>

ለማ መገርሳ  “ዛሬ የመጣነው እንደከዚህ ቀደሙ እሳት ለማጥፋት ሳይሆን ተስፋን ለማብሰር ነው” 

አዲሱ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ዛሬ የረፋድ ውሏቸውን በአምቦ ከተማ አድርገዋል፡፡ የአምቦ ከተማ ነዋሪዎች የጠቅላይ ሚኒስትሩን ንግግር ለማድመጥ ማልደው ወደ አምቦ ዩኒቨርስቲ ስቴድየም ተምመዋል፡፡ በሀገር ባህል ልብሶች ያጌጡ እና የዶ/ር አብይ ምስሎች የታተሙባቸው ካኔቴራዎችን ለብሰው ወደ ስቴድየም የተጓዙም ነበሩ፡፡ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ አቀባበል ለማድረግ በተሸሞነሞኑ ፈረሶቻቸው ሆነው ወደ አደባባይ የወጡ በርካታ ፈረሰኞች እንደነበሩ የከተማይቱ ነዋሪዎች ለዶይቼ ቬለ ተናግረዋል፡፡ ከፈረሰኞቹ ውስጥ በአምቦ ዙሪያ ካሉ አካባቢዎች ጭምር የመጡ እንደሚገኙበት ገልጸዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ስልጣን ከያዙ ሁለተኛቸው በሆነው በዚህ ጉብኝት ምክትላቸውን አቶ ደመቀ መኮንን፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩን አቶ ወርቅነህ ገበየሁን እና የኦሮሚያ ክልል ፕሬዝዳንት አቶ ለማ መገርሳን አስከትለው ተጉዘዋል፡፡
ከሁለቱ የኢትዮጵያ ልጆች ቀድመው የተናገሩት ኦቦ ለማ መገርሳ ናቸው እንዲህም ብለዋል፥ “ዛሬ የመጣነው ለቅሶ ይዘን አይደለም፡፡ እንደከዚህ ቀደሙ እሳት ለማጥፋት ሳይሆን ተስፋን ለመናገር ነው” ማለታቸውን በስነ-ስርዓቱ የታደሙ ነዋሪ ለዶይቼ ቬለ ገልጸዋል፡፡
* ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ በመቀጠል፥
 “ከአምቦ ጀግንነት እና ትግልን እናማራለን፡፡ “አምቦ ከዚህ በኋላ የቱሪዝም፣ የባህል እና የፖለቲካ ማዕከል ትሆናለች፡፡ ካሁን በኋላ እንደበፊቱ በሌላ ነገር አትጠራም” ብለዋል።
እስከ እኩለ ቀን የዘለቀው ስነ ስርዓት ምን ዓይነት ችግር ሳይፈጠር መጠናቀቁን እድምተኞቹ ተናግረዋል፡፡
*ዘገባው የጀርመን ድምጽ ነው
Filed in: Amharic