>
5:13 pm - Friday April 19, 4650

ግቢው ! ዩኒቨርስቲው !! (አሥራደው ከፈረንሳይ)

ግቢው ! ዩኒቨርስቲው !!

(አሥራደው ከፈረንሳይ)

 

 

 

እንዳልነበሩበት – ተናዳፊ ንቦች ፤

ለህዝባቸው ጥቃት – ዘብ ቆሞ አዳሪዎች ፤

የዕውቀትን ጥበብ – ትምህርት ቀስመውበት፤ ለለውጥ ሃዋሪያነት – ሃሳብ ላመኑበት፤

በአንድላይ ተነስተው – እንዳልተመሙበት፤

ዘመን አሳልፎ – ዘመንን ደርቶ ፤

ሳየው ይገርመኛል ግቢው አንቀላፍቶ ፤ ግቢው አንኮራፍቶ ::

” ፋኖ ተሰማራ – ፋኖ ተሰማራ ፤ ”

” እንደነ ሆ ቺ ሚን – እንደ ቼ ጉቬራ ፤ ”

“መሬት ላራሽ ይሁን – ገባርነት ይጥፋ ፤ ”

” የድሃ ልጅ ይማር – ትምህርት ይስፋፋ ፤

” ሃሳብን በሃሳብ – እያሞሻለቅን፤ ትምህርት እንማር – እንቅሰም እውቀትን ::

ማለቱ ቀረና !

የአይምሮ ባዶነት – የሃሳብ ድህነት፤ የህሊና ዝገት – ሃሞተ ቢስነት ፤

ተደማምረውበት – ጎሣ_ ዘረኝነት ፤

ይታያል ተኝቶ – ግቢው አንቀላፍቶ ፤

ግቢው አንኮራፍቶ ::
የባዶነት ስሜት – ኳኳታ _ ኳኳታ ፤

የውስጣዊ ቁሸት – ክርፋት _ ክርፋት ሽታ፤

ቂም በቀል ጥላቻ – ተደማምረውበት፤

ይታያል ተኝቶ – ግቢው አንቀላፍቶ፤

ግቢው አንኮራፍቶ ::

ዘመን አሳልፎ – ዘመንን ሸኝቶ ፤

የዘርና_ ጎሣ – ድሪቶ ደርቶ ፤

ሳየው ይገርመኛል – ግቢው አንቀላፍቶ ፤

ግቢው አንኮራፍቶ ::

ኩርር !! ኩርር !! ኩርር !!

 

አንድ ቀን

 

በአገራችን ኢትዮጵያ፤ በተለያዩ ዩኒቨርስቲዎች፤ በተማሪዎች መሃከል ያለው ፤ የዘርና የጎሣ፤ የቂም በቀል ጥላቻና ብጥብጥ፤ ህወሓትና አጋሮቹ፤ የዘር ፖለቲከኞች ለ30 ዓመታት፤ ተክለው እየኮተኮቱ ያሳደጉት ቁልቋል ውጤት ነው ::

የዘርና የጎሣ ፖለቲካ አቀንቃኞችና ካድሬዎቻቸው፤ ወጣቱን አይኖቹን ብቻ ሳይሆን፤ አይምሮውንም በዘርና በጎሣ መሃረብ ከልለው በማደናበር፤ ወጣቱን አመክነዋል፤ አገራችንንም ገድለዋል ::

የዘርና የጎሣ ፖለቲከኞች የሠረቁት፤ የአገራችንን ሃብትና ንብረት ብቻ ሳይሆን፤ የወጣቱን ህልምና ዕድሜ፤ የአገራችንንም ሠላምና ልዕልና ጭምር ነው ::

የራሳቸውን ዕድሜ አገባደው፤ በወጣቱ ዕድሜ ገበጣ የሚጫወቱትን፤ የዘርና የጎሣ ፖለቲከኞች፤ ወጣቱ በአብሮነቱ ጸንቶ በመተባበር በቃ ሊላቸው ይገባል ::

መማር ማለት፤ የአስተሳሰብ አድማስን በማስፋት፤ በአብሮነት ማማ ላይ ሆኖ ፤ አርቆ በማስተዋል፤ ዛሬን በሠላም እየኖሩና እየተማሩ፤ ነገን በተስፋ በማለምለም ፤ ለራስ፤ ለቤተሰብና ለአገር  ዋልታ መሆን ነው ::

በግጥም ያቀረብኳት ወቀሳዬን ሰምቶ፤ ወጣቱ በአብሮነት ማማ ላይ ሆኖ፤ እጅ ለእጅ በመያያዝ፤ አገር ገዳይ ትውልድ ከመሆን ይልቅ ፤ አገር ገንቢ የመሆን ተስፋንው እንዲሰንቅ ምኞቴ ነው ::

Filed in: Amharic