>

"የኢትዮጵያ እናቶች ይጸልዩልኛል"፤ዶ/ር አብይ ከአስለቃሽ ወደ እንባ አባሽ (ያሬድ ሀይለማርያም)

“የኢትዮጵያ እናቶች ይጸልዩልኛል”፤ ዶ/ር አብይ
 ከአስለቃሽ ወደ እንባ አባሽ
ያሬድ ሀይለማርያም
ሁል ጊዜ ሰዎች በተገደሉ፣ በጅምላ ወጣቶች እየታፈሱ በየማጎሪያው በተጣሉ ቁጥር፣ ሰዎች ታፍነው የደረሱበት ሳይታወቅ ቀረ በተባለ ቁጥር ከተጎጂዎቹ በፊት ወደ አዕምሮዮ የሚመጡት የኢትዮጵያ እናቶች ናቸው። ደርግ ያስለቀሳቸውን፣ ማቅ ያስደፋቸውን እና ጧሪ ያሳጣቸውን በሺዎች የሚቆጠሩ እናቶች ማጽናናት ያልቻለች አገር ከሃዘኗ ሳትወጣ ነበር በወያኔ እጅ የወደቀችው። የኢትዮጵያ እናቶች አሁን ልናርፍ ነው፤ እንባችን ሊታበስ ነው፤ ጧሪም ልናገኝ ነው ብለው እዝጌርን አመስግነው ሳይጨርሱ ሌላ አሳቃቂ፣ አስለቃሽ፣ ማቅ የሚያስደፋ እኩይ ሥርዓት ላይ ጣላቸው።
ወያኔም ከደርግ ባልተናነሰ በብዙ ሺ የሚቆጠሩ እናቶችን ደም እንባ አስለቀሰ። በ፪፯ ዓመታት ውስጥ በኢትዮ-ኤርትሪያ ጦርነት ያለቁትን በአሥር ሺ የሚቆጠሩ ወጣቶችን ጨምሮ በብዙ ሺዎች የሚቆጠሩ የአገሪቱ የነገ ተስፋዎች በዚህ እኩይ ሥርዓት ተቀጩ። ብዙዎች ታስረው ለሥቃይ ተዳረጉ። ገሚሶቹ ቋሚ የአካል ጉዳኛ ተደረጉ። ባጠቃላይ ላለፉት አርባ አመታት የኢትዮጵያ እናቶች በመከራ ላይ መከራ ሲደራረብባቸው ቆየ።
ኢሰመጉ ውስጥ በሰብአዊ መብት ጥሰት አጣሪነት ባገለገልኩበት ወቅት ሁሌም ሰላም ይነሳኝ የነበረው የእነኚህ እናቶች ሃዘን እና እሮሮ ነበር። የሚገርመው ልጄ ታሰረ፣ ልጄ ተገደለ፣ ልጄ ታፈነ፣ ልጄ ተደፈረችብም፣ ለጄ ተደበደበ ብለው የልጆቻቸውን ብሶት ይዘው ለአቤቱታ ይመጡ የነበሩት እነሱ ስለነበሩ አባቶች ወዴት ሄዱ የሚል ጥያቄ አይምሮዮ ያነሳ ነበር። ብዙ ግዜ እናቶች ነበሩ ያለ ምንም ፍርሃት እና መሳቀቅ የልጆቻቸው ብሶት ይዘው አደባባይ በመውጣት አቤቱታ የሚያቀርቡት።
በአብዛኛው የአገሪቱ ክፍሎች ከጋምቤላ እስከ ሐረር፤ ከቤንች ማጂዞን እስከ ማይጨው፤ ከአርባ ምንጭ እስከ ደብረ ማርቆስ፤ ከደሴ እስከ ሞያሌ ከሌሎች የሥራ ባልደረቦቼ ጋር በመሆን የመብት ጥሰቶችን  ለማጣራት በተዘዋወርንበት ሁሉ የእናቶች ለቅሶ፣ ሃዘን እና ስቃይ ተመሳሳይ ነበር። ልጆቻቸውን በግፈኞች ተነጥቀው ጧሪ ያጡ፤ ባሎቻቸውን ተነጥቀው በከፋ ድህነት ውስጥ ሆነው ልጆቻቸውን ለብቻቸው የሚያሳድጉ እናቶች እልፍ ናቸው። በቅርቡ በኦሮሚያ ክልል ውስጥ ልጃቸውን ከገደሉባቸው በኋላ በአስከሬኑ ላይ ቁጭ እንዲሉ የታዘዙ እናትን ዽምጽ ከሰማን ብዙም ውለን አላደርንም። የኢትዮጵያ እናቶች የኢትዮጵያ መከራ መገለጫዎች  ናቸው።
ያን ሁሉ መከራ ላሳለፉ እናቶች ዛሬ የእኔ ጤንነት የሚጠበቀው በእናንተ ጸሎት ነው የሚል መሪ ሲያገኙ ምን ሊሰማቸው እንደሚችል እያሰብኩ ሲቃ ተናነቀኝ። ለአንድ አገር የመሪው ወይም ፖለቲካውን የሚዘውሩት ሰዎች ስብዕና ለሕዝቡ ጤና ውሎ ማደር ምን ያህል ወሳኝ እንደሆነ በቅርቡ መለስን እና ዶ/ር አብይን በማነጻጸር አጭር ነገር ጽፌ ነበር። ከብዙ አፍቃሪ መለሶች ስድብ እና የንዴት ምላሽ ደርሶኛል። ብዙዎቹም የመለስን ሊቅነት እና አለም ያደነቀው ሰው መሆኑን ሊመሰክሩልኝ ሞከሩ። ልጇን በመለስ ዘመን በግፍ ለተነጠቀች እናት የመለስ ምጡቅነት ምኗ ነው። እስኪ አንዳንድ ጊዜ እራሳችሁን ከጎሳም ሆነ ከካድሬ ከረጢት ውስጥ አውጥታችው እንደ ሰው አስቡ። ያኔ የዛች ልጇን በሥርዓቱ ኃይሎች ተነጥቃ የምትማቅቀው እናት ስቃይና ሰቆቃ ይገባችዋል። ሃዘኗ አጥንታችሁን ሰርስሮ ሲገባ ይሰማችኋል።
ሰው እራሱን በጎሳ፣ በኃይማኖት ወይም በሌላ የልዩነት አጥር ከልሎ እና ሌላውን ሰው ከሱ ውጭ ያለ ፍጡር አድርጎ ማሰብ ሲጀምር የስብዕናውን ግማሹን ያህል ያጣዋል። ግማሹን ያልኩት የኔ ለሚላቸው ሰዎች የሚያዝን ትንሽ ልብ ቀርታዋለች በሚል ነው። በዚህ ደዌ የተለከፈ ሰው የሚያዝነው፣ የሚከፋው ወይም የሚደነግጠው የእኔ ብሎ በከለለው አጥር ውስጥ ያለ ሰው ሲጎዳ ብቻ ነው። ደስ የሚሰኘውም እንዲሁ የእኔ ብሎ የሚያስበው ሰው ጥሩ ነገር ሲያገኝ ሲያይ ብቻ ነው። ከሱ ዘር ወይም ኃይማኖት ወይም ሌላ አይነት የማንነት መገለጫ አጥር ውጭ ያለ ሰው ሲጎዳ፣ ለጥቃት ሲጋለጥ ወይም አደጋ ላይ ሲወድቅ ምንም እንዳልተፈጠረ ነው የሚቆጥረው። እንዲህ ያለውን ስሜት ተደጋግሞ በማህበረሰባችን ውስጥ ሲስተዋል ቆይቷል። አንዱ የኪሳራችንም ጥልቀት መታያ ነው። ስለሚያለቅሱ እናቶች ስናወራ ስለ መለስ ምጡቅነት የሚያወሩትም ሰዎች የዚህ ደዊ ሰለባዎች ይመስሉኛል።
ለማንኛውም የኢትዮጵያ እናቶች የሚያስለቅስ ሳይሆን አብሯችሁ የሚያለቅስ፣ ቤታችሁን በላያችው ላይ አፍርሶ ከነልጆቻችሁ ሜዳ ላይ የሚጥል ሳይሆን ቤታችሁን የሚያድስ እና አብሯችሁ ማዕድ የሚቀርብ፣ ልጆቻችሁን ከአገር የሚያሳድድ ሳይሆን በየአገሩ እየዞረ ግማሹን ከስደት፤ ግማሹን ከእስር እያስፈታ እቅፋችሁ የሚያስገባ፣ ቆሎ ቆርጥማችሁ አሳድጋችሁና አስተምራችሁ ይጦሩናል ያላችዋቸውን ልጆች ካድሬ ካልሆናችሁ እያለ ሥራ የሚነፍግ እና ዲግሪ እየጫነ ድንጋይ የሚያስነጥፍ ሳይሆን በትምህርት እና በእውቀት ከራሳቸው ተርፈው ለአገር ኩራት እንዲሆኑ የሚያበረታታ እና ደብተር እያሲያዘ ተማሩ የሚል፤ አቁስሎ እና ገድሎ ለሀዘን አትቀመጡ፣ የጥይት ክፈሉ፣ የአስከሬን ማስመርመሪያ ክፈሉ፣ ባንክ ሲዘርፉ ነው የተገደሉት፣ አደገኛ ቦዘኔዎች እያለ በሃዘን ላይ ሃዘን የሚደርብባችው ሳይሆን ዛሬም እናንተን አንገት ለማስደፋት ክርናቸው ያልዛሉ ክፉዎች በልጆቻችሁ ላይ ጥቃት ሲሰነዝሩ የሚያጽናና፣ አብሮ የሚያለቅስና የሚጎበኝ መሪ ስላገኛችሁ እንኳን ደስ አላችሁ።
የዶ/ር አብይ እርህራሄ፣ ለሰው ልጅ ክብር እና መብት ተቆርቋሪነት እና አርቆ አስተዋይነታቸው ለቀሩት ባለሥልጣናት ትልቅ ትምህርት ይሆናል ብዮ ተስፋ አደርጋለሁ። ያለፉት መሪዎች እንዳይማሩ ሆነው አልፈዋል እና በክፉ ታሪካቸው ስናወሳቸው እንኖራለን። አለም በክፋታቸው የሚያወሳቸው ከእነናዚ ጀምሮ ብዙ ክፉ ሰዎች እንዳሉ ሁሉ በመልካም ሥራቸው ሲወሱ የሚኖሩም በርካቶች ናቸው። የሚያጠግብ እንጀራ ከምጣዱ ያስታውቃል እንደሚባለው ዶ/ር አብይም እስከ መጨረሻው በመልካምነት ሲወሱ የሚኖሩ ሰው ይሆናሉ ብዮ ተስፋ አደርጋለሁ።
ሰብአዊ መብትን በማስከበር፣ የሕግ የበላይነት እንዲረጋገጥ እና ኢትዮጵያ ውስጥ የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት እንዲሰፍን ለሚያደርጉት ጥረት የሁሉም ኃይል እገዛ እና ድጋፍ ያስፈልጋቸዋል።
Filed in: Amharic