>
5:13 pm - Friday April 19, 3895

ምርጫችን አንድና አንድ ነው!

ምርጫችን አንድና አንድ ነው

ፊልጶስ


ምርጫችን አንድና አንድ ነው፤  ትግል ተጀምሯል፤ ነገር ግን የተበጣጠስና ወጥነት የሌለው፤ ሁሉም በየመንደሩ የሚያደርገው ነው። ስለዚህም የተበታተነውንና  የተበጣጠሰውን ህዝባዊ እንቢተኝነት   ወደ አንድ ማዕከላዊ  ትግል ማምጣትና በኢትዮጵዊነት ጥላ ስር ማሰባሰብ፤ ብሎም ከውጩ ኃይል ጋር የተቀናጀ የተደራጀ ፓለቲካዊ ራዕይ ያለው  ትግል  ካደረግን፤ ገዥዎቻችን  ሳይወዱ ተገደው ሥልጣናቸውን የሚለቁበት፤  የአገር እንድነትንም መታደግ  የሚያስችል  ኃይል መፍጠር እንችላለን።

ብልጽግና  ወደ መበሩም ሲመጣ ሆነ  አሁን አገር እየመራ አይደለም። ህዝብ እያስተዳደረ አይደለም። ህዝብን ከህዝብ እያባላና እየበላ ያለ የወንበዴዎችና የዘራፊዎች አገዛዝ መሆኑን  በተለያየ መንገድ አስመስክሯል።
አንድ መንግሥት፤ እንደ መንግሥት አገረ -መንግሥት  የሚያሰኘው ሁሉንም ማሟላት ባይችል እንኳ’ መሰረታዊ የህዝብን ደህንነትና የአገርን ልዕልና ማስከበር ሲችል ነው። ያለያ በተለምዶ የከሸፍ መንግስት (ፌልድ ስቴት) ይባላል። ታዲያ  አገሮችን ለመክሸፍ የሚያበቃቸው ዋና ምክንያት ማዕከላዊ መንግስት መዳከምና  ህግና-ሥርዓት ሲጠፋ ነው። ከዚህ ላይ መጤን ያለበት የሰው ልጅ መሰረታዊ መብቱ በገዥዎች ተረግጦና  ታፍኖ፤  ህዝብ ሙሉ በሙሉ በቁጥጥር ስር ከዋለና ያለነጻነት ከተገዛ፤ ብሎም የአገር ሃብትና ገንዘብ   የአምባገነኖች የግል ኪስ  ከሆነም እንደ ከሸፈ አገር-መንግሥት ይቆጠራል።

አንድን አገር ከመክሸፍ  አልፋ ለርስ-በርስ እልቂትና ለዋአላዊነት መናድ  መሰረታዊ ችግር፤ ገዥዎች ተገደው ይሁን በኃይል ከስልጣናቸው ሲወገዱ ፤ አገርንና ህዝብን ለመታደግ የሚችል ጠንካራ ህዝባዊ  የፓለቲካ  አመራር ወይም ድርጅት ያለመኖር ነው።
አምባገነን ገዥዎች እድሜያቸው በተራዘመ ቁጥር ህዝብን ያስተሳሰረውን የአንድነት  መረብና ተቋማት ያፈራርሳሉ። ለዚህ በቂ ማሰረጃ ኦነጋዊ ብልጽግና በኦርቶዶክስና በእስልምና  ሃይማኖት ላይ እየወሰደ ያለው እኩይ ምግባር አገዛዙ የመጨረሻ ጣረሞት ላይ ምሆኑን  ብቻ ሳይሆን አገርና ህዝብን ይዞ ሊጠፋ መወሰኑን ያሳያል።

በወያኔ-ኢህአዲግ ላይ  የተደረተው የኦነጋዊ-ብልጽግና ለመሰረታዊ ለውጥ የተደረገውን ትግል ጠልፎ  አራት ኪሎን ይቆጣጠር እንጅ፤ አገር ማስተዳደር የተሳነውና  ራሱን ብልጽግና ብሎ የሚጠረው  የጎሳ ስብስብ፤ አሁን ደግሞ ወያኔ የጋጣትንና  በጦርነት ያዳከማትን አገር፤ በተረው መጋጡ ሳያንሰው፤ ”ሌባ ሲከፋፈል እንጅ ሲሰርቅ አይጣላም ” እንደሚባለው ሆነና ፤ ፤  ‘ርስ በርሱ እየተባላ ከተደረተበት   ወያኔያዊ ስፌት እየተተረተረ፤  በጠ/ሚ የሚሰበኩት የኢትዮጵያዊነት ”ማስክ”’እርቃኑን እየውጣ፤ አገርና ህዝብ ይዞ ሊጠፋ   እየተደረደረ ነው። 


የግዜ ጉዳይ እንጅ  የኦነጋዊ- ብልጽግና መፈራረሱና መወገዱ አይቀሪ ነው።   ታዲያ ዋናው መሰረታዊ ጥያቄ ፤ እንደ ወያኔ አወዳደቅ ፤ ካለፈው በባሰ ዳፋው ለአገርና ለህዝብ እንዳይተረፍ፤ እኛ  የአገርና የህዝብ አንድነት እንዲቀጥልና ያስተሳሰሩንን የኢትዮጵያዊነት እሴቶቻችን ለማስጠበቅ ምን እየሰራን ነው? የሚለው ነው።

በአሁኑ ሰዓት ሃቁን እንቀበልና፤  አገራችን እንታደግ የምንል ከሆነ ፤ በርግጥም  የምንገዛው በከሸፈ  የጎሳ ፓለቱካና ተላላኪ ካድሪ   ነው። ከከሸፋ ገዥዎች የምንማረው ደግሞ  ህዝብን ከፋፍለውና ኃይል አሳጥተው ፤ ከጋጡት የአገር አንጡራ ሃብት  የተረፈም ካለ ቋጥረውና ለ’ርስ-በርስ ጦርነት አመቻችተው መሸሽ ነው። 

አሁን ብልጽግናዎች መጨረሻው ሰዓት ላይ መሆናቸው ገሃድ የወጡ፤የሚውስዷቸው እርምጃዎች በደመነፍስ እየተደናበሩና ሁሉም ነገር ከቁጥጥራቸው እየወጣ ለመሆኑ ፤ በገሃድ የሚታየውን ልግንዛቤ ያህል ልጥቀስ፤
1/ ከወያኔ ጋር የተደረገው ጦርነትና በሚሊዮኖች የረገፈው ህይወት፣ ብሎም በትርሊዮን ለሚቆጠር  የሃብትና ገንዘብ ውድመት ትርጉማ አልባ እንደነበር ለህዝብ ግልጽ መሆኑ ብቻ ሳይሆን ፤ የሰላም ስምምነቱ ዘላቂ ሰላም እንደማያመጣና የወያኔና የብልጽግና ጦርነት የሥልጣን እንጂ የምንም አለመሆኑ በገሃዱ እያየነው ነው። የሰላም ስምምነቱም ሳይጀመር ክሽፋል። ሰሞኑን አቶ ጌታቸው ረዳ በትግረኛ እንደነገሩን ” ትጥቅ ማስፈታት የሚለው የቲቪ ድራማ” መሆኑን  በግልጽ ነገረውናል፡  
2/ አሁንም በትግራይ ሚሊዮኖች እየተራቡ ብቻ ሳይሆን፤ ወያኔ በሁለት ተከፍሎ ማለትም በወያኔው ሊቀ-መንበር በአቶ ደብረ ጺዮን ገ/ ሚኬኤልና  በትግራይ የግዚያዊ አሰተዳደር በአቶ ጌታቸው ረዳ መካከል  የገመድ ጉታቶው  እየተካሄደ ነው።  በ’ርግጥ ይህ የተለመደው የፓለቲካ ሴራን ቁማር ይሁን ግልጽ አይደለም። አንድ ነገር ግን እርግጠኞች ነን፤ ይኽውም   ወልቃይትንና ራያን ለመውረርም ዝግጅቱ ተጠናቋል። ከአራት ኪሎ ከኦነጋዊ ብልጽግናም  ድጋፋ ቀጥሏል።

አላማው ደግሞ ግልጽ ነው፤ የጎንደርን፣ የወሎን፣ የሸዋንና የጎጃምን ህዝባዊ እንቅስቃሴና ፋኖን  ተባብሮ ለመምታት ነው።  የኢትዮጵያዊንት ጠላቶች ትብብር።


3/ ብልጽግና በክፋ ቀኑ የደረሰለትን ከወያኔ ጋር ላደረገው ጦርነት ፤ “ተዋጋና የማረከውን መሳሪያ ታጠቅ “ ያልውን ፋኖንና የአካባቢውን ልዩ ኃይል ለማስፈታት  የአገር መከላከያን ያሰማራበትና የሄደበት የክህደትና የሃሰት መንገድ   ከአካባቢ ህዝብ ጋር  ያሰተሳሰረውን የሰለለች ገመድ  በድጋሜ ላይቀጠል በጣጥሶታል። በአጠቃላይ ብልጽግና የህዝብ ቀንደኛ ጠላትና መንደርተኛነቱን ራሱ አጋልጧል።   የአገር መከላከያ  ሰራዊት  ክላሽ ለታጠቀ በታንክና በዙ-ሃያሶስት  ቢዋጋም -ቤት ክርስቲያን ከመድብደብ፣ ንጹሃን ዜጎችን ከመግድልና ከማሰቃየት፣  በህዝቡ ዘንድ የበልጠ መከዳትንና  የበልጠ መከዳትንና ቁጭትን  በመቀስቀስ  የብልጽግናን እድሜ ከማሳጠር ውጭ ወደፊትም የሚሰራው ፋይዳ አንደማይኖር እያየን ነው።

4/ ኦነጋዊ ብልጽግና የዳቦ ስም የሰጠው ሸኔ በየደረሰበት ሁሉ ዜጋን እንደ ከብት ከማረድና ካማሳደድ አልፎ ፤ ከመቸውም በላይ ተጠናክሮ  አዲስ አባባን ዙሪያውን ከቦ ከእነ አቶ ሽመልስ አብዲሳ   ‘’ፊችካ’’ እየጠበቀ ነው።

5/ ብልጽግና ከአዲስ አበባ ህዝብ ጋር ተፋቷል።  የአዲስ አበባን ዲሞግራፊ ለመቀየር የተከሄደበት መንገድ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎችን ማፈናቀልና ቤት አልባ ማድረጉ ሳያንሰው፤ አካባቢውን ለቀው እንዲሄዱ እያደረግ ነው። የሚያፈርሳቸው ቤተ-ክርስቲያናትና መስጊዶች በራሱ ላይ ነዳጅ እያርከፈከፈ ለመሆኑ መረጃዎች ናቸው። ታዲያ የብልጽጋና  ይኽን ሁሉ ግፍ የሚሰራውና ቤት  የሚያፈርሰው  በመከረኛ የኦሮሞ ህዝብ ስም  መሆኑና ራሱ የሸጠውንና ህጋዊ ያደረገውን  መሬት ነው። 

6/ የብልጽግና አገዛዝ የአገሪትን ሃብት ግጦ በልቶ ዛሬ  ለራሱ ካድሪዎችና ለውጭ ምንዛሬ የሚሆን ካዝናው ከደረቀ ውሎ አድሯል። የሚገርመው በልመና ላይ ተሰማርቶ ሚሊዮኖችን አፈናቅሎና በርሃብ እያረገፍ፣ ‘’የሸገር ከተማና የጫካ ቤተመንግሥት ልሰራ ነው ‘’ ሲል መደመጡ ነው፡  አንድ አገዛዝ መጨራሻው ሲደርስ አዕምሮን ስለሚስት፣  በዘረፋ ስለሚጠመድ የሚያደርገን እንደማያውቅ ከዚህ መረዳት እንችላለ።

ታዲያ አገዛዙ የውጭ ምንዛሬ ለማግኘት ሲል የአገርን አንጡራ ሃብት ከመሸጥ ወደ ኋላ እንደማይልና በቅርቡ የስኳር ፋብሪካዎችን ለጨረታ ማቅረቡን ማስታወስ ተገቢ ነው። በግዜ ካልተወገደ ነገ   የኢትዮጵያን አየር መንገድንም ለጨረታ እንደሚያቀርበው እንጠራጠር።  ወሎ ሲያድርም የአገሪቱ ምጣኔ ሃብት ሙሉ በሙሉ እንዳይጠፋ ያስፈራል።

7/ የዋጋ ግሽበት በኑሮ ላይ የፈጠረው ጫና ፣ በርግጥም የኢትዮጵያ ህዝብ ከዚህ በላይ ምን እየጠበቀ ነው ያሰኛል። የኢትዮጵያ ህዝብ በታአምር ይኖራል ማለቱ ይቀላል።  ያለመደራጅታችን እንጅ የኑሮ ውድነት ብቻ ኦነጋዊ ብልጽግናን ከአራት ኪሎ ባረረው ነበር።

8/ በተለያዩ የአገራችን ክፍሎች መለስተኛም ሆነ ዝቅተኛ ጦርነቶች እየተካሄዱ ነው። በጋምቤላ፣ በጎንደር፣ በጎጃም፣ በወሎ፣   በሸዋ —- በአጠቅላይ ህግና ሥርዓት ጠፍቶ  ብልጽግና አዲስ አበባን የሙጥኝ ብሎ ፤ አገርና ህዝብ ይዞ ለመጥፋት በየዕለቱ የመከፋፈልና የሴራ አጀንዳ እየፈበረከ ነው። የመብት ታጋዮችን፣ ጋዜጠኞችን፣ ባለሃብቶች ፤ በአጠቃላይ ዜጎችን በማንነታቸው  እያሰረና እያሰቃየ፤  እንደ ጡት  አባቱ ወያኔ ጥፍር እየነቀል  ህዝብን በገዛ አገሩ ምጻተኛ  እያደረገ ነው።

ከላይ ለማንሳት የሞክርኩት  አገራችን ያለችበት ሁኔታ ጸሃይ የሞቀው፤ የየዕለት ኑሯዋችን  የአደባባይ ሃቅ ነው። ነገር ግን አሁን-አሁን በህዝብና በአገር ላይ ሊፈጸሙ ወይም ሊሆኑ የማይገባቸው ነገሮች፤ ሲከናወኑ  ደጋግመን በማየታችንና በመላመዳችን፤ ከዚህም አልፎ በየቀኑ አዳዲስ አጀንዳ እየተወረወረልን ስንቧጨቅ፤ ከሁሉም በፊት ቅድሚያ ልንሰጠው የሚገባንን  ህልውናችን የማስጠብቅ ትግል ዘንግተን፤ ከገዥዎቻችን ባልተናነሰ፤ እነሱ በከፈቱት ቦይ እየፈሰስን ጎሰኝነት አገራችን አድነታችን እያሳጣን ነው።

በእውነቱ  ብልጽግና  ተቃውሚ ነኝ ከሚሉት ሙሉ ድጋፍ ቢያገኝምና ለሆድ አደሮች ስልጣኑንም ቢያካፍል ፤ ገዥዎቻችን ግን  ”ርስ-በርሳቸው እየተወነጃጀሉና እየተባሉ ነው። ታዲያ ይህ የሆነው ኢትዮጵያዊ የሆነ አስገዳጅ የተደራጀ ኃይል ተፈጥሮ ሳይሆን ፤  የጎሳ ፓለቲካ መጨረሻው ርስ-በስ መበላለትና ፤ ቆምንለት ለሚሉት ጎሳ በስሙ እየቆመሩ ህዝብን ከህዝብ እያቃቃሩን እያገዳደሉ አገርን ያለባለቤት ማሰቀረት  መጨረሻቸው በመሆኑ ነው።

ለኢትዮጵያዊነትና ለአንድነታችን ይቆማሉ ያልናቸው  ተቃዎሚ ተብየዎች ፤ በተለይም እንደ ኢዜማ ያሉትም  የስልጣን ፍርፋሪው በልጦባቸው ሲያወግዙት በነበረው የጎሳ ፓለቲካ ውስጥ ተቀርቅረው; የህዝብን ትግልና የገቡትን የኢትዮጵያዊነት ቃል  ሰልቅጠው ፤ የብልጽግንና መክሸፍ ሲረዱ፤ ” የአህያ ባል ከጅብ አያስጥል” መሆኑን ተረድተው እነሱም  አሁን  መክሸፋቸውን  ብቻ ሳይሆን ዜና እረፍታቸውን እየሰማን ነው። በዚህ አጋጣሚ ለኢዜማዎች ነፍስ ይማር ለማለት እወዳለሁ። በ’ርግጥ ለብልጽግና  የመንደር አገዛዝ ከዚህ ደረጃ ለመድረስና ኢትዮጵያን ምስቅልቅሏ እንዲወጣ ላደረጋችውት መረባረብ ከተጠያቂነት  አታመልጡም።

 የኢትዮጵያን ህዝብ የበለጠ ሃዘኑን መራራ የሚያደርገው ፤ ከዚህ ሁሉ መሰዋአትነት በኋላ እንኳን ፤ራሱን መመራት  ያቃተው ኦነጋዊ -ብልጽግና በጎሳ ካርድ እየቆመረ እየፈራረሰ ሲሆን ፤  እንደ ትላንቱ እንደ ወያኔ አወዳደቅ  ሁሉ አሁንም አንደም   ክፍተቱን የሚተካ  ኢትዮጵያዊ የተቃውሚ ወይም የህዝብ መሪና  የፓለቲካ ድርጅት ያለመኖሩ ነው።። ይህም ኦነጋዊ-ብልጽግና ሲደናበር፤ የአገር  ህልውና በወያኔዎችና በኦነግ-ሸኔዎች እጅ  እንድትወድቅ የሚያደርግ ብቻ ሳይሆን፤ ሊከተል የሚችለውን የዘር ማጽዳትና እልቂት—-በ”ርግጥም ማሰብ አልፈልግም። እግዚአብሄር ከዚህ ይሰውረን።

 አሁን ያለን ምርጫ አንድና እንድ ነው፤  ይኽውም   የሁላችን መዳኛ ለሆነው፤ በአንድነት- ለአንድነት ለኢትዮጵያና ለኢትዮጵያዊነታችን  ተደረጅተን መታገልና ያለውን አገዛዝ አስወግዶ  ፤ ለሁላችን የሚሆን ስርዓት ለመገንባት የሚከፈለውን መሰዋእትነት ሁሉ መክፈል ነው።

በየቦታው ያለን የተበጣጠሰ ትግል ወደ አንድነትና በማምጣት፤ ከሆሆታ፣ ከበለው በለው፣ ከሽለላ፡ ከፍከራና ከቀረርቶ ወጥተን፤  በጎሳና በመንደር መናቆራችን አቁመን፤  ከማንኛውም  ግዜ በበለጠ በሰከነ መንፈስ’፤  ለዘላቂ መፍትሄ፤ ከተራ ዜጋ ጀምሮ  ለአገርና ለህዝብ ተቆርቋሪ ነኝ እስከ ሚል ድረስ ቆም ብሎ፤  በአገርና በህዝብ ላይ የተደቀነውን አደጋ ተገንዝቦ ለመፍትሄ መኳተን  የእያንዳንዳችን የፍላጎት ጉዳይ ሳይሆን  ግዴታ እየሆነ ከመጣ ውሎ አድሯል። ምክንያቱ አሁን ያለው አገዛዝ ትላንት ከተነሳበት አንስቶ  አሁን እስከ አለበት ደረጃ ያደረግው ጉዞ፤ በአጭር አገላለጽ፤ ራሱ ከሽፎ  አገርና ህዝብን እያከሸፈ ነው።

አሉ የሚባሉትም ተቃዋሚዎች ሆድ-አደርና የከሽፈውና  የብልጽግና መጠቀሚያ የሆኑ አሮጌ ”ቁናዎች” ናቸው። አሁን በአዲስ ኢትዮጵያዊ መንፈስ፤ አዲስ አደረጃጀት ፤ በዚህ ትውልድ የሚመራ አዲስ አመራርና ፓለቲካዊ ትግል ያስፈልገናል።  የኢትዮጵያዊነት ትግሉ  ለሆዳቸውና  ለስልጣን ሲሉ ከሚቆምሩት፤ ከያ ትውልድ ነጻ ማደረግ የግድ ይላል።

ስለዚህም  ያለን የምርጫ  አንድና እንድ ነው፤ ይኽውም የገዥዎቻችን የጎሳ ከፋፍለህ የተለመደ አገዛዝ  አስወግደን፤ ትግሉ የሁሉም ኢትዮጵያዊ መሆኑን ተረድተን፤ የተበታተነውንና ወጥነት ያጣውን ህዝባዊ እንቅስቃሴ  አሰባስበንና ውጭ ካለው ወገናችን ጋር አቀናጅተን፤ ትክክለኛና ታማኝ  የትግል ሚዲያ ተጠቅመን፤ የሚጠይቀን መሰዋአትነት  በመክፈል፤ የአገራችንም ሆነ የራሳችን ህልወና ለመታደግ ለነገ ሳይሆን ዛሬ  መተግበር ያለበት የመኖርና ያለመኖር ጥያቄ ነው።

ኦነጋዊ ብልጽግናም ሆነ ወያኔ  አገርና ህዝብ ለማፍረስ የበቁት ግራም -ነፈሰ ቀኝ ፤ ስለ ተደራጁና በጽናት ስለታገሉ  የመሆኑን ሃቅ መቀበል አለብን። እንግዲህ ምርጫው የኛ ነው። ኢትዮጵያ ወይም ሞት!
ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኖራለች!!

e-mail: philiposmw@hotmail.com

Filed in: Amharic