ኢትዮጵያ: ከእልቂት አምልጠው የሙጥኝ ላሏት የአርመን ስደተኞች ዜግነት ትሰጥ ነበር :: አንዱ የዜግነት ተቀባይ አቶ ሰርኬዝ ሲሆን በፓስፖርቱ ላይ የሚከተለው ፅሁፍ ሰፍሯል:-
“ሞአ አንበሳ ዘ እምገደ ይሁዳ ዳግማዊ ምኒልክ ስዩመ እግዚአብሄር ንጉሰ ነገስት ዘኢትዮጵያ
ሰርኪስ ተረዚያን አገሩ አርመን የተወለደበት ከተማ አረብአገር : እድሜው ሰላሳ ዘጠኝ አመት: ቁመቱ መካከለኛ : ጠጉሩ ከርዳዳ ላዛ: ፊቱ አጭር: በግራ አገጩ ለምፅ ያለበት ነው:: ለመንግሥቴ ለኢትዮጵያ ሎሌ ሆኖ ብዙ ቀን አገልግሎኛልና ከንግዲህ ወዲህ ቁጥሩ የሀበሻ ሰው ነው:: በሚሄድበት አገር ሁሉ ክፉ ነገር እንዳያገኘው የኢትዮጵያ መንግስት ዜጋ መሆኑን ለማስታወቅ ይህን ባስቡርት ሰጥቸዋለሁ”
(የፓስፖርቱን ወሪጂናል ባሰተያየት መስጫ ሳጥኑ ውስጥ ይመልከቱ)
የታሪክ ምፀት ይሉሃል ይሄ ነው:: መድረሻ ያጡ ጠጉረ ልውጦችን ያስጠጋ የነበረ ህዝብ ዛሬ ራሱ መድረሻ አጥቷል::
ሰርኪስ ያስመጣው ባቡር ስሙን ወርሶ “የሰርኪስ ባቡር “ይባል ነበር:: ባቡሩ በዛሬው አይን ሲታይ ካንድ ግዙፍ ቡልዶዘር አይበልጥም :: ያም ሆኖ በጊዜው እንደ ብርቅ እንደ ትንግርት ይታይ ነበር::
የሰርኬስ ባቡር ትንሽ እንዳገለገለ ተሰናክሎ ተገትሮ ቀረ:: ባለ ባቡር የነበረው አርመናዊም ባለበቅሎ ሆኖ ቀጠለ:: የሰርኪስ ባቡር የፍጥነት ምሳሌ መሆኑ ቀርቶ የቁሞ ቀርነት ምሳሌ ሆነ:: የዚያን ዘመን ያራዳ አዝማሪ:-
ብነግርሽ ብነግርሽ አታጠናቅሪ
እንደ ሰርኪስ ባቡር ተገትረሽ ቅሪ
ብሎ መዝፈኑ ተመዝግቧል::
አሁን እዚህ ዘመን ላይ ቆሜ ሳስበው “ተገትረሽ ቅሪ “ተብላ ባዝማሪው የተረገመችው ማን ትሆን? ያዝማሪው ፍቅረኛ ? ወይስ ያዝማሪው አገር?