>

በኢህአዴግ ውስጥ የአርከበ እቁባይንና የለማ መገርሳን ያህል ምርጥ ፕሮፖጋንዳ የተሰራለት ባለስልጣን የለም (ዮናስ ሃጎስ)

 
አርከበ እቁባይ በአዲስ አበባ ውስጥ ያደርጋቸው የነበሩ አንዳንድ እንቅስቃሴዎቹ እስካሁንም ድረስ አወዛጋቢ ናቸው። ግማሾቹ አዲስ አበባ የአርከበን ያህል የሰራላት ከንቲባ በታሪኳ አላገኘችም ሲሉ ግማሾቹ ደግሞ የአርከበን ያህል የአዲስ አበባን መሬት የቸበቸበ የለም። ኃይለኛ ያልተነቃበት ዘራፊ ነው ይላሉ። ያም ሆነ ይህ አርከበ በከንቲባነት ዘመኑ እጅግ በጣም ብዙ ፕሮፖጋንዳ ተሰርቶለታል። የሚገርመው ፕሮፖጋንዳው ይሰራለት የነበረው በተቃዋሚዎች ሲሆን በወቅቱ በነበረው ፈላጭ ቆራጭ መሪ ጋሼ መለስ ዜናዊ «አርከበ ማለት አስር ድስት ጥዳ…» አስተያየት ከባልቦላው እንዲጠፋ ከተደረገ በኋላ መለስ እስከ ሞተበት ጊዜ ድምፁን አጥፍቶ ለመኖር ተገድዷል።
ንግዲህ በተቃዋሚዎች ኃይለኛ ፕሮፖጋንዳ እየተሰራላቸው ያሉት አቶ ለማ መገርሳ ሌላኛው «አስር ድስት የጣዱ…» አርከበ ሆነው ጧት ማት ደጋፊዎቻቸው ፌስቡኩን በፕሮፖጋንዳ እያመሱት ይገኛሉ። አቶ ለማ ወደ ስልጣን ከመጡ ወዲህ በጥዑም አንደበታቸው ብዙ ጣፋጭ ቃላትን ያፈሰሱ፣ ብዙ ቃል ኪዳን የገቡና በውቅያኖስ መሐከል ያለች ጠብታን የምትመስል ስራን የሰሩ ሰው ናቸው። እየተሰራላቸው ያለውን ፕሮፖጋንዳ ስናየው ግን አቶ ለማ ወይ መዋጥ ከሚችሉት በላይ ጎርሰው እንዲታነቁ የፈለገ አካል አለ አሊያም ትኩረት በሙሉ ወደርሳቸው ዞሮ በፀጥታ ስራውን ለመስራት የፈለገ አካል አለ ወይ ደግሞ…
•°•
ወይ ደግሞ አቶ ለማ ሪቮልዩሽናሪ ለመሆን ቆርጠው ተነስተዋል ማለት ነው… ቂ ቂ ቂ ቂ!
•°•
የዛሬው አደንቋሪ ፕሮፖጋንዳ ደግሞ «አቶ ለማ ብሔርን ከመታወቅያ ላይ አነሱ!» የሚል ነው። ሲጀመር የኦሮሚያ አብዛኛው ከተሞች መታወቅያ ብሔር ተጠቅሶበት አያውቅም። ኧረ ከአዲስ አበባ ውጭ አብዛኛው ክልል መታወቅያቸው ብሔርን አይጠቅስም። ይህ ነገር ከዚህ በፊትም ተነስቶ የተለያዩ የክልል መታወቅያዎችን ለአብነት አይተንበታል። ስለዚህ በዚህ ረገድ አቶ ለማ ምንም የሚጨበጨብ ስራ አልሰሩም።
ባይሆን በቴሌ በኩል ፈጣሪ ይርዳቸው እንጂ የመታወቅያውን ነገር በማዕከላዊ ዳታ ቤዝ የተመዘገበ ሆኖ የመታወቅያን ማጭበርበር ለመቆጣጠር የጀመሩት ጥረት ይበል የሚያሰኝ ነው። የመሬት ይዞታን ዲጂታላይዝ ምዝገባ እንዲሆን ማድረግ ምንም እንኳን ቀድሞም በአዲስ አበባ የተጀመረ አሰራር ቢሆን ወደ ኦሮሚያ ክልል እንዲስፋፋ ማድረጋቸው ያስመሰግናቸዋል። ሌሎች ክልሎችም የቴሌ መሰረተ ልማት ከረዳቸው ይህን በማድረጋቸው የሚጎዱበት ነገር ስለማይኖር ሊበረቱበት ይገባል።
•°•
ከዚያ በተረፈ ግን ዝም ብሎ ፕሮፖጋንዳ መንፋት ምንም ትርጉም የለውም። ዶክተር ዳኛቸው OBN ላይ ቀረቡ ብላችሁ የምታናፉ ሰዎች ዶክተሩ የዛሬ ዓመትም አማራ ክልል ቴሌቭዥን ላይ ቀርበው ነበረ። ዶክተሩ የሸገር ራድዮ ደንበኛ ናቸው። የኦሮሚያ ክልል ለረዥም ዓመታት ታጥሮ የነበረ መሬት ወደ መሬት ባንክ ተመላሽ እንዲሆኑ አደረገ… አዲስ አበባም ሌሎች ክልሎችም ይህን ዓይነት ዜና ደጋግመን ሰምተናል። ችግሩ እነዚህ ወደ መሬት ባንክ የተመለሱትን መሬቶች ማን እንደሚቀራመታቸው አይነግሩንም። ልክ ባለፈው ተያዘ የተባለው ዶላር ፍርድ ቤት በወሰነለት መልኩ ለሶማሊ ክልል ተፈናቃይ የኦሮሚያ ተወላጆች እንዲውል ተብሎ ያ ሁሉ ፕሮፖጋንዳ ጥሩንባ ከተነፋ በኋላ ገንዘቡ አንድም በጥሬ ተሰጣቸው አሊያም እዚህ ቦታ ሰፍረው እንዲኖሩ መሬት ተገዛለቸው… ምናምን የሚል ዜና አፍጥጠን ጠብቀን እንዳላገኘነው ማለት ነው።
•°•
ኢና ሚን ለማሌት ኖ…
ምን ጊዜም ቢሆን ከፕሮፖጋንዳው ጀርባ ያለውን እውነታ እንፈልግ። ነገሮችን እኛ ከማጮህ ይልቅ ስራው ይጩህላቸው። የተሰራ ነገር ማንም ፕሮፖጋንዳ ሳይሰራለት ሲጮህ ያምራል። እኛ ብንጯጯህ እናፈርሳለን እንጂ አንገነባም።
Filed in: Amharic