>

በባሌና በጉጂ "ብሔራቸው ያልተረጋገጠ" ኢትዮጵያውያኖች በረሃብ አለንጋ እየተቀጡ ነው!!! (ዘመድኩን በቀለ) 

በባሌና በጉጂ “ብሔራቸው ያልተረጋገጠ” ኢትዮጵያውያኖች በረሃብ አለንጋ እየተቀጡ ነው!!!
 ዘመድኩን በቀለ 
 * እነ አቢቹ ሆይ ከብሄር ሰውነት ቢቀድምም  ለእናንተ ዋጋ ያለው ብሄር ነውና እናጣራለን የምትሉትን የዜጎቹን ብሔር አጣርታችሁም ቢሆን በቶሎ ድረሱላቸው!!!
•••
በዛሬዋ ኢትዮጵያ ለሚደርስብህ ማንኛውም በደል ሁሉ ከእግዚአብሔር ቁጣ በታች ዋነኛው ተጠያቂ የህወሓት ኢህአዴግ መራሹ የጎጠኞች ስብስብ ነው። እኔማ አንዳንዴ ሳስበው ህውሓትን የመሰለ ካንሰር ያመጣብን እኛ ኢትዮጵያውያን አባት አያቶቻችን ምን ቢበድሉ ነው ብዬም አስባለሁ። በእውነት እደነቃለሁ።
•••
በችሎታ ተወዳድሮ መቀጠር ከቀረ 27 ዓመት አለፈህ። ርቦህ እንኳ ምግብ ለማግኘት ብሔርህ ወሳኝ ነው። ብሔርህ አክቲቪስት ከሌለው ግን አለቀልህ በዚያው ነው እንደቅጠል የምትረግፈው። ከአንዳንድ ክልል የተፈናቀሉ ናቸው የተባሉ ብሔረሰቦች ሲገኙ እሽቃባጩ፣ የሚጮኸውና የሚሯሯጠው ብዙ ነው። አሸርጋጁም ብዙ ነው። የግመል ጭራ እየተከተለ በረሃብ የሚሰቃይ ክልል የሚመራው አብዲ ኢሌ እንኳ ከዚያችው ባጀቱ ላይ አውጥቶ ሲረዳ ይታያል። የራሱን ብሔር በውኃ ጥም እየጠበሰ ዘመደ ብዙ፣ ገንዘበ ብዙ ለሆነና ተራሩጦ ራሱን ማገገም ለሚችል ብሔር ሲያሽቃብጥ ይታይ ነበር። በነበር ቀረ እንጂ።
•••
ከባለፈው ከጌዲኦ ተፈናቃዮች በኋላ አሁን ደግሞ በኦሮሚያ ክልል ባለፈው ዘመን ከሶማሌ ክልል የተፈናቀሉ ናቸው የተባሉ ኢትዮጵያውያን ዜጎች በባሌ ክፍለ ሀገር በከፍተኛ ረሃብና ጉስቁልና ላይ እንደሚገኙ መረጃዎች እየወጡ ነው። እነዚህ ዜጎች በኦሮሞ ስም እንዲፈናቀሉ ተደርገው የቦለጢቃ ሥራ ከተሠራባቸው በኋላ አሁን ገሸሽ የተደረጉ ዜጎች ናቸው የሚሉ አሉ። በተፈናቃዮቹ ብሔር ላይ መንግሥት ከስምምነት ላይ ስላልደረሰ በቶሎ የሚረዱም አይመስለኝም።
•••
ገሚሱ ተፈናቃዮቹ ኦሮሞዎች ናቸው ሲል በዚህ ጉዳይ የማይስማሙ አካላት ደግሞ በፍጹም ዜጎቹ ኦሮሞዎች አይደሉም። ኦሮሞማ ቢሆኑ ኖሮ አሁን ያለው የኦሮሞ መንግሥት በቶሎ ይደርስላቸው ነበር። ተፈናቃዮቹ በኦሮሚያ ክልል የሚገኙ በደም የኢትዮጵያ ሶማሌ የሆኑ ዜጎች ናቸው። እናም የእነ አብይ መንግሥት ችላ ያላቸው ለዚህ ነው የሚል ሙግት ያቀርባሉ።
•••
እንደ ሲንጋፖር እንሆናለን ብለው የሊጥ ቡዋቃቸውን ሳይቀር ሳይከድኑ፣ ህንጻና ጋራዣቸውን፣ ኬክቤቶቻቸውን ጣጥለው አዲስ የበለፀገች ሀገር እንገነባለን ብለው ወደ አስመራ ኤርትራ ክተት ዐውጀው ሄደው በዚያው ያሰቡት ሳይሳካላቸው፣ ነዳጁ ቀርቶ አናዳጅ መንግሥት፣ እንጀራ ሳይሆን ገጀራ ስሎ አፈር ከድሜ ያበላቸውንና ድሃ የድሃ ድሃ አድርጎ ያደቀቃቸውን የኢሳይያሷን ኤርትራ ስደተኛ አሽሞንሙኖ አንቀባርሮ ይዞ የገዛ ወገነንን ሱማሌ፣ ዐማራ፣ ኦሮሞ ነህ ብሎ በረሃብ መፍጀት ይሄ የጤናማ መንግሥት ተግባር አይደለም።
•••
ደቡብ ሱዳኖች ተንደላቀው ከጋምቤላዊው በላይ ፏ ብትን ብለው እየተረዱ በሚኖሩበት ሀገር የገዛ ወገኔ ወይ ኦሮሞ ነህ፣ ወይ ሶማሌ ነህ ተብሎ በረሃብ መቀጣት የለበትም። የአቢይ አህመድ መንግሥትም ለ2 መቶ ሺህ ችግኝ 40 ቢልየን ብር አውጥቻለሁ ብለህ መሳቂያ ከመሆንህ በፊት ዜጎችን በረሃብ ከመርገፋቸው በፊት በቶሎ ድረስላቸው። ሰሞኑን ብቻ በባሌ ከ10 በላይ የሚሆኑ ህፃናት በረሃብ መሞታቸውም ነው እየተነገረ ያለው።
•••
ረሃብን ለቦለጢቃችሁ አታውሉት። በህዝብ ስቃይ አትነግዱ። በቃ ኦሮሞ ከሆኑም እርዷቸው። ሱማሌም ከሆኑ እርዷቸው። የተራበው ሰው ነው። በረሃብ ከመሞት ደግሞ በጦርነት መሞት ይቀላል። ይሻላልም። እናም በህጻናቱ አምላክ ይሁንባችሁ ለእነዚህ ወገኖች እንድረስላቸው።
•••
ያ ኢልማን ኦሮሞ ማሊፍ ጨሊስቲኒ ላለተን። ረኮ ከነ ማሊፍ ኦፒዲኦፊስ ሃተኡ አባኦ ዳፊስ ማሊፍ ሂሙ ደደብደን። ቄሮን ጀዴሙ ሱን አመ ኤሴ ጂራ? ማል ሆጀቹቲ ጂራ? ያ ቀማቱ ወዪ ሲላ ነመ ታተኒ ዬሮን ነማፍ ኢይተን አመ ቱሬ። አማ ማሊፍ ኢዩ ዲፍተን? ከንቤለያ ጂሩ ኡመተ ኬሰኒሚቲ? ዳኢመን ጢጢኖን፣ ጃርሶሊን ቢያ፣ ማንጉዶን፣ ሸመሬን ሁንዱ ቤለየኒ ጂሩ። ዋን ኡፈተን ኢንቀበን፣ ቢሻን ኢንጂሩ፣ ዋንኛተሙ ሚዻን ኢንጂሩ ጀኡ ነሞኒ በከ ረኮን ኩኒ ጂሩ ዱፈን ከኑመ ዱበቱ። ኢሲን ቆይ ሞርሚን ኬሰን ፊንፊኔ መጋላ ጎዶ ኦሮሚያ ቆፈ ጎዱፍ ወያኔ ወጂኒን ቀብሶዋ ቱርተን? በቃ ከኑማፍ ደርገጎን ኩማን ለካወመን አጋዚዳን አደ ሳኒ ሩከተመኒ ሃንዱአን። ከነሙፊጀቹዳ? አማስ ኢሲኒቲን ሂማ ዱቢ ቤላከነ ጨሊስተኒ ኢላሊና። ማንጉዶታ ወጂን ወልመሪአዳቲ መቃ ኦሮሞቲን ወረ ቤተ መንግሥቲ ሚኒልኪ ገለን ዐቢይ አህመዲ ፋ ጋፈዳቲ ደፋቲ ኡመተ ቤለዬ ከናፍ ዬሮን ኦዶ ኢንዱከናዪን ደቀባ።
•••
በጉጂም እንዲሁ፣ በወለጋም ረሃብ አለ እየተባለ ነው። የጃዋር ኦኤም ኤንም ሀብታም ከሆነ በኋላ ስለኦሮሞ ረሃብ መዘገብ አቁሟል። ገጽታ አባቱ ይጥፋና ገጽታ እንዳይበላሽ መሆኑ ነው። የቄሮ ትግልም ከህዝቡ ይልቅ አዲስ አበባ ዳቦ ትሆን ይመስል ፊንፊኔን ኬኛ ሲል ይውላል። አዲስ አበባ የሚሠራባት ያድግባታል። ኬኛ ስላልካት መና አታውርድልህም። ቄሮ ወገኑ ተርቦ አሁንም ወሎ ኬኛ ሲል ይውላል። ጎጃም ኬኛ፣ ጎንዶር ኬኛ፣ አክሱም አካሱማ ኬኛ ይልልሃል። ኬኛውን ትተህ መጀመሪያ ያሉትን፣ በቦታው ላይ የሰፈሩትን ኦሮሞዎች ነፍስ ታደጉ። ወገን ለወገን እንድረስ። ድምጽም እንሁናቸው።
•••
ደግሞ አንተ የሐረር ቆቱ ስለሆንክ ነው እንዲህ ለኦርሞ የምትጮኸው በለኝ አሉህ። እኔ ለወገኔ ሁሉ ድምጼን አሰማለሁ። #Yared_Shumete #ያሬድ_ሹመቴ ሆይእስቲ ብቅ በልና እንደፈረደብህ እንመካከር።
•••
ማስታወሻ | ~ በዚህ በጾም ፍልሰታ የጀመርነውን አጀንዳም አጠንክረን እንገፋበታለን።
★ እኔ ዘመዴም ከነሐሴ 1/2011 ዓም ጀምሮ ከራየን ወንዝ ዳር ወደ ራየን ወንዝ ማዶ ተዘዋውሬያለሁ። በዩቲዩብና ከዚያም ከፍ ባለ መንገድ ለመከሰትም መንገድ ጀምሬያለሁ። በጸሎታችሁ አስቡኝ። አክሊለ ገብርኤል።
•••
ሻሎም !   ሰላም !  
ነሐሴ 2/2011 ዓም
ከራየን ወንዝ ማዶ።
Filed in: Amharic