>

ይህች አገር በየዘመናቱ ዕብድ አታጣም (ግርማ በላይ)

ይህች አገር በየዘመናቱ ዕብድ አታጣም

 

ግርማ በላይ (gb5214@gmail.com)

 

ሆ! ምን ዓይነት አገር ናት ይቺ ኢትዮጵያ ግን?

ሲያቀብጠኝ የዚያን ወፈፌ ልጅ የዋለልኝ መኮንንን የአምስት ገጽ የዕብደት ጽሑፍ አሁን አነበብኩ፡፡ አንዳንዴ ምናልባትም ብዙውን ጊዜ የራሳችን የበሽታ ምንጮች እኛው ራሳችን ነን፡፡ ለምን አነበብኩ? ይበለኝ! ስህተቱ የኔው ነው፡፡

የኢትዮጵያን የመፈራረስና የመበታተን የማዕዘን ድንጋይ ያስቀመጠው “አማራው” ዋለልኝ መኮንን ስለመሆኑ ከዚህ ጽሑፍ የበለጠ ማሰረጃ ሊኖር አይችልም –  ነፍሱ አትማር፤ ሲዖልን ይውረስ – አሜን፡፡ ዋለልኝ ሰለጠነች ቢሏት የባሏን መጽሐፍ እንዳጠበችው ሴት ራሱ በሞረደው ቢላዎ የራሱን ነገድ ሸርክቶ ጣለው፡፡ ይህ ዕብድ ልጅ በዚያን ዘመን የነበሩ አንዳንድ ምሥራቃዊ መጻሕፍትን ማንበቡ ሳይጎዱት አልቀሩም፡፡ ፈረንጆች “ጥቂት ዕውቀት መጥፎ ነው” እንዲሉ እነዚያ ሶሻሊስታዊ ጽሑፎች ናላውን አዙረውት ከእውነቱ ለዩት፡፡ ለዩትናም ምስኪኑን የአማራ ሕዝብ ለአራጆቹ አሳልፎ እንዲሰጥ በውሻ ዕብደት ጭንቅላቱ ተነደፈ፡፡ ያ ዕብደትም ለኅልፈት አበቃው፡፡ የውሻ ዕብደት ትክክለኛና የማያዳግም በመሆኑ ዋለልኝም በያዘው ዕብደት ምድርን ተሰናበተ፡፡ ግልግል፡፡ ጦሱ ግን ለሀገራችን የዘመናት ስቃይ ዓይነተኛ ምክንያት ሆነ፡፡ 

የኢትዮጵያን በትረ ሥልጣን የያዙት እንደዋለልኝ ሁሉ በፖለቲካዊ ዕብደትና የአመለካከት ሽርሙጥና የተለከፉ እንደመሆናቸው ይሄው ዕብድ በታሪክ የሚዘከር ቁም ነገር ኖሮት በየስብሰባ ማዕከሉ ኮንፈረንስ እየተጠራ  50ኛ ዓመቱን በማስመልከት በሰሞኑ ይወደስ ይዟል – ግም ለግም አብሮ ማዝገሙ የነበረና ያለ ነውና እነዚህኞቹ የዕብድ ገላጋዮችም ለዚያኛው ዕብድ ጽላት ሳያስቀርጹለት አይቀሩም፡፡ “ባለጌን ካሳደገ ያነቀ ጠደቀ” መባሉ ትክክል ነው፡፡ እንደነዚህ ያሉት ጽንሶች ከማኅጸን ሳይወጡ ውኃ ቢሆኑ አገርና ሕዝብ እንዲህ መቅኖ ባላጡ፡፡ ለማንኛውም ጊዜው የሀፍረት የለሾችና የከሃዲዎች በመሆኑ እየሆነ ያለውን ሁሉ እኛም ዝም ብለን እንታዘባለን፡፡ ግን እግዚአብሔርና ታሪክ ራሱ ፍርዳቸውን የሚሰጡበት ወቅት በመቃረቡ ብዙም አንተክዝም – ለማንስ ይድላው ብለን? ሀገርን የሚበታትኑና የሚያፈራርሱ ግን ፀሐያቸው እየጠለቀች በመሆኗ በተለይ በአሁኑ ወቅት በከፍተኛ ደረጃ እየተቅበዘበዙ ይገኛሉ፡፡ ቀኒቱ ቀርባለች!!

ዋለልኝ ኢትዮጵያን ለማፈራረስ ሰይጣን በእጁ የሠራው ልዩ አጋንንታዊ ፍጡር ነበር፡፡ ከርሱም በኋላ መለስ የተባለ ዲያብሎስ ነበር፡፡ ከመለስም በኋላ ጃዋር የተባለ የባለሦስት ዓመቱ ወፍ ዘራሽ ሜንጨኛም አለ – ኦሮሞ ሳይሆን ኦሮሞን ከወንድም እህቶቹ የሚያባላ፤ እነሕዝቅኤልም፣ ዶ/ር ገመቹም፣ በቀለ ገርባም፣ ፀጋየ አራርሳም እንዳይረሱ ታዲያ፡፡ ቢገባን ሁሉም የኃጢኣታችን ፍሬዎች ናቸው፡፡ ከኃጢኣትና ከክፉ ሥራችን በቶሎ ተመልሰን ወደ ትክክለኛው የፈጣሪ መንገድ ካልገባን  ከነዚህ የባሱ እርጉሞች ገና አሣራችንን ያሳዩናል፡፡ የሀገራችን ችግር የሚፈታው በሰው መስሎን እንዳንጃጃል፡፡ በፈጣሪ ነው፡፡ የሰውን ነገር ብዙ ጊዜ አየነው፡፡ አይሆንም፡፡ እኛ ኢትዮጵያውያን እውነቱን ለመናገር ችግሮቻችንን እኛው በኛው ለመፍታት የታደልን አይደለንም፡፡ ሥልጣን ወዳድ ነን፡፡ ዝና ወዳድ ነን፡፡ ገንዘብና ቁሣቁስ ወዳድ ነን፡፡ ብዙዎቻችን በፍቅረ ንዋይ ታውረን በተለይ በአሁኑ ወቅት በንግዱና በፖለቲካው ዘርፎች ያለን ዜጎች ያላንዳች ይሉኝታ የወገኖቻችንን መቅኒ እየመጠጥን እንገኛለን፡፡ ይሉኝንና ሀፍረትን ባወጣ ሸጠናል፡፡ በተለይ የዚህ ዘመን ትውልዶች ከእግዚአብሔር ይልቅ ለገንዘብ እንሰግዳለን፤ ገንዘብንና ጠንቋይ አበጋርንም እናመልካለን፡፡ አስተሳሰባችን ከአፍ እስካፍንጫ ነው፡፡ ትግስት ብሎ ነገር፣ መቻቻልና መግባባት ብሎ ነገር፣ መደማመጥ ብሎ ነገር፣ በትምህርት መለወጥ ብሎ ነገር … አያውቁንም፡፡ በነዚህ ምትክ መናናቅና በተንኮል በሤራ መጠላለፍ፣ በራስ ወዳድነት ልክፍት ተመርዘን ለግል ሥልጣንና ለሀብት ክምችት መሯሯጥ፣ ከሀገር ፍቅርና ብሔራዊ ስሜት ተነጥለን በአጋንንታዊ አዶከብሬ መክለፍለፍ፣ በድግምትና በአንደርብ ሰውን እያረዱ ለግል ብልጽና መሽቀዳደም…. ዋና ተግባሮቻችን አድርገናል – መቶ እንኳን ለማትሞላ አጭር ምድራዊ ዕድሜ፡፡ ይህ ሁሉ ግን ያልፋል፡፡ የጨለማው መበርታት የሚጠቁመውም ጊዜው ሊያልፍ መቃረቡን ነው፡፡ የተነገረ አልቀርም፤ ያልተነገረም አልታየም፡፡ እውነት ነው –  “ብን” ብለው ስለሚጠፉት ሲነገረን ያላመንን ምንም ነገር ብንሰማ አናምንም፡፡ አንቺኛሽም የዶግ አመድ ትሆኛለሽ፡፡ “ብን” ብሎ መጥፋትማ ለ“ታደሉት” ነው፡፡ ቅኔ አይደለም – ሌጣ እውነት ነው፡፡

ስሙን አባቱ ሉሲፈር ይጥራውና የዚያን የአጋንንት ውላጅ ጽሑፍ ከዚህ በታች እንዳለ አስቀምጫለሁና የፈለገ ያንብበው (ወዳማርኛ ልመልሰው አልኩና ሥራ የመፍታት ያህል ቆጠርኩት)፡፡ እርግጠኛ ነኝ – እንደመለስ ሁሉ ልጅ አልወጣለትም፡፡ ኢትዮጵያ ለልጆቿ አትሆንም እንጂ ጠላቶቿን በእንባዋ ድባቅ ለመምታትና ዘር ማንዘራቸውን ድራሽ ለማጥፋማ ማን ብሏት! (እርሷን በድሎ ዘር የወጣለትና መጨረሻው ያማረ እስኪ አንድ ሰው  ጥሩልኝ! እመኑኝ የለም፡፡)

Filed in: Amharic