>
5:13 pm - Tuesday April 18, 8924

የምስጢር ቋቱ ኮሎኔል ተስፋዬ ወ/ሥላሴና የኢትዮጵያ ጦር ሰራዊት!!! (ዳንኤል እንግዳ)

የምስጢር ቋቱ ኮሎኔል ተስፋዬ ወ/ሥላሴና የኢትዮጵያ ጦር ሰራዊት!!!

ዳንኤል እንግዳ
➢ወንዳወንድ ገፅታና ደንዳና ሰውነት የነበራቸው ኮ/ል ተስፋዬ፣ በሕይወት ዘመናቸው ብዙ ከመናገር ይልቅ ማዳመጥን የሚወዱ ሰው እንደነበሩ በቅርብ የሚያውቋቸው ሰዎች ይናገሩላቸዋል፡፡
የደርግ አባል አልነበሩም ሆኖም፣ አብዮቱ የመጣላቸው እንጂ የመጣባቸው እንዳልነበር ነጋሪ አላስፈለጋቸውም ተስፋዬ የጭቁኖች ልጅ ነበሩ ወዲያው ነበር ታማኝ የሆኑት፡፡
በመጀመሪያዎቹ የአብዮት ዓመታት ከደርግ አባሉ ተካ ቱሉ ስር ሆነው ሰርተዋል በማዕረግ ግን ተስፋዬ ይበልጡ ነበር በስልጠናም የሰማይና የምድር ያህል ይራራቁ ነበር ማለት ያስደፍራል ተስፋዬ እስራኤል ድረስ ሄደው ተምረዋል ከሞሳድ ጋር ትከሻ ለትከሻ ተጋፍተዋል አክራሪ አብዮተኞች የእስራኤል ቆይታቸው ሁልጊዜ ይቆጠቁጣቸው ነበር፡፡ ብዙም ሲያሟቸው ኖረዋል፡፡
የመንግሥቱ ኃይለማርያም ልብ ግን በተስፋዬ ብቃት በጠዋቱ ማልሏል ተስፋዬ ሰለቸኝ ሳይሉ ጧት ማታ ይሰራሉ አለቃቸው እንደዚያ ዓይነት ሰው አልነበሩም ብዙም ሳይቆይ፣ ተካ ተነስተው ሜዳውም ፈረሱም የተስፋዬ ሆነ፡፡
ተስፋዬ፣ ሚኒስትርነት ወዲያው ነበር የተመቻቸው ከጭንቅላታቸው እስከእግር ጣታቸው ወፈሩ፡፡ ዝምታቸውም በዚያው ልክ ጨመረ፡፡
ብዙ ሚስጢሮችን እየዋጡ አስቀሩ አንደበታቸው ቢከፈት አፈትልከው የሚያመልጧቸው ሳይመስላቸው አልቀረም ሚስጢሮቹም ከቀን ወደ ቀን ተደራርበውባቸዋል፡፡
ለምሳሌ፣ ስለ በዓሉ ግርማ አሟሟት ያውቁ ነበር፡፡ ብርቅየው ደራሲ በሞቱ ጊዜ የመንግሥት «የጓዳ ሚስጢር» በእሳቸው መስሪያ ቤት ውስጥ ተማክሎ ነበር ወደመቃብራቸው ይዘውት ሄደዋል ከመንግሥቱ ሌላ፣ ይሄን ሚስጢር የሚያውቅ አሁን ከቶ በነፍስ ይኖር ይሆን?
ደርግ፣ እረፍትን የማያውቅ መንግሥት ነበር ከ1971 እስከ 1978 ዓ.ም የነበሩት ሰባት ዓመታት አንፃራዊ ሰላም ነበራቸው ሻዕቢያ ተዳክሞ ነበር ሕወኃት ገና በዳዴ ላይ ነበረች የዚያድ ባሬ መንግሥትም ተንፍሷል፡፡ ደርግ የማይገፋ ተራራ ነው ተብሎ የተነገረለት በእነዚህ ዓመታት ነበር፡፡
በ1978 ግን፣ የአልጌና ግምባር በሻዕቢያ እንደ ድንገት ተመታ ከዚህ በኋላ፣ ደርግ ከማጥቃት ወደ መከላከል ተሸጋገረ ከሁለት ዓመት በኋላ አፍአበት ላይ ከፍተኛ ጥቃት ተከፈተ ስርአቱ መናወጥ ጀመረ፡፡
መንገዳገድ የጀመረው ከዚህ ግዜ አንስቶ ነበር ማለት ይቻላል ከሶስት ዓመት በኋላ፣ በግንቦት 1983 ዓ.ም፣ ሙሉ ለሙሉ ሰራዊቱ ተበተነ የስርአቱም ማብቂያ ሆነ፡፡
በደርግ ተቀዋሚዎች ላይ መረጃ የማሰባሰብ ኃላፊነት የተጣለው በኮሎኔል ተስፋዬ መሥሪያ ቤት ላይ ነበር፡፡ ኃላፊነቱ ሁለት ገፅታዎች ነበሩት፡፡
አንደኛው፣ አማጺያኑ በከተማ የነበራቸው መዋቅር መበጣጠስ ሲሆን፣ ሁለተኛው አማጺያኑ እምብርት ድረስ ዘልቆ በመግባት መረጃ ማሰባሰብ ነበር፡፡
ይህንን ተልዕኮ ለማስፈፀም፣ ሙያዊ ስልጠና የተሰጣቸው በርካታ የመረጃ ሰራተኞች በኮሎኔል ተስፋዬ ስር ነበሩ፡፡
የመጀመሪያውን ኃላፊነት እነ ኮሎኔል ተስፋዬ በብቃት ተወጥተዋል፡፡ አንድም አማፂ፣ በከተማ የረባ መዋቅር አልነበረውም፤ እስከመጨረሻው እለት ድረስ፡፡
ሁለተኛው ተልዕኮ ላይ ይህ ነው የሚባል ሰርጎ በመግባት መረጃ መቃረም ሳይችሉ ቀርተዋል ያ ሁሉ የተማረ ኃይል አንዲትም ቁም ነገር መስራት አልቻለም፡፡
የአልጌና፣ የአፍአቤት፣ የምፅዋና የሽሬ ድንገተኛ ወታደራዊ ጥቃት የዚህ ክፍተት ውጤት ነበር፡፡ አማጺያኑ ድል የተጎናፀፉት ድንገተኛ ጥቃት መሰንዘር በመቻላቸው ነበር፦
Filed in: Amharic