>

ኢሃዴግ ደንበኛ የማፍያ ድርጅት መሆኑን የምታውቁት ከዚህ ቀጥሎ ያለውን ዓረፍተ ነገር ስትሰሙት ነው (ዮናስ ሃጎስ)

«ድርጅቴ የሚለቀኝ ከሆነ ከጉሊትም ተነስቼ ሐብት ማፍራት እችላለሁ…»
***
በዓለም ላይ ካሉ የድርጅት ዓይነቶች ከገባህበት በኋላ ለመውጣት ፈቃድ የምትጠይቅበት ግን የማታገኝበት የድርጅት ዓይነት አንድ ብቻ ነው። የማፍያ ድርጅት!
***
ነፍሱን ጌታ በደንብ ይጠይቀውና ሟች ባሏም ይህቺኑ ዓረፍተ ነገር እንደደጋገመ ነው ወደ መቃብር የተከተተው። «ድርጅቴ አልለቅ ብሎኛል»፣ «ድርጅቴ ከዚህ ተርም በኋላ ትለቃለህ ብሎኛል» እያለ ሲያነበንብ ነው የተቀደመው። (በነገራችን ላይ አንዳንድ ተንታኞች መለስ አለመሞቱንና አሁን በወታደር የሚጠበቀው የሬሳ ሳጥን ባዶ መሆኑን የሚናገሩበት ምክንያት አቶ መለስ ድርጅታቸው አልለቃቸው ስላለ የራሳቸውን ሞት አቀነባብረው ድራማ እንደሰሩ በማስረገጥ ነው) ከዚህ በፊት ‹በመተካካት› ሰበብ ከጨዋታው ገለል እንዲሉ ተደርገው የነበሩ እነ አዲሱ ለገሰ፣ እነ ስዩም መስፍን ምናምን ወደ ጨዋታው እንዲመለሱ የተደረገው ድርጅቱ የማፍያ ድርጅት በመሆኑ ነው።
***
በማፍያ ድርጅት ውስጥ ሰዎቹ ቃልኪዳን ተገባብተው የሚኖሩት ፊርማ ተፈራርመው አሊያም ውልና ማስረጃ ሄደው አስፀድቀው አይደለም። በማፍያ ዓለም ውስጥ አባላቶች የሚተማመኑት በአንድ ነገር ብቻ ነው። ይህም ሁሉም ወንጀል በመስራት አንዳቸው የሌላቸው ጠባቂ በመሆን ብቻ ነው። የማፍያ ድርጅት ውስጥ ለመቀላቀል ከፈለግክ ከብዙ መስፈርቶች በኋላ የማትቀረዋ ወሳኝ መስፈርት ወንጀል እንድትሰራ መጠየቅ ነው። (ወይ ሰው እንድትገድል ትደረጋለህ አሊያም ሌላ ወንጀል ያሰሩሃል) አንድ ጊዜ ያቺን ወንጀል ከሰራሃት በኋላ ጭውቴው አለቀ ማለት ነው።
***
ከኢሃዴግ ባለፉት 26 ዓመታት ብዙ ሰዎች ኮብልለዋል። እነዚህ ሰዎችን በሁለት ካታጎሪ ልንከፍላቸው እንችላለን። አንደኛው የሚሰራው ወንጀል ብዛት እየከነከናቸው ሄዶ ከሕሊናቸው ዓቅም በላይ ሆኖባቸው የፈረጠጡና ‹አምልጥ› ተብለው በቦሌ የተሸኙ ተብለው ሊከፈሉ ይችላሉ። እስካሁን ከፈረጠጡ አሊያም እንዲፈረጥጡ ከተደረጉ የኢህአዴግ ቀደምት ሐላፊዎች ውስጥ የኢሃዴግን ጉድና ገመና በደንብ አድርጎ የተነተነው ኤርምያስ ለገሰ ዋቅጂራ ብቻ ነው። ከሱ ውጪ ያሉት ባለስልጣናት ግን ከኢሃዴግ ከወጡም በኋላ አፋቸው እንደተሎገመ ነው። ይህ የሚያሳየው ድርጅቱን አመለጥኩኝ ብለህ ብታስብም አንተ ማውራት ስትጀምር ያንተም ጉድ መወራት እንደሚጀምር ነው።
***
ለማንኛውም አንድ እርግጠኛ ሆኜ የምነግራችሁ ነገር አዜብ ‹ኔፓ› ነኝ ካለች ሌሎቹ ባለስልጣናት ይህን ዕድል ካገኙ «እንዲያውም ተበድረንና ተለቅተን ስለምንኖር ከፍተኛ እዳ ውስጥ ነንና በGo Fund Me የሆነ ነገር አሰባስቡልን» እንደሚሉን አትጠራጠሩ!
Filed in: Amharic