>

ጴጥሮሳዊነት! (ፊልጶስ)

ጴጥሮሳዊነት!

ፊልጶስ


አገራችን ቀውስ ውስጥ ከገባች ውላ አድራለች። በ’ርግጥም የአሁኑ ቀውስ  ያለገደለው ዜጋ፣ ያላፈረሰው ቤት፣ ያልገባበት የሃይማኖት ተቋምና ድርጅት የለም።  ሁሉም ነገር ከቁጥጥር ውጭ እየውጣ መያዥና መጨበጫው ጠፍቷል።
መጭውን የኢትዮጵያን ፓለቲካ ለመናገር ከመሞከር ይልቅ ”የከርስቶስን ዳግም መምጣት” መተንበይ ሳይቀል አይቀርም።

ገዥዎቻችን  ከምዕራብ እስከ ማስራቅ፤ ከሰሜን እስከ ደቡብ፤ከመሃል እስከ ዳር ፤ በጎሳ ከልለው፣ የ’ርስ በርስ ጦርነት ለኩሰው፣ በኑሮ ውደነት እየጠብሱን፤ የኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነትን ህልውና የምናጠፋበት ግዜው አሁን ነው ብለው በህዝብ ደም እየቆመሩ ነው። የህዝብ እምባ እያፈሰሱ ነው። ከህጻን እስከ አዛውንት፣ ከወጣት እስከ ሽማግሌ ፤ ኢትዮጵያዊ የሆነውን ሁሉ ህይወቱን እየተቀጠፈ ነው። እያሰሩና እያፈኑ የምድርን ስቃይ ሁሉ እያሳዩን ነው።   የኢትዮጵያ ህዝብ  ”ኤሉሄ!  ኤሉሄ!” እያለ ቢማጸንም ፤ ከፓለቲከኞችም ሆነ ከሃይማኖት አባቶች  የሚታደገው ካጣ ዘመናት አስቆጠረ።

እንድ ሃቅ ግን እየመረረንም ቢሆን መዋጥ አለብን።  የጎሳ ፓለቲከኞች— ተረኛው ኦነጋዊ ብልጽግናም ሆነ የጡታ አባቱ ወያኔ የኢትዮጵያን  መመበረ ሥልጣን  ይዘው ለዚህ የበቁት ፤  ተደረጅተው ስለታገሉና መሰዋአትነት ስለከፈሉ ነው። እኛ ኢትዮጵያዊን ደግሞ ለዚህ የበቃነው ስለ አለተደራጀንና ጴጥሮሳዊነት ሰለጎደለን ነው። ለአገር አንድነትና ለህዝብ ልዕልና ለሚያስፈልገው  ጴጥሮሳዊ መሰዋትነት በመፈንስም ሆነ በስጋ ስላለተዘጋጀን ነው።

አሁን የመከራው  ጽዋ  ሞልቶ እየፈሰሰ ነው።  ገዥዎቻችን ኢትዮጵያን ገፍተው ! ገፍተው፣ እኛም የዳር ተመልካች በመሆን  ገደል አፋፍ ላይ አድርሰናታል። ይዋል ይደር እንጅ፤  እልቂቱም ሆነ አገር አልባ መሆኑ ለሁላችንም ነው። ለዚህም ነው መጸሃፍ፤ ”’—ማናም የቆመ የሚመስለው እንዳይወድቅ ይጠንቀቅ–” የሚለው።

 ጎሰኞቹ ወያኔና ኦነጋዊ ብልጽግና ከመሰሎቻቸው ጋር ተባብረው  ግራዚያዊነትቸውን ፤ እኛም ጴጥሮሳዊነታችን የምናስመሰከርበት የትግል ወሳኝ ምዕራፍ ላይ  ደርሰናል። ቅድመ አያቶቻችንና አባቶቻችን የሚከፈለውን መስዋእትነት ሁሉ ከፍለው ለድል በቅተዋል። ጥያቄው አሁን  ‘እኛስ?’

ባለፈት  ዓመታት  የኢትዮጵያን ህዝብ ለመከክፋፈልና ህልውናውን ለማጥፋት ብዙ ሥራ ተሰርቷል፤ ውጤቱም አሁን  ካለንበት የዓለም ጭራ ከመሆን  አድርሶናል። የጎሳ  ገዥዎቻችን ግን  ኢትዮጵያዊያን እንደሚፈልጉት ለመደረግ  የቀረቸው  ፤ ህዝቡ የተሳሰረበት የሃማኖት ግማደን መበጣጣስ ስለነበር፡ አሁን ወያኔና ኦነጋዊ ብልጽግና ለዚህ ዓላማቸው ከፓለቲካው ጋብቻ  በተጨማሪ የሃይማኖት ” ቁርባን” ፈጽመዋል።

ወያኔ እንደ ወራሪው ግራዚያን ሁሉ ገና ጫካ እያለ ነበር  የኦርቶዶክስ ተዋህዶ  ሃይማኖትን እንደ ኢትዮጵያዊነት ሁሉ በጠላትነት ፈርጆ  ማዳካምና  ”ዶግማ፤” እምነቷን መናድና ማስናድ የጀመረው። ታዲያ በወያኔ  የተጀምረው ኦርቶዶክሳዊያንን የመከፋፈልና የማጥፋት አጀንዳ፤
–  እንዴት አሁን ላለንበት ”ለጎሳ ፓለቲከኞች የኦነጋዊ ብልጽግና  መጫዎቻ ለመሆን በቃች?”
– ኦርቶዶክስን የሚያክል ለ ሺ ዘምናት በክርስቶስ ደም የተመሰረተች፣ እንዲት፣ ቅድስትና ሉዓላዊት፣ ሐዋርያዊት ቤተክርስቲያን  እንዴት በፓለቲክኞችና በአጥፊዎቿ  እጅ ወደቀች?  ወዘተ—  ብለን በቅንነት ከጠየቅን፤ መልሱ የእምነቱ አባቶችና መሪዎች ጴጥሮሳዊያን አለመሆን ነው። ከዘላለማዊ ቤታቸው ይልቅ ምድራዊ ቤታቸውና ስጋቸው ስለበለጠባቸው ነው።

በ1983 ዓ ም  ወያኔ አዲስ አበባን ሲቆጣጠር የመጀመሪያ ተግባሩ የቤተክርስቲያኗን ቀኖና ዶግማ ማፍረስ ነበር።  ታዲያ  ” እራስችን ለእግዚአብሄር አሳልፈን ሰ’ተን፤ የክርስቶስን መስቀል ተሸክመናል። ሰማያዊ እንጅ ምድራዊ ቤት የለንም ” ያሉት የኦርቶዶክስ ጳጳሳትና አባቶች፤  ከወያኔ  የሚመጣባቸውን መከራ ሁሉ በጴጥሮሳዊነት በጽናትና በትዕግስት፤ በጸሎትና በሱባኤ፤ ለወገናቸው ተምሳሌት ሆነው የመፈሳዊ ተጋድሏቸውን ማስመስከር ሲችሉ፤ ምዕመናንን አሳዝነው፣ ለወያኔ ቅጥረኞች፣  ተሿሚዎች፣ ተኩላዎችና ሆድ-አደር ሎሌዎች በትነው፤ እነሱም ወደ ምዕራቡ ዓለም “የድሪም ገዳም” ገደሙ። ጴጥሮሳዊነትን ሸሹ። ይኽን ያዩ  ጠላቶቿ “ ለካስ የማይነካውም ይነካል” ብለው የፈሪ ልብ አገኙ። ምዕራባዊያኑም “አይዟችሁ! አለንላችሁ! “ አሏቸው። ጴጥሮሳዊነትንም ይኽው እየተፈታተኑት ይገኛሉ።

ጴጥሮሳዊነትን በተመለከት፤  ነፍሳቸውን ይማርልንና ፤ የኔታ መስፈን ወልደ ማርያም፤  ኢትዮጵያዊነት ከየት ወዴት?  በተሰኘ መጽሃፋቸው፤ ( ገጽ 42)  እንዲህ ይሉናል።—-
”—–የአቡነ ጴጥሮስ መንፈስ እንደ ሐውልታቸው የተረሳ ይመስለኛል። አቡነ ጴጥሮስ እንደሌሎቹ ሁሉ ኢጣልያ ኢትዮጵያን የወረረችው «የእግዚአብሔር ፈቃድ ሆኖ ነው»፤ በማለት የኢጣልያ ወታደር የኢትዮጵያን ሕዝብ አበሳውን ያሳየው በእግዚአብሔር ፈቃድ ነው በማለት ሊገብሩና የተደላደለ ኑሮ ለመኖር ይችሉ ነበር። አቡነ ጴጥሮስ የራሳቸውንና የአገራቸውን ጉዳይ ወደ እግዚአብሔር ሳይወረውሩ ኃላፊነታቸውን ሳይሸሹ «እምቢኝ አሻፈረኝ!» አሉ። በእምቢተኛነታቸውም የኢጣልያን ክርስቲያንነትና ሥልጡንነት ፈተና ውስጥ ከተቱት። በእምቢተኛነታቸው ለእግዚአብሔር ለአምላከ ጽድቅ ያላቸውን ፍቅርና ክብር፤ ለሃይማኖታቸው ያላቸውን ጽናት፤ ለጨበጡት መስቀል ለመስዋዕትነት ምልክቱ ያላቸውን ስሜት ለአገራቸውና ለወገናቸውም ያላቸውን ታማኝነት አረጋገጡ። በመትረየስ ተደበደቡ። ዛሬ በዚህ ድርጊት ኢትዮጵያ ትኮራለች፤ ኢጣልያ ታፍራለች።——‘
ጴጥሮሳዊነት የምለው የአቡነ ጴጥሮስን ዓይነት የእምቢተኛነት መንፈስ ነው። ጴጥሮሳዊነት በእግዚአብሔር አምላክ ጽድቅነት (ጽድቅ እውነት ማለት ነው) አምኖ የራስንም ኃላፊነት ከነውጤቱ የእግዚአብሔር ፈቃድ ነው ብሎ መቀበል ነው። —”

ታዲያ  አሁን ያሉት የኦርቶዶክስ አባቶችና ጳጳሳት፤ ብዙዎቹ ያኔም  በወያኔ   ዘመን በ1983  የነበሩ ናቸው። አሁን በዚያን ግዜ የሸሹት የጴጥሮሳዊነት እድል  ዳግም  አግኝተዋል።    አሁንም ከማንኛውም ዘመን በከፋ  ሁኔታ ቤተክረስቲያኗም ሆነች አገራችን ጴጥሮሳዊነትን የምትጠይቅበትና፤ ሁላችንም እምነታችን የሚፈተንበት፣ ለአገራዊና ወገናዊ ፍቅራችን በተግባር መሰዋአትነት የምንከፍልበት ሰዓት ላይ ደርሰናል።

እናም ፤ ——
ሞት እንደሆን ላይቀር፣ በዚህ ቢሉት በዚያ
እንዴት አገር ይጥፋ የሌለው  መተኪያ።—  ነውና ፤

 ለሁላችን መዳኛና ህልውና ለሆነችው ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነታችን ሁላችንም ጴጥሮሳዊያን እንሁን።

ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኖራለች!!!

ፊልጶስ

E-mail: philiposmw@hotmail.com

 

Filed in: Amharic