>

ከትግራይ አፓርታይድ አገዛዝ ጋር የሚደረገውን ፍልምያ ዉስብስብነት ካልተረዳን፣ በቲም ለማና በኦህዲድ ላይ ትችት ከመሰንዘር መታቀብ ይገባናል። (ሃራ አብዲ)

ወቅቱ የመረጃ ፍሰት የመላበት በመሆኑ፣ ከዚህም ከዚያም የሚገኙ ወቅታዊ ክስተቶችን አጣፍጦና ከሽኖ ለህዝብ ጆሮ ለማድረስ የሚደረገዉ ሽምያ በራሱ፣ ከአጭር ርቀት የሩጫዉድድር ባልተናነሰ ፍጥነት ይካሄዳል ቢባል ግነት የለዉም። ይህም ባልከፋ ነበር።አሳሳቢ እየሆነ የመጣዉ ነገር ግን የነገሩን ጫፍ በማንጠልጠል በግልቢያ ሚሰራዉ የዜና ትንታኔም ሆነ ትችት ፣ያለንበትን ሁኔታና የኢትዮጵያ ልጆች ከትግራይ አፓርታይድ ጋራ የሚያደርጉትን የሞት ሽረት ትንቅንቅ በብዙ እጥፍ አቅልሎ የሚያሳይ መሆኑ ነዉ።
በተለይም፣ ለሚዲያዉ የቀረቡ ፕሮፌሽናል ጋዜጠኞች እንደዚህ አይነት የፋስት ፉድ (fast food) ዜና አቅርቦት ላይ ሲጠመዱ ማየት ግምት ዉስጥ  ያስገባቸዋል።
በቅድምያ; ኦህዴድ በቁርጠኝነት የሚያደርገዉን ተጋድሎ በመገንዘብ የድጋፍ ሃሳባችሁን በመለገስ ላይ ለምትገኙ የሚዲያ ባለሞያዎችም ሆነ የፖለቲካ ተንታኞች ምስጋናዬ ይድረሳችሁ።
የዚህ ጽሁፍ አላማ ; ከህወሃት ጋር ትንቅንቅ በማድረግ ላይ በሚገኙት ግለሰቦች፣ ቡድኖችና የፖለቲካ ድርጅቶች ላይ ትችትና ሃሳብ ስንሰነዝር፣ በዋናነት ማተኮር ያለብን በሃይል አሰላለፉ ላይ ተመርኩዘን እንዲሆን ለማሳሰብ ነዉ።

ለዚሁም፣ ህወሃት በሀገራችን የዘረጋዉን የዉስጥ ቅኝ አገዛዝ ( አፓርታይድ) ምንነት ጠለቅ ብለን ማየት ያስፈልጋል። «ኦሁዴድ በጅብ ተከቦአል»…«ከጨዋታ ዉጭ ተደርገዋል»…እያላችሁ የምታራግቡ ሰከን
በሉ። ነገሩ እንዲህ ነው።ህወሃቶች:-
1, ዋና ዋናዎቹን የመንግስት ስልጣን ማለትም፤ እንደ መከላከያ ፣ የሀገር ዉስጥ ደህንነት የዉጭ ጉዳይ ና ሌሎችንም ቁልፍ ሃላፊነቶች ፣ ከበረሃ ባመጡዋቸዉ ሽፍቶች ሞልተዋል።
2, በየእርከኑ የሚገኙ የሚኒስትር መስርያቤቶችን፣ላእላይና ታህታይ መዋቅሮችን ከፊሉን ያለ ይሉኝታ የአማራ ወይንም የኦሮሞ ስም ባወጡላቸዉ የትግራይ ተወላጆች አስይዘዋል።

3, የተቀረዉን ከፊል ደግሞ፤ በሽፍትነት ዘመናቸዉ በምርኮ የገቡላቸዉን ፣ በሂደትም በተለያየ ጥቅማጥቅም አስረዉ የስልጣናቸዉ ዘብ ጠባቂ ያደረጉዋቸዉን በቀጥታ በማዘዝ በመላ ሀገራችን የሚገኘዉን ሃብት እየዘረፉ ጡንቻቸዉን ለማፈርጠም ተጠቅመዉባቸዋል።
4, ሕወሃት /ትህነግ( የትግራይ ህዝብ ነጻ አዉጭ ግንባር) ኢትዮጵያን በዉስጥ ቅኝ አገዛዝ እየገዛ እንጂ እንደ መንግስት ኢትዮጵያን እያስተዳደረ አይደለም።
5, የራሱን ብሄረሰብና የፈለቀበትን አካባቢ ከሌላዉ የሀገሪቱ ክፍል ለይቶ በግልጽ መድልዎ (የአፓርታይድ ስርአት) ትግራይንና የትግራይን ህዝብ ተጠቃሚ ማድረግ መነሻ አላማዉና መድረሻ ግቡ ነዉ።
6, ይህ የአፓርታይድ ስርአት በኢትዮጵያና በህዝብዋ ጫንቃ ላይ ከተቆናጠጠ እነሆ ሃያ ሰባት አመቱን ሊደፍን ነዉ። የትግራይ ነጻ አዉጭ ቡድን ትንሽ አንገታቸዉን ቀና አድርገዉ ለመብታቸዉና ለሀገራቸዉ የሚቆረቆሩትን ፣ኢ-ሰብአዊ በሆነ መንገድ እየጨፈጨፈ ብቻዉን አምባ ገነን ሆኖ ያለ አንዳች ሞጋች በብረት ክንድ ይገዛል።
ይህንን የኢኮኖሚ፣ የጦር ሃይልና የስለላ ድርጅት ባለቤት የሆነ፣ የትግራይ ነጻ አዉጭ ድርጅትን ነዉ እንግዲህ ካለፉት ሶስት አመታት ወዲህ ህዝባችን በቃ ሲል ለለዉጥ በመትመም ላይ የሚገኘዉ። ከዚህ የለዉጥ ሀይል ካከል ደግሞ ኦህዲድ( የኦሮሞ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት) በቁልምጫ ስሙ ፣ቲም ለማ በዋነኛነት ይገኛል።
ማነቆዉን የሚያጠብቁበት የዉስጥ አርበኞች እየበዙ እንጂ ብአዴንም በትግሉ ዉስጥ እጁን በመስደድ ላይ ነዉ።
እንግዲህ፣ከህወሃት ጋር ትንቅንቅ በሚያደርጉት ላይ ትችት ለመሰንዘር ስንሞክር ያለዉን የሃይል ሚዛን ከግምት ማስገባት ያስፈልጋል ያልኩት ለዚህ ነዉ። አላስፈላጊ መስዋእትነት ከመክፈልና ትግሉን ከመበተን ለመዳን ለሚያደርጉት ጥንቃቄ ቦታ(space) መስጠት ግዴታችን ይሆናል።
አንዳንድ አስተያየት ሰጪዎች ኦህዴድ ከብአዴን ጋር ሆኖ ስብሰባዉን ረግጦ ይዉጣ ይላሉ። ሌሎች ደግሞ፤ ከስብሰባዉ መዉጣት ብቻ ሳይሆን ከኢህአዴግ ግንባር ቢወጡ የተሻለ አማራጭ ነዉ ይላሉ።እንዲህም፤ ሁለቱ ፓርቲዎች በፓርላማ አብላጫ ድምጽ ስላላቸዉ ህጋዊ በሆነ መንገድ ቢያንስ ለሽግግር ጊዜ የመንግስት ስልጣን ተረክበዉ መቀጠል ይችላሉ ሲሉ በልበ-ሙሉነት እስትራቴጂያቸዉን ይነድፋሉ። እነዚህ አስተያየት ሰጪዎች
ያስገርሙኛል!!
ለመሆኑ፤« በፓርላማ አብላጫ ድምጽ ስላላቸዉ» የሚባለዉ፤ የትኛዉን ፓርላማ ነዉ??
ይህ በድምጽ ብልጫ የወደቀን አጀንዳ ቁጥር ደልዞ እንዲያዉም ከሚፈለገዉ በላይ በሆነ ድምጽ አልፎአል ሲል ዜጎቻችን በጠራራ ጸሃይ የሚገደሉበትን የአስቸኩዋይ ጊዜ አዋጅ ያስጸደቀዉን ፓርላማ ነዉ ወይንስ ሌላ የማናዉቀዉ አለ??
ከቶዉንም ኦህዴድና ብአዴን የሽግግር ጊዜ የመንግስት ስልጣን ሲረከቡ የትግራይ ነጻ አዉጭ መከላከያ፣የት ሄዶ ነዉ? የስለላ መረቡስ? ፌደራል ፖሊሱስ? ልዩ ሃይሉ ?

ፋሽስቱ አጋዚ ጦር የት ሄዶ ነዉ? ( መቼም ኢትዮጵያ የጦር ሃይል እንደሌላት ይታወቃል ብዬ ነዉ) ከመቼ ወዲህ ነዉ ታዲያ ወያኔ በድምጽ ብልጫ ተሸንፌአለሁና እናንተለጊዜዉ ስልጣኑን ተረከቡ ሊል ይችላል ተብሎ የሚታሰበዉ??
የትግራይ ነጻ አዉጪ ለዝንተ-አለም በጫናቃችን ላይ እንደ ተባይ ተጣብቆ ደማችንን እየመጠጠ ይኖራል፤ የሚነቀንቀዉ ሃይል የለም እያልኩ አይደለም።የምለዉ ግን፤ እንዲህ እንደ አሁኑ ከየአቅጣጫዉ የህዝብ ሃይል ትንፋሽ ሲያሳጣዉ፤በሰላማዊ ትግሉም፤(በህዝብ እምቢተኝነት)፤በትጥቅ ትግልም፤በዲፕሎማሲም መስክ በተቀናጀ መልኩ በሚደረግ ትግል ተንኮታኩቶ ይወድቃል እንጂ፤ ኦህዴድና ብአዴን በፓርላማ በድምጽ ብልጫ
ያሸንፋሉ ማለት ከየዋህነትም አልፎ ጅልነት ነዉ።ነዉ።
እንግዲህ፤ ይህ ኦህዴድ ስብሰባ ረግጦ ይዉጣ….. ከብአዴን ጋር በመሆን የኢህአዴግን ግንባር ለቀዉ ይዉጡ….. እነ ለማ ስብሰባዉ ዉስጥ ምን ይሰራሉ? ለህወሃት እጅ ከሰጡ ስማቸዉ በአስነዋሪ የታሪክ መዝገብ ላይ ይጻፋል….ከግንባሩ ቢወጡ የሚከፍሉት መስዋእትነት ጊዜያዊ ነዉ…..ምናምን …በማለት ከርቀት በዉክቢያ ዜና የተጠመዳችሁ ግለሰቦች የቲም ለማ ኦህዴድ በሚያስደንቅ ጀግንነት ለኢትዮጵያ ህዝብ
ትግል ታላቅ ድርሻ በማበርከት ላይ መሆኑን ረጋ ብላችሁ አስተዉሉ ማለት እፈልጋለሁ።
ቲም ለማ፤ በነፍሳቸዉ ተወራርደዉ ትግሉን ከዳር ለማድረስ ከህዝባቸዉ ጋር ትከሻ ለትከሻ በቆሙ ጀግኖች የተዋቀረ ነዉ። ማንም ለርካሽ ዘገባ ማጣፈጫ እንዲህ ባታደርጉ ወዮላችሁ ስላላቸዉ የሚቀይሩት አቁዋም የለቸዉም። ማንም ስላስፈራራቸዉ ወደሁዋላም ወደፊትም አይሉም።(peer pressure ለቅንጅትም አልበጀም!!) ቲም ለማ የሚያደርገዉ ተጋድሎ የሌሎች ታጋዮችን ትግል አዳምሮ ኢትዮጵያን ከትግራይ
አፓርታይድ አገዛዝ ያላቅቃታል ብለን ሚሊዮኖች ተስፋ እናደርጋለን። ለጊዜዉ ወያኔ በጠመንጃዉ አፈሙዝ እያጣጣረ በዚሁ ከቀጠለም፤ የቲም ለማ ኦህዲድም ሆነ የብአዴን ተራማጅ ክንፍ የቻለዉን ወርዉሮአል። ያለዉን የወረወረ ፈሪ አይባልም። ትግሉ ከደከመበት አንስቶ የበኩሉን ሩጫ መሮጥ የሌሎች ድርሻ መሆን አለበት።
በልጅነቴ ያሳደገችኝ እናቴ ያጫወተችኝ ትዝ አለኝ።

«ወንዱ በመቁዋሚያዉ አይረዳኝም ወይ፣ሴትዋ በማማሳይ አትረዳኝም ወይ፣ እኔ አበበ አረጋይ ግድ አለብኝ ወይ» አሉ ደጃዝማች አበበ አረጋይ።ከሰሞኑ ፤ ቲም ለማ፣ እነዚያን በምቀኝነት የነተቡ ጉፋያዎች ወጥረዉ እንደያዝዋቸዉ ሰማን። ጀግናዉ ዶክተር አብይ « የማንም ቧንቧ ለመሆን ፍላጎት የለኝም» ሲል እንደተናገረም ሰማን።
ወያኔዎችም፤እንደ ኦነግ ልቅምቅም አድርገን ዘብጥያ እናወርዳችሁአለን ብለዉ ተወራጩ አሉ።በዚያ ክፉ ዘመን፤የኦነግን ሰራዊት ትጥቅ አስፈትቶ በሴት ወያኔዎች እየነዳ መሳለቂያ እንዳደረገዉ ሁሉ አሁንም በራዳሩ ዉስጥ ባስገባዉ ቲም ለማ ላይ ተመሳሳይ እርምጃ ለመዉሰድ ወያኔ አሰፍስፎ እንዳለ ልንረዳ ይገባል።
የግል አስተያየት መስጠት ከልካይ ባይኖርበትም፤ በቲም ለማ ላይም ሆነ በማንኛዉም ወያኔን በሚታገል ድርጅት ላይ ትችት ስንሰነዝር ለትግሉ ጉልበት ለመሆን በሚያስችል መልኩ (positive reinforcement) ቢሆን ይመረጣል። አይዞን እንባባል እንጂ፣ ወዮልህ አይጠቅምም።
እያንዳንዳችን የአፓርታይድን ምንነት ላላወቀዉ ህዝባችን እያሳወቅን ትግሉን እናፋፍም። ዱላ የያዙ አስር ጎረምሶች አንድ ባዶ እጁን ራሱን የሚከላከል ወጣት ሲደበድቡ ብናይ፤ «ትሸነፍና ወዮልህ« ብለን ከዳር ቆመን የማናስደበድበዉ ከሆነ፤ «ወዮላችሁ» በቲም ለማም ላይ አይሰራም።
ኦሁዴድ በጅብ ተከቦአል…ከጨዋታ ዉጭ ተደርገዋል… እያላችሁ የምታራግቡ ሰከን በሉ።ጨዋታ፣ ጨዋታ የሚሆነዉ ሜዳዉ እኩል ሲሆንና የሀይል አሰላለፉ ሲመጣጠን ነዉ። ከዚያ የዘለለዉ ፣ትግል ነዉ…ፍልሚያ ነዉ…ክርፍስ ነዉ.. ጀግንነት ነዉ….ብቻቸዉን!!

መታ ቲም ለማ ኢራ ቡአ !!!

Filed in: Amharic