>

''እነዚህን ማን ከሰው ይቆጥራል? እንደ አይጥ በመርዝ መፍጀት ነው እንጅ!” - ቤንቶ ሞሶሎኒ (ቅዱስ ማህሉ)

እነዚህን ማን ከሰው ይቆጥራል? እንደ አይጥ በመርዝ መፍጀት ነው እንጅ!”
የጣሊያን ንጉስ ኢማኑየል እና ቤንቶ ሞሶሎኒ
አርበኞቹ ኢትዮጵያዊያን ነፍጠኞች እንጅ ወሬኞች አልነበሩም። ነፍጠኛ ባይኖር ኖሮ ኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያዊያን የአዲሱ ጁሊየስ ቄሳር ንብረት ይሆኑ ነበር። አዲሱ ጁሊየስ ቄሳር ፈረንሳዮቹ እንደሚሉት በ’ሚኒሊክ ሌ ግራንዴ’ (ታላቁ ምንሊክ እንደማለት) ላይ እጅግ አድርጎ ቂም ይዟል። ራሱንም “አዲሱ ጁሊየስ ቄሳር” ሲል የሰየመው በታላቁ አጤ ምንሊክ የተዋረዱ አባቶቹን፣አያቶቹን እና አገሩን ታሪክ እንደ አዲስ ለማደስ ሲል ነው። አዎ! ‘አዲሱ ጁሊየስ ቄሳር’ የዘመኑ የጣሊያን ጠቅላይ ሚንስትር የነበረው ቤኔቶ ሞሶሊኒ ነው። ቤኔቶ ሞሶሎኒ የጣሊያንን እና የነጮችን ታላቅ ክብር የናዱት ኢትዮጵያዊያን ላይ የማያዳግም የበቀል ርምጃ ወስዶ ህዝቡን ምርኮኛው ለማድረግ ዝግጅቱን እያጠናቀቀ ነው። በወቅቱ ጣሊያን እና ኢትዮጵያ የሊግ ኦፍ ኔሽን እና የኬሎግ ፓክት ስምምነት አባል የነበሩ ሲሆን ይህ ስምምነት አባል ሃገራት ርስበርስ ጦርነት ውስጥ እንዳይገቡ ይከለክላል። ይህ ግን ለበቀል ሕልሙ የፋሽዝምን ውጥን ለጠነሰሰው ቤኔቶ ሞሶሎኒ የሚያግደው አልነበረም። ንጉስ ኃይለስላሴ ለሊግ ኦፍ ኔሽን አቤት አሉ። አጤ ኃይለስላሴ እንግሊዝ እና ፈረንሳይ ጣሊያንን እንዲያስቆሙላቸው ጠየቁ። ሁለቱ ሃገራት ለኢትዮጵያ ምንም ማድረግ ሳይችሉ ቀረ። ለዚህ ምክንያቱ ከአሜሪካ ድጋፍ እና ይሁንታ ውጭ የሁለቱ ሃገራት ጣልቃ ገብነት ትርጉም የለሽ ስለነበር ሲሆን አሜሪካ ደግሞ ራሷ ባቋቋመችው የሊግ ኦፍ ኔሽን ውስጥ አባል አለመሆኗ በጉዳዩ ቀጥተኛ ተዋናይ እንዳትሆን አድርጓታል። በአሜሪካው ፕሬዝዳንት ውድሮው ዊልሰን አማካይነት የአንደኛውን የዓለም ጦርነት መገባደድ ተከትሎ የተቋቋመው ሊግ ኦፍ ኔሽን በዋናነት አሜሪካን በሌላ ሃገር ጦርነት ውስጥ እንዳትገባ ለማቀብ በሚል ምክንያት ነበር።
ጣሊያናዊያን በአባቶቻችን የተዋረደውን ክብራቸውን ሊያስመልሱ ኢትዮጵያዊያንም የአባቶቻቸውን ክብር ለማስጠበቅ ውጊያው የማይቀር ሆነ። የሞሶሎኒን ታንኮች በባዶ እግራቸው የሚሄዱ ነፍጠኞች ተጋፈጧቸው። አጤ ኃይለስላሴ “ድንበሬ በሰላቶ እንዳይሸራረፍ እንግሊዝ የተቻላትን ታድርግ” ሲሉ መወትወታቸውን አላቆሙም። ንጉሱ ጣሊያን በኢትዮጵያዊያን ላይ ቦምብ ለማውረድ የሚረዷትን የጦር አውሮፕላኖች ማጓጓዟን እንዲያስቆሙላቸው የዓለምን ሃያላን ተማጸኑ። ይህን ካላደረጋችሁ ታሪክ ይፈርዳል አሉ። እጅግ ዘመናዊ የጦር መሳሪያዎች እና አውሮፕላኖች የታጠቀው የፋሽስት ጦር አሮጌ መውዜር እና ምንሽር፣ጎራዴ፣ ጋሻ እና ጦር በያዙ ኢትዮጵያዊያን አሳሩን ያይ ገባ። ጣሊያን መግቢያ ቀዳደው፣መውጫ ማምለጫው ጠፋበት። ሲጨንቀው ጊዜ በኢትዮጵያዊያን ላይ የመርዝ ጋዝ አዘነበባቸው። የተከዜ ወንዝ ቀይ እስኪሆን ድረስ ኢትዮጵያዊያን ደማቸው ፈሰሰ። የባዲራችን ቀይ ቀለም ስለ ኢትዮጵያ እና ስለ ነጻነት ሲፈስ የኖረውን፣የፈሰሰውን እና የሚፈሰውን የኢትዮጵያዊያን ደም እና መስዋዕትነት እንደሚወክል ስንቶቻችሁ ታውቆ ይሆን? የጣሊያን ንጉስ ኢማኑየል እና ሞሶሎኒ ውስኪ እየተራጩ በኢትዮጵያዊያን ላይ ተሳለቁ። “እነዚህን ማን ከሰው ይቆጥራል? እንደ አይጥ በመርዝ መፍጀት ነው እንጅ!” እያሉ አላገጡ። ኢትዮጵያዊያን በዚህ መንገድ እየራባቸው፣እየጠማቸው ሲዋጉ በአንጻሩ ሌሎች ጥቂቶች ሆዳቸውን እየሞሉ ለሞሶሎኒ ምስል እየሰገዱ በአርበኞች እልህ አስጨራሽ ተጋድሎ ግራ የተጋባውን ጣሊያን መንገድ ይመሩ ነበር። እንዲህ ያሉት ኢትዮጵያዊያን ባንዳ በመባል ይታወቃሉ።
“ባንዳና አህያ ሁለቱ አንድ ናቸው
ጋማና ጅራት ነው የሚለያያቸው” የተባለውም ስለዚህ ነው።
የሆነ ሆኖ የአጤ ኃይለስላሴ ንግግር እውነት ነበር። ታሪክ በቁማቸው ፍርዱን አሳያቸው። አውሮፓዊያኑ ላይ የአዶልፍ ሂትለር እሳት እዚህ ቀረ ከማይባል ግፍ ጋር ይዘንብባቸው ያዘ። ናዚ ጀርመን ከእንግሊዝ በስተቀር ድፍን አውሮፓን በምርኮ ያዘ። ያልወረራቸው ጥቂት ሃገራት አንድም በግዛታቸው ውስጥ ናዚ መተላለፊያ መንገድ እንዲያገኝ ፈቅደዋል አሊያም ለሚያደርገው ጦርነት ድጋፋቸውን ችረዋል ወይም ደግሞ “ጥይት አታዝንብብን እንጅ የፈለከውን አድርግ” ብለውት ንቆ የተዋቸው ናቸው። ናዚ ፈረንሳይን እንደ ቡሄ ቤት አፈራረሳት። ኢትዮጵያዊያን ያለማንም እገዛ በዱር በገደል እየወደቁ ፋሽስትን ማርበድበድ ቀጥለዋል። ናዚ ጀርመንም አውሮፓዊያንን ሲኦል ምን ሊመስል እንደሚችል በምድር ላይ ያሳያቸው ይዟል። በአውሮፓ የሂትለር እሳት ተባብሶ በተቀጣጠለበት ወቅት የኢትዮጵያ አርበኞች እጅግ መራራ የሕይወት ዋጋ ከፍለው ኢትዮጵያችንን ከፋሽስት መንጋጋ ነጻ አወጧት። ጣሊያን በኢትዮጵያ ምድር በድጋሚ ተሸነፈች። ኢትዮጵያን በአፍሪካ ለማንም ወራሪ ያልገበረች ብቸኛ ሃገር አደረጓት። ጣሊያን እና ጣሊያናዊያንም ሽንፈታቸውን ሊቀበሉ ግድ ሆነ። ከኢትዮጵያ በተባረረች ማግስት ከሂትለር ጋር ያበረችውን ጣሊያን ለመቅጣት የአሜሪካ ጦር የጣሊያንን ድንበር ጥሶ በቀናት ውስጥ ሮምን ተቆጣጠረ። ጣሊያን በሃገሯም ላይ ዳግም መራራ ሽንፈት ልትጎነጭ ግድ ሆነባት። ቤኔቶ ሞሶሎኒ እምጥ ይግባ ስምጥ ደብዛው ጠፋ። በመጨረሻም ተደብቆ ከኖረበት ጉድጓድ ወጥቶ በጀርመን ደህንነቶች ከለላ ሊያመልጥ ሲል በአሜሪካ ወታደሮች ድንበር ላይ ተይዞ ለጣሊያናዊያን ተላልፎ ተሰጠ። ጣሊያናዊያን ውርደት ያተረፈላቸውን ቤኔቶ ሞሶሎኒን ዘቅዝቀው ሰቀሉት። በነገራችን ላይ ኢትዮጵያዊያን ያለማንም እገዛ የጣሊያንን የቅኝ ግዛት ህልም ሲያጨነግፉ በጀርመን ፍዳቸውን ከሚያዩት አውሮፓዊያን አንዳቸውም እንኳ ያለ አሜሪካ የገንዘብ፣የስንቅ፣የሎጅስቲክ እና ቀጥተኛ ወታደራዊ ድጋፍ ራሳቸውን ነጻ ማውጣት አልቻሉም ነበር። ታዲያ ደማቸውን አፍስሰው አጥንታቸውን ከስክሰው የውርደት ማቅ እንዳንለብስ ላደረጉት ነፍጠኞቹ ኢትዮጵያዊያን ታላቅነት ደጋግሜ ብጽፍ ምን ይገደኛል? ማንስ ተው ይለኛል? እዚያው ጣሊያን ሃገር ሮም ውስጥ የሃገሬን ባንዲራ በኩራት እንዳነሳ እና ቀና ብየ እንድሄድ ላደረጉኝ ነፍጠኛ አያቶቼ ዘላላማዊ ክብር ይሁን እላለሁ።በቃላት ከዚህ በላይ መግለጽ ብችል ምንኛ ደስ ባለኝ ነበር። አዎ! ለጀግናዎቹ አርበኞቻችን ዘላለማዊ ክብር ይሁን!!!!!!!
Filed in: Amharic