
አስገራሚው ነገር ትላንት “መንግሥታችን ልማታችን” ያሉ ሰዎች ባንዲት ጀምበር ተገልብጠው መንግሥትን ማጥላላት ሲጀምሩ እኛ ደግሞ ጠቅላይ ሚኒስትራችንንማ አትንኩ ማለት ጀምረናል። ነገ መንግሥታችንን ማለታችን አይቀርም። እንግዲህ ቦታ ተለዋውጠን እነዚህን የልማትና የአንድነትና የዴሞክራሲ ጸሮችን እምንቃወምበት ጊዜ ሩቅ አይሆንም። ይልቁንስ ቀልዱን ትተን መንግስት ሁልጊዜም መንግሥት ነው። በባህርዩም ወስላታ ስለሆነ ምንም ይሁን ምን መደገፍ የለሌበት ተቋም ነው። ሊከታተሉት ሊቆጣጠሩት ሊጠረጥሩት እሚያስፈልግ ተቋም መሆኑን ማወቅ ይኖርብናል። በመንግሥት ውስጥ ያሉ ሰዎችን ሀሳቦችን አንዳንድ ፕሮግራሞችና አገራዊ አቋሞችን መደገፍ እንችላለን መንግሥትን በጅምላ ከመደገፍ ግን በጅምላ መቃወሙ የተሻለ ይመስለኛል። መንግሥት ራሱን እሚደግፍበትና እሚያስደግፍበት ብዙ አቅም አለው። እንደ አብይ ያሉ ሰዎችን ማስተዋወቅና ህዝብ እንዲገዛቸው መሸጥ ማለፊያ ስራ ነው። እንዲያመልካቸው ማስገደድ ግን እነ አብይንም አገርንም መግደል ይሆናል። ያውም እኮ መንግሥታቸውን ሲያመልኩ በኖሩ ሰዎች ስንሰቃይ ከኖርበት ዘመን ገና አልተላቀቅንም። መንግሥትህ ውስጥ ሆነህ መንግሥትህን ተቃወም ማለትም ሲናገሩት መቅለሉ ጠፍቶን አይደለም። መንግሥት ውስጥ ሁሉ ያሉ ሰዎች መንግሥትን መቃወም ያለባቸው የመሆኑ ረቂት ጥበብ አጓግቶን ነው። ምርጫ ማለት ዋሽንግተንን እሚለወጥ ሰው ወደ ዋሽንግተን የመላክ ጨዋታ ሆኖ እምናየው ለዚህ ይመስለኛል። ሰዎቻችን የተመራረጡበት ምርጫ መሆኑ ቀርቶ ምርጫ በህዝብ እንዲሆን ማድረጉ ግን ገና ያልተፈጸመ መሠረታዊ ጥያቄ ይመስለኛል።