>

እነ እህተ የከበደ ድንበር ተሻጋሪ ወንጄል !  (ነቢዩ ሲራክ)

የማለዳ ወግ…

እነ እህተ የከበደ ድንበር ተሻጋሪ ወንጄል ! 

ነቢዩ ሲራክ

 
* የእህተ ማርያም ስንዱ የከበደ ወንጄል…
* ህግ ማስከበር ያልቻለ ህግ አስከባሪ !
* የጋጠ ወጧ እህተ ማርያም መንገድ … 
* እነ እህተ መካ የሰሩት ጸያፍ ስራስ ?
 
የከበደ ወንጄል ስሰማ
    እህተ ማርያም ስንዱ የተባለችን ጋጠ ወጥ ጽንፈኛ ፣ እርኩስ ፣ መያዣ የሌላት ፣ መቆሚያ መቀመጫዋ ስለማታውቅ  ከንቱ ሰው ፎቶ በገጼ ለጥፊ ባልናገር ደስ ባለኝ ነበር። ከቀናት በፊት አንዲት የእህተ ማርያም ስንዱ “ደቀ መዝሙር ነኝ ” የምትል ሴት ጥቁር አበያ ለብሳ ፣ ተሸፋፍና ኒቃብ አድርጋ የሙስሊም ቅዱስ ከተማ በሆነቸው መካ ከተማ በሚገኘው የካዕባ መስጅድ እየዞረች እስልምናን በማንቋሸሽ የሰራችው ቪዲዮ ብዙም ሳይሰራጭ ደረሶኝ ተመለከትኩት ።  ተበሳጨሁ ፣ አዘንኩም !
   መረጃው እየተሰራጨ እንዳለ ብዙም ሳይቆይ መካ ላይ ክርስትያን ነኝ ብላ በጸያፍ ፉከራ ያሰራጨችው ቪዲዮ ዙሪያ ትንታኔ የሚሰጡ ሙስሊም ወገኖች መረጃው ቅንብር ነው እያሉን ነው ። አዎ አስነዋሪና አሸማቃቂው የእህተ ደቀመዝሙር  መርዘኛ መረጃ ቅንብር ቢሆን ደስ ይለኝ ነበር ። ያም ሆኖ ራሷ እህተ ማርያም ተብየዋ እርኩስ ሳውዲ መካ ካዕባ መስጅድ ደጋፊዋ የፈጸመችውን ወንጄል በእሷ እውቅና የተሰራ መሆኑን ሳታግር በኩራት ነገረችን  🙁   እኔም መረጃው የሀሰት ነው የሚሉት እውነት በሆነ ስል በመመኘት እህተና ደጋፊዎቿ በኩራት ” አድርገነዋል “ባሉት አስጸያፊ ስራ ከማፈር መሸማቅቄያ የመነጨውን ሀሳብ ላካፍላችሁ …
     በወቅቱ መካ ካዕባ እየዞረች የምትቀባጥረውን የእህተ ደቀ መዝሙር መረጃውን ከመረጃ ቆጥሬ ላለማቅረብ ከአንድም ሁለትም የበለጡ ምክንያቶች ነበሩኝ። ከምክንያቶቸ መካከል ወቅቱ የሮመዳን የተከበረ ጾምና ጸሎት ወቅት በመሆኑ ፣ የሰላም ጾም ጸሎት አየሩን ላለመበከል፣  የብዙ አማኞችን ስሜት ላለመንካት የሚሉት ይገኙበታል ። ከምንም በላይ ደግሞ የጽንፈኞች የረከሰ መልዕክት ላለማሰራጨትና ትኩረት እንዳይሰጠው ለማድረግና ብሎም የፊስ ቡክ መራኮቻ አጀንዳ ላለመክፈት በሚሉት ምክንያቶች አሳምነውኝ በመካ የእህተ ደጋፊዎች ለተሰራው ነውር ውግዘቴን ለማቅረብ  አልፈድኩም ! ያም ሆኖ ቪዲዮው በሰፊው መሰራጨቱን ተመልክቸ እህተ ደጋፊዎቿ  የሰሩትን ነውረኛ ስራ ለማውገዝ በተሰበረ ልብ ብዕር ለመጨበጥ ተገደድኩ!
በኮሮና ህግ ጥሰት የተባለው ዘብጥያ  …
   የእህተ ደቀ መዝሙር ያሰራጨችው መረጃ ጉዳዩ በሳውዲ መንግስት እጅ ወድቆ በአደገኛው ስራቸውን የሚጎዳውን ስደተኛ ኢትዮጵያዊ ደህንነትና የሀገር ስም ጥላሸት አስቤው ተሸማቀቅኩ ። የተከበረ ስማችን ክፉ በሚሰሩት እየረከሰ ለመናቅ መርከሳችን ሳያንስ በቅዱስ የካዕባ መስጅድ ሀበሻ ይህን ሰራ ሲባል የሚከተለው አደጋ አሳሰበኝ። ለምን ይህ ይሆናል ? ብየ አስረጅ መልዕክቴን ስሞነጫጭር እህተ ማርያም ስንዱ የመታሰሯ መረጃ ደረሰኝ። የምጽፈውን አቋርጨና ትቸ ከጋለ ስሜት ወጣሁና አጠየቅኩ … ጥያቄየ እህተ በምን ጉዳይ ታሰረች ? የሚል ሲሆን አንድ ለእስሩ መረጃ ቅርብ የሆነ ወዳጄ እህተና ደጋፊዎቿ ኮሮናን ለመከላከል የወጣውን ህግ ጥሰት ሰው ስለሰበሰቡ መታሰራቸውን ነገረኝ።  ጭራሽ እንደ መደሰት ተናደድኩ 🙁 እነ እህተ ሳውዲ መካ የሰሩት ጸያፍ ስራ በራሱ  በክሱ ቀዳሚነት የከበደ ወንጄል ሆኖ አለመጠቀስ በእርግጥም ከመናደድ በላይ ያሳምማል 🙁
ህግ ማስከበር ያልቻለ ህግ አስከባሪ !
   አዎ ፣ ሊነጋ ነው እያልን በተስፋ በምንኖርባት በዚህች ሀገር ህግ ማስከበር ያልቻለ ህግ አስከባሪ አለ ። መናገር ያለብኝን ልናገረው ! እህተ ማርያም ስንዱ “መንግስት የለም” እስኪባል ድረስ የርክሰት ስራ በአደባባይ ስትሰራ ዝም ተብላለች። እሷና ደጋፊዎቿ የራሳቸውን እምነት በሌላው ላይ ለመጫን በሚደረጉት ጽንፈኛ አካሄድ ብዙዎች ተከፍተናል። የሚሰራው የክፋት ስራ ከሀገር ቤት አልፎ በቅዱስ ከተማዋ መካ ካዕባ መስጅድ ደርሶ እህተና ደጋፊዎቿ ከሰው ተራ የወረዱ እንስሶች መሆናቸውን አሳይተውናል። የመካው አስነዋሪ እስልምናን የማራከስና የመሳደብ ስራዋ ቅንብር ነው እንኳ ቢባል እህተ ማርያም በአንደበቷ ” ሰራሁት ፣ አሰራሁት ፣ መስራቴን እቀጥለሰለሁ ” በሚል አንድምታ በአደባባይ ተናግራለችና ውግዘቴ የሚያጠነጥነውም ሆነ እህተ በወንጄል መጠየቅ አለባት የምለው በተናገረችው የምስክርነት ቃሏ ልክ ይሆናል   🙁
   ይታያችሁ ፣ ይሰማችሁ እህተና ደጋፊዎቿ የመንግስት ህግ አስከባሪዎች ባሉበት ሀገር በአደባባይ የሌላውን አማኝ እምነት ሲያንቋሽሹ ተው አልተባሉምና ዛሬ ለሀገርና መንግስት ብሎም ለህዝብ አደጋ የሚተርፍ ስራ ሰርተዋል።  ከሀገራቸው አልፎ በሰው ሀገር ፣ በሰው ሐይማኖትና በሌላው የእምነት ቦታ እየገቡ የሌላውን እምነትን መሳደብና የማንቋሸሽ አደገኛ ወንጄል ፈጽሙዋል። መካ ላይ ሄደው እስልምናን አንቋሸው ነውረኛ ስራ የመስራታቸውን ድፍረት እንደ ሀገር ብዙ ዋጋ ያስከፍለናል።
    እህተና ደጋፊዎቿ  ከዚህ ቀደም ከሰሩት ተደጋጋሚ ወንጀል አድበስብሶ በማለፍ የኮሮናን መከላከያ ህግ ጥሰዋል ተብለው በተራ ወንጄል ደግሞ ከፊዝ በላይ ነው ባይ ነኝ። ይህም ፊዘኛ አካሄድ ህግ ማስከበር ያልቻለ ህግ አስከባሪ በመንግስት መዋቅር መሰግሰጉን ያሳያል ።
የከበደው ድንበር ተሻጋሪ ወንጄል …
   የመንግስት የህግ አስከባሪዎች አይንና ጄሮ እህተ ማርያም ስንዱን የሰራችውን ተደጋጋሚ ወንጄል በሆደ ሰፊነት ቢያልፉት አደገኛውን ሳውዲ መካ በቅዱስ ከተማዋ መካ ካዕባ የሰሩትን ድንበር ተሻጋሪ ወንጀል በዝምታ ማለፍ በራሱ ከባድ አደጋ አለው። ወደ ወህኒ መቀመቅ የሚያዎርደው ወንጄል ትተው በተራ የኮሮና መከላከል ብዙ ሆኖ የመሰብሰብ አዲስ ህግ ጥሰት እነ እህተ ማርያምን ማሰር የህግ የበላይነትን አያረጋግጥምና አፍሬያለሁ ። እህተና ደጋፊዎቿ በሐይማኖቶች መካከል ተከባብሮ የመኖርን እሴት ለመናድ ሞክረዋልና በሚረጩት የጥላቻ መርዝ በግልጽ መከሰስ አለባቸው  !
    በተለይም መካ የሰሩት ነውር ድንበር ተሻጋሪ ወንጄል ኢትዮጲያ ከሳውዲ ጋር ያላትን የባህል ፣ የንግድ የኢኮኖሚና የፖለቲካ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነትንም በእጅጉ የሚጎዳ ነው። ወረድ ሲል በሳውዲው ስደት ራሳቸውን ረድተው ወገን ሀገር እየደገፉ የሚኖሩ ንጹሃን  ኢትዮጵያውያን ዜጎችና ላይ አደጋና ስጋት ላይ የሚጥል ስራ ሰርተዋል። ከዚህም አልፎ ተርፎ በሀገራት መካከል በዘር  በሐይማኖቶች መካከል ያለውን መከባበር መተማመን የሚያሻክር ነውረኛ ስራ በእህተና በደጋፊዎቿ ተሰርቷል ።
   እህተ ማርያም ስንዱ መከሰስና መታሰር ያለባት በጀምላ እየተጣሰ ባለው የኮሮና መከላከያ ህግና መመሪያ ባይሆን ደስ ባለኝ ነበር። ጽንፈኛዋ እህተ ማርያምና ደጋፊዎቿ መከሰስና ዘብጥያ መቀመቅ መውረድ ያለባቸው ብዙ ህግን የመተላለፍ  ወንጀሎች ሞልተው ተርፈዋል። በቅርብ ሳምንታት እህተ ማርያም በድፍረትና በንቀት በሀገር ቤት የኦርቶዶክስን እምነት ላይ የሰነዘረችው ጸያፍ ንግግር በሆደ ሰፊነት ይቅር ቢባል ድንበር ተሻግራ በሙስሊማን ቅዱስ ከተማ መካ ላይ ያሰራችው ጸያፍ ስራ ብቻና ብቻ የከበደ ቅጣት በአደባባይ ሊያቀጣት ይገባል።
    እንደኔ እንደኔ እህተና ደጋፊዎቿ  ለተላለፉት የከበደ ህግ እንደ ቀድሞው የጃንሆይ መንግስት አርባ ጅራፍ በአደባባይ ቢገረፉ ለተጎዳን ወገኖች የሞራል ካሳና ለሌላው መቀጣጫ በሆነ ብየ አምናለሁ። ከአደባባይ ግርፋት ባለፈ በህጉ መሰረት የማያዳግም ቅጣት ሊወሰንባት ይገባል ። እህተና ተከታዮችዋ ለሰሩት አስነዋሪ ስራ መከሰስና መቀጣት ያለባቸው በማያዎላዳው ህግና በከበደ ቅጣት እንጅ ነገ በ30 እና 50 ሽህ ብር ቅጣት በዋስ የሚያስፈታ ወይንም ሶስት አራት አመት በሚያስቀጣ የህግ አንቀጽ ሸብቦ እህተና ደጋፊዎቿን ወህኒ ማውረድ ቀልድ ነው። ይልቁንም ይህ ህግን ማስከበር ሳይሆን ወንጄል እንዲሰራ ከማበረታታል ለይቸ አላየውም !
እስኪ ቸር ያሰማን  !
Filed in: Amharic