>

የወያኔ ኮንስፓይረሲ (ኤርሚያስ ቶኩማ)

ከሰሞኑ በኢሉ አባቦራ ዞን በሚገኙ የተለያዩ አካባቢዎች የነበረውን ድርጊት ተከትሎ ነገሮች ከሚገመተው በላይ እንዲጮሁ እየተደረገ መሆኑን እየተሰማኝ ነው በተለይም የመንግሥት ደጋፊ የሆኑ የሚዲያ ተቋማትና አክቲቪስቶች ነገሩን በማጦዝ ለአማራው ህዝብ ያዘኑ በመምሰል የኦሮሞውንና የአማራውን ህዝብ ለማጋጨት እጅግ አደገኛ የሆኑ ፅሁፎችን እየበተኑ ይገኛሉ፤ በእጃቸው ካለው የሚዲያ ሀብት አንፃር የሴራ ፖለቲካቸውን በሰአታት ውስጥ በመላው ኢትዮጵያ እንዲዳረስ እያደረጉት ይገኛሉ ለዚህም ተግባራቸው በዋነኝነት እየተጠቀሙ የሚገኙት በዛሚ ራዲዮ እና በENN ቴሌቪዥን አማካኝነት ነው።
ዛሚ ራዲዮ ከምስረታው ጀምሮ ፀረ አማራና ኦሮሞ ሆኖ የሚንቀሳቀስ ሚዲያ ሲሆን ብዙም አድማጭ የሌለው ሚዲያ በመሆኑ ነው እንጂ ሕዝብን ከሕዝብ ለማጋጨት ያልሰሩት የፕሮፖጋንዳ ሥራ የለም፤ አምና ጎንደር የሚገኙ የትግራይ ተወላጆች ተፈናቀሉ ተብሎ በሌላ ክልል የሚገኙ የአማራ ተወላጆች ተመሳሳይ እጣ እንዲደርሳቸው በሚመስል መልኩ ሚሚ ስብሃቱ “አማራው የትግራይ ተወላጆችን ቢያባርርም ብዙ አማራዎች በተለያዩ ክልሎች እንዳሉ መዘንጋት የለበትም” ስትል በአማራው ላይ ኢንተርሃሞይ ስታውጅ የነበረች እጅግ አሣፋሪ ጋዜጠኛ ነች አሁንም እያደረገች ያለችው ነገር ለአማራው ያዘነች በመምሰል በሁለቱ ጎሳዎች መካከል መተላለቅ ይኖር ዘንድ ተግታ ጥላቻን መስበክና ነገሮችን ማጦዝ ነው።
በተመሳሳይ ENN የተሰኘውም ቴሌቪዥን ጣቢያ ከዛሚ ራዲዮ ጋር አንድ አይነት ተልእኮ አንግቦ በመንቀሳቀስ ላይ የሚገኝ የግጭት መሣሪያ የሆነ ተቋም ነው።
ይህንን ሚዲያ ለመጀመሪያ ጊዜ ያየሁት ኦዳ የተሰኘ የመወያያ ፕሮግራም ላይ ተወያዮች ውይይት ሲያደርጉ ነው በጊዜው በጣም የገረመኝ ተወያዮች ተብለው የቀረቡት ግለሰቦች በሙሉ የአንድ አካባቢ ሰዎች ከመሆናቸውም በላይ የህወሃት ደጋፊ እንደሆኑ ብዙዎቻችን የምናውቃቸው እነፍፁም ብርሃነ ፣ እነየማነ ነጋሽ (አሁን ቢቢሲ ትግርኛ ላይ የሚፅፈው) እና አንድ ሌላ ለጊዜው ስሙን የማላስታውሰው ከየማነ ነጋሽ ጋር የአማረ አረጋዊ ንብረት የሆነው ሪፖርተር ላይ ይፅፍ የነበረ ግለሰብ ነው። እነዚህ ተወያዮች ስለሚዲያ ነፃነት ከተወያዩ በዃላ እንደመደምደሚያ የተጠቀሙት አሁን በኢትዮጵያ በሚዲያ በኩል ያለው ቁጥጥር አነስተኛ ከሆነ ህዝብ ከመንግሥት በተቃራኒው ይቆማል በማለት ነበር። ይህ ምን ማለት እንደሆነ ግልፅ ነው መንግሥት ነፃ ሚዲያን አጥፍቶ የኮንስፓይረሲ ስራዎችን መሥራት ካልቻለ ህዝብ በአንድነት በመንግሥት ላይ ይነሳል እንደማለት ነው ስለዚህ ነፃ ሚዲያ የተባለ በሙሉ ዝግ ሆኖ የእነሰለሞን አስመላሹ ENN ቴሌቪዥን እና እነዛሚ የህወሃት ድምጽ ሆነው የመንግሥትን እድሜ ማራዘም አለባቸው ነው መርሃቸው።
ከላይ የገለፅኩት የENN ቴሌቪዥን አቋም በይፋ በትላንትናው እለት ታይቷል እንዴት ለሚለው አብረን እንመልከት።
 በመጀመሪያ ደረጃ ENN ቴሌቪዥን መቀመጫው አዲስ አበባ ነው በጉዳዩ ላይ ትክክለኛ መረጃ ለማግኘት ግጭቱ ወደተነሳበት አካባቢ ለመጓዝ የሚፈጀው የ7 እና የ8 ሰአታት መንገድ ሆኖ ሳለ ተጎጂዎችን አነጋገርኩኝ ያለው በስልክ ነው። ሰበር ዜናው ላይ የስልክ ቃለመጠይቁ ከጀርባው ብዙ ነገር አለው፤ የመጀመሪያው የተዛባ መረጃ ለማስተላለፍ አመቺ ሲሆን ሁለተኛው ምስል አልባ የስልክ ዘገባ በሰዎች አእምሮ ውስጥ የሚፈጥረው ነገር ብዙ መሆኑ ነው። ENN ወደስፍራው ተጉዞ ነገሮችን አጣርቶ ተጎጂዎችን ጠይቆ ዘገባውን ቢሠራ በዚህ ደረጃ የተዛባ መረጃ ማቅረብ ስለማያስችለው ነው አሁን እየሄደበት ባለው መንገድ መጓዝን የመረጠው።
 ሁለተኛው ሰበር ዜናው የቀረበበት ሁኔታ ነው፤ ሰበር ዜናው ሲቀርብ በታለመለት አላማ ብዙ ተመልካቾች የቴሌቪዥን ጣቢያውን የሚመለከቱበት ሰአት ተመርጦ ነው። እንደዚህ አይነት የተዛባ መረጃ ለማቅረብ የኢትዮጵያ ቡናና የቅዱስ ጊዮርጊስ ጨዋታ ትልቅ አጋጣሚ ነበረ ይህንንም አጋጣሚ ህወሃት በሚገባ ተጠቅሞበታል፤ ብዙ መነጋገሪያ እና የጊዜው አንገብጋቢ አጀንዳ እንዲሆን በማድረግ በኦሮሚያ የተነሳውን ህዝባዊ አመጽ በሌሎች ህዝቦች እንዳይደገፍ እንዲሁም ከኦሮሞ ህዝብ ጎን እየቆሙ ያሉት አዳዲሶች የኦህዴድ አመራሮች በተቀረው ህዝብ ጥርስ ውስጥ እንዲገቡ በማድረግና ለፍርድ አቀረብኩ በማለት ዘብጥያ ለመክተት ብሎም የፖለቲካ ትርፍ ለማጋበስ የተሠራ ትልቅ ድራማ ነው ለዚህ እንዲረዳም በENN ቴሌቪዥን የኦህዴድ አመራሮች ስለጉዳዩ ለህዝብ መግለጫ ለመስጠት ፍቃደኛ አይደሉም ሲሉ በመናገር ማሠሪያ ነጥብ አስመዝግበዋል። ብዙ ሠው የኦሮሚያ አመራሮች ለፍርድ ይቅረቡ እያለ የሚገኘውም የዚሁ የኮንስፓይረሲ ውጤት እያመጣ በመሆኑ ነው።
Filed in: Amharic