>

የጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ እናት አቤቱታ

ለኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን
አዲስአበባ

ጉዳዩ፡-የልጄ የተመስገን ደሳለኝን ጤንነትና የጉብኝት ሁኔታን ስለማወቅ፦

temesgen-desalegns-motherየልጄ ተመስገን ደሳለኝን ጉዳይ ይዤ እናንተው ጋር መመላለስ የግድ ሆኖብኝ ዛሬም ከደጃችሁ መጥቻለሁ፡፡ ባሕሌና አስተዳደጌ ያስተማረኝ አንድቦታ ለአንድ ጉዳይ መመላለስለ ችግሩ ባለቤትም ሆነ ለመፍትሄ ሰጭው አሰልቺ መሆኑን ነው፡፤ እውነት ለመናገር ዛሬም ወደ በራፋችሁ ስመጣ እንደው እነዚህን ሰዎች ስራ እያስፈታኋቸው ይሆን ከሚል ሃፍረት ጋር ነው፡፡ ግን ምን ላድርግ? ጉዳዩ ልጅን የሚያኽል የስጋ ክፋይ ነገር ሆነብኝ፡፡ እንድትረዱልኝ የምፈልገው እኔም ተቸግሬ እያስቸገርኳችሁ መሆኑን ነው፡፡ በተጨማሪም ጭንቀት እረፍት ስላሳጣኝና ጤናዬንም እየፈተነኝ በመሆኑ የመፍትሔ ያለህእ ያልኩ አለሁ፡፡
ከዚህ ቀደም እናንተ መ/ቤት ብቅ ያልኩት ልጄን ለመጎብኘት ፈቃድ እንዳገኝ ትተባበሩኝ ዘንድ ነበር፡፡ በወቅቱ የተሰጠኝ ምላሽ እጅግ እንዳስደሰተኝ በአደባባይ መናገሬን ማንምያውቀዋል፡፡ አንጀቴ እንደራሰም ሁሉም ተረድቶታል፡፡ ዛሬም በድጋሜ ስመጣ በባለፈው መፍትሔ ተበረታትቼ ነው፡፡ ይህን ሳልናገር ማለፍ በእኔ እድሜ ለሚገኝ ሰው መልካም አይሆንም፡፡ እንደ ከዚህ ቀደሙ ሁሉ የዛሬውም አቤቱታየ ተመሳሳይ ምላሽ እንደሚኖረው በሙሉ ልቤ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡

በዝዋይ ማረሚያ ቤት በእስር ላይ የሚገኘው ልጄ ተመስገን ደሳለኝ ከታሰረ ሁለት ዓመታት አለፉ፡፡ በዚህ ግዜ ውስጥ የወገብ ህመምና የጨጓራ በሽታ እየባሰበት መምጣቱን በተደጋጋሚ ሰምቻለሁ፡፡ አንደኛው ጆሮውም ስቃይ እየፈጠረበት መከራውን እንዳባሰበት እሱን ባየሁበት ወቅት ለማወቅ ችያለሁ፡፡ ይባስ ብሎም የማረሚያ ቤቱ አስተዳደር አለፍ አለፍ እያለ ያለመጎብኘት እገዳ ይጥልበታል፡፡ ይኽን ታዲያ ምን ትሉታላችሁ? በእስር ላይ ሌላ እስር አይደለምን? እነዚህና መሠል ተደራራቢ ችግሮች እየከፉ መምጣታቸው በእኔና በተቀሩት ጎብኝዎቹ ዘንድ ከፍተኛ ስጋትና ጭንቀትን ፈጥሮብናልን፡፡

ከሳምንንታት በፊት ህዳር 28/2009ዓ.ም የዝዋይ ማረሚያ ቤት ሰዎች ልጄ የት አንዳለ አናውቅም በማለታቸው ለአስር ቀናት እምጥ ይግባ ስምጥ ሳላውቅ በእየሰር ቤቱ ከሚንከራተቱት ልጆቼ ጋር ልጄን ፈለኩት፡፡ አለገኘሁትም፡፡ የወለደ አንጀት አልስች ልቢለኝ “እርሜን ላውጣ” እያልኩኝ ልጄን ስል ሰነበትኩኝ፡፡ መቼምአምላክ ሰሚነውና በአስረኛው ቀን ታህሳስ 7/2009ዓ.ም በዝዋይ እስር ቤት ተመሰገን ተገኘ አሉኝ፡፡

ደስም አለኝ፡፡ ግን ምን ዋጋ አለሁ ይኼን ደስታ ማቅ የሚያለብስ ሌላ ወሬ ደረሰኝ፡፡ ‹‹የልጄን ዓይን አያለሁ›› ብዬ በተነሳሁ ውዬ ሳላድር በድጋሜ የክልከላው ዕጣ እኔኑ ገጠመኝ፡፡

ከዚህም አልፎ ህመሙ እንደ ባሰበትና ከእስር ቤቱ ቅጥር ውጭ ወደሚገኘው ባቱ ሆስፒታል እንዳደረሰው ልጆቼ ቢደብቁኝም ስለጉዳዩ የሚያውቁ ሰዎች ነግረውኛል፡፡ ይህን ከሰማሁ ጀምሮ ተመስገን ስል ዛሬም አለሁ፡፡

ብቻ ተባበሩኝ፤ እርዱኝ፡፡ ይኼን መከራ ብቻዬን ለመወጣት አቅም የለኝም፡፡ የምታግዙኝ ነገር እንዳለ ስለተረዳሁ ነው የእናንተንም ደጅ የምጠናው፡፡ እገዛችሁ ልጄን የማየት ምኞቴንና እርሱም የሚያስፈልገውን የህክምና እርዳታ በአፋጣኝ እንደሚያስገኝለት ሙሉ ዕምነት አለኝ፡፡ እስኪ ለሁሉም ፈጣሪ ይርዳን፡፡
ከሰላምታጋር፡፡
ወ/ሮ ፋናዬ ይርዳቸው
ግልባጭ
 ለጠቅላይሚኒስቴር ጽ/ቤት
 ለተወካዮችምክርቤትአፈ-ጉባዔ ጽ/ቤት
 ለተወካዮችምክርቤትየህግ፣ ፍትህናአስ/ር ጉዳዮች ቋ ኮሚቴ
 ለጠቅላይዐቃቤህግ ጽ/ቤት
 ለሰብዓዊመብቶችጉባኤ (ሰመጉ)
 ለሕዝብዕምባጠባቂተቋም
 ለኢትዮጵያቀይመስቀልማሕበር
 ለሚዲያዎች

Filed in: Amharic