>
5:13 pm - Saturday April 19, 3862

እንጨት ለቃሚው ብአዴን! (ጌታቸው ሽፈራው)

~“የአማራ ደን ኢንተርፕራይዝ ባይኖር የማይጨው ችቡድ ፋብሪካ ይዘጋ ነበር”
(የባህርዳር ወጣት ያጫወተኝ ነው)
እየውልህ! የአማራ ደን ኢንተርፕራይዝ የሚባል አለ። ኢንተርፕራይዝ ስለሆነ ፌደራል መንግስቱ ነው የሚወስንበት። ጨረታ አውጥቶ የሚሸጠው ፌደራል መንግስት ነው። የሚያሸንፉት ደግሞ የህወሓት ሰዎች ናቸው። (ህወሓት የሚለውን የተጠቀምኩት እኔ ነኝ፣ እሱ “ቻይናዎቹ” ይላቸዋል።)
ይህ ደን የአማራ ደን ኢንተርፕራይዝ የሚባለው እየቆረጠ የሚሸጠው በደርግ ዘመን የተከለለለውን ጭምር ነው። እየከለለ፣ እየቆረጠ ይሸጣል። የሚሸጠው ለችቡድ ነው። ችቡድ ፋብሪካው ትግራይ ነው ያለው። ለምሳሌ እኔ አንድ እንጨትን ማይጨው ለማድረስ 10 ብር ይከፈለኛል። በአጠቃላይ ፋብሪካው ለአንድ እንጨት 59 ብር ወጭ ያደርጋል። ሁለቱ እንጨት አንድ ችቡድ ይሆናል። አንድ ችቡድ ደግሞ ከማይጨው ተጭኖ ወደ ባህርዳር ይመጣልሃል። ስንት እንደሚሸጡልን ታውቃለህ? 460 ብር! እኛው ቆርጠን፣ እኛው አድርሰን… …340 ብር ያተርፉብናል። ይህ እንግዲህ ከ2 እንጨት ነው። የአማራ ደን ኢንተርፕራይዝ የሚባለው ባይኖር የትግራይ ችቡድ ፋብሪካ ይዘጋ ነበር።
እንደምልህ ብአዴን እንጨት በመሸጥ የሚተዳደር ድርጅት ነው። እንጨት ለቅሞ የሚሸጥ ድርጅት ማለት ብአዴን ነው።
“እንዲያው ባህርዳርስ ምን ተሰራላት?” ልትል ትችላለህ። ብቸኛው ያለንኮ ጣሊያን ለደም ካሳ የተከለው የጨርቃጨርቅ ፋብሪካ ነው። ረስቸው! ሌላም አለ። ቀለም መበጥበጫ አለን። የቀለም ፋብሪካ ይሉታል። ቀለም ፋብሪካ የሚሉት ቀለም መበጥበጫውን ነው ፋብሪካ ሊባል አይችልም። ይህ ቀለም መበጥበጫ ብዙ ሰው አይቀጥርም።
ሌላም አለን። ወፍጮ ቤት ሞልቷል። ሲሰድቡን ይመስለኛል። ይገርህማል፣ እናቴም ወፍጮ ነበራት። ያውም ባለ 6ቋት። አንዱ በርበሬ፣ አንዱ ስንዴ፣ አንዱ ሽሮ፣ አንዱ ጤፍ……የሚፈጭ ነበራት። አሁን ከተማው ባለ አንድ ቋት ወፍጮ ሞልቶታል።
ሌላ ፋብሪካ የለም። ብአዴንም እንደነገርኩህ እንጨት ለቅሞ የሚሸጥ ድርጅት ነው! ብአዴን ባይኖር፣ የአማራ ደን ኢንተርፕራይዝ የሚባለው ባይኖር የማይጨው ችቡድ ፋብሪካ ይዘጋ ነበር።
Filed in: Amharic