ አይደለም። ሕዝብ አንቅሮ ተፍቶታል፤በአገር ውስጥና በውጭ አገር የሚኖረው ዜጋ በሰላማዊ ሰልፍ እያወገዘውና እያጋለጠው ይገኛል።በውስጡ ሰላም አጥቶ በልዩነት ይታመሳል፣እርስ በራሱ ይባላል፤በውጭ ሃይሎችና መንግሥታት እቀባና ግዴታ ተወጥሯል፤በኤኮኖሚ ድቀት ባህር ውስጥ ይዋኛል። በአጠቃላይ የመንግሥት መውደቂያ ምልክቶችን እያስተናገደ ነው።   

ሰሞኑን በፖሊስ አባላት ምረቃው ላይ የታዬው ሰልፍና ትርኢት ሕዝብ የሚኮራበት ሳይሆን ሕዝብን ለማሸማቀቅ ታስቦ የተዘጋጀ ነው።በዚህ ሰልፍ ላይ ከየአገራቱ በብዙ ሚሊዮን ግፋ ሲልም ቢሊዮን ዶላር ወጭ የሆነበት በሰው ሸክምና በተሽከርካሪ የሚንቀሳቀስ  የጦር መሣሪያ  ታይቷል።በአፍሪካ ውስጥ የተሻለና የበለጠ ከፍተኛ ተቋም እንደሆነም ተወስቷል።የሚያኮራው በጦር ክምችት ሌላውን አገር መብለጥ ሳይሆን በሰላም፣በአንድነት፣ከርሃብ፣ከበሽታ፣ከጎሳ ንትርክና ጦርነት፣ከስደት ነጻ መሆን ነው።የሰልፍ ብዛት የሚያሳዬው ቢኖር ሰላም አልባ መሆንን፣ የመንግሥትን ፍርሃትና ስጋትን ነው። 

 ዘመናዊ መሣሪያ መታጠቁ በደፈናው የሚነቀፍ አይደለም።ተንኳሽና ወራሪ ስለማይጠፋ በእራስ ችሎታና ጥረት የመሣሪያ ማምረት አቅም ቢኖር ይደገፋል።የሚነቀፈው የአገርን እንጥፍጣፊ ካዝና እያራቆቱ ለጥቂቶች የሥልጣን ዘመን ሲሉ ለመሣሪያ አምራች አገሮች ሲሳይ መሆኑ ነው።መሣሪያ አምራቾቹም በአገራት ውስጥ ሰላም እንዲሰፍን አይወዱም።ከውጭ የሚያገኙት ገቢ ከግማሹ በላይ በሚያመርቱት የጦር መሣሪያ ሽያጭ ስለሆነ ጦርነት ባይኖርም ጦርነት እንዲኖር ተግተው ይሠራሉ።ፋብሪካ ሲያቋቁም ጦርነት መኖሩንና ሸማች እንደማይጠፋ በማመን ነው። ጦርነት ባይኖርም እንዲኖር ያደርጋሉ።አገራት ከልማት ይልቅ በጦርነት እንዲደቁ ይመርጣሉ።ለዚያ በኢትዮጵያ እንደ ወያኔና ኦነግ ያሉትን ሁሉ ጸረ ኢትዮጵያ ሃይሎች ከመደገፍና ከማስታጠቅ አይመለሱም።በሌሎቹም አገሮች እንዲሁ።ዓለምን ሰላም የነሳውና የጦርነት አውድማ ያደረጋት የነዚሁ በሆዳሞችና አውሬዎች የሚቃኘው የሸፍጥና የዘረፋ ፖለቲካ ፍልስፍና(ርዩተዓለም) ወይም መስመር ነው። 

     ልቡ የሸፈተ ሕዝብና ለዓላማው የተሰለፈ ዱላ የያዘ አገር ወዳድ ፋኖ ከብዙ ለሆዱ ካደረ፣ ዘመናዊ ጠብመንጃ ከተሸከመ፣ታንክና ሚሳይል ከታጠቀ ወራሪ ጦር ይበልጣል፤ያሸንፋልም።ትእቢትና ጥላቻ ከወጠረው ይልቅ አስተዋይነትን፣እውነትንና ድፍረትን የታጠቀ ሕዝብ አሸናፊ ነው።የጠላት ጎራ የሚፈራርስ የእምቧይ ካብ ነው።

ሁሉም ለአገሩ ዘብ ይቁም፣ሁሉም ፋኖ ይሁን!!

የጎሰኞች ስርዓት ይደምሰስ፣ሕዝባዊ ሥርዓት ይስፈን!

ኢትዮጵያ በልጆቿ ታፍራና ተከብራ በአንድነትና በነጻነት ለዘላለም ትኑር!!! 

 

 

Filed in: Amharic