>
5:13 pm - Tuesday April 19, 3363

የዘር ፍጅቱ በነፃና ገለልተኛ አጣሪ ኮሚሽን ይጣራ!!! (ፀ/ት ፂዮን ዘማርያም)

የዘር ፍጅቱ በነፃና ገለልተኛ አጣሪ ኮሚሽን ይጣራ!!!

 ፀ/ት ፂዮን ዘማርያም


የህወሓት፣የኦነግ ቄሮ፣ ኦነግ ሸኔ፣ ኦፌኮ ድርጅታዊ የዘር ፍጅት!!!

 

‹‹የሃጫሉን ሞት ተከትሎ በኦሮሚያ ክልል በብሔር እና ሃይማኖት ማንነት ላይ ያነጣጠረና በዘር ተኮር ጭፍጨፋ ሊፈረጅ የሚችል የጥቃት እርምጃ በተደራጁ እና በታጠቁ ኃይሎች  መፈጸሙን የሚያሳዩ ማስረጃዎች ከተለያዩ አቅጣጫዎች በመውጣት ላይ ናቸው። አንዳንድ የመንግስት አካላትም በዚህ ጥቃት ዙሪያ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ተሳትፎ እንደነበራቸው በመንግስት መገናኛ ብዙሃን ሳይቀር ተገልጿል። በአንዳንድ ስፍራዎችም የክልሉ ታጣቂዎች መሳሪያቸውን ጭምር በሕዝብ ላይ ጥቃት ይፈጽሙ ለነበሩት ቡድኖች አሳልፈው በመስጠት ጥቃቱ እንዲፈጸም መደረጉም ተገልጿል። ይህም ብቻ አይደለም በበርካታ የኦሮሚያ ከተሞች ዘር ተኮር የሆነው ጥቃት እና ጭፍጨፋ ሲፈጸም በአካባቢው የነበሩ የመንግስት ባለሥልጣናት እና የጸጥታ ኃይሎች ዳር ቆመው ጭፍጨፋውን፣ የንብረት ማውደሙት እና የዝርፊያውን ተግባር ይመለከቱ እንደነበር እማኞች መስክረዋል።››1  ይላል እውቁ የስብዓዊ መብት ተሞጋች ያሬድ ሀይለማርያም፡፡

‹‹የኦሮሚያ ፖሊስ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ኮሚሽነር ግርማ ገላን መግለጫ መሠረት ‹‹በርካታ ኦሮሚያ ዞኖች በአርሲ፣ በጅማ ብሔር ተኮር ጥቃቶች ተፈጸመዋል፡፡ ከዛም አልፎ በአርሲ አካባቢ ላይ የተፈፀሙት የግድያ ወንጀሎች የሃይማኖት አዘል ንቅናቄዎች ነበሩ፡፡ በሃይማኖት ክርስቲያን እምነት ተከታዬች ኦሮሞ ሆነው የሞቱ በተለይ ምስራቅ አርሲ ሠላሳ አምስት ሰዎች ነው የሞቱት ከዚህ ውስጥ ሃያ ሁለቱ የሸዋ ኦሮሞ ተወላጆች ናቸው፡፡ ክርስቲያን  በመሆናቸው የተገደሉ፡፡ አስራሦስቱ የአማራ፣ ደቡብ ክልል ተወላጆች መሆናቸው አረጋግጠናል፡፡››2

‹‹እንዲ ባሉ አሰቃቂ እና ዘር ተኮር በሆኑ ጭፍጨፋዎች ላይ የመንግስት አካላት በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ ተሳትፎ ከነበራቸው ይህ ጉዳይ በራሱ በመንግስት ሳይሆን በገለልተኛ ወገን ሊጣራ ይገባዋል። እነዚህ የክልል ባላሥልጣናት ለተፈጸመው ወንጀል ተጠያቂ የሚሆኑባቸውን መረጃዎች ቀድመው ሊደብቁ የሚችሉበት እድል ሰፊ ነው። ስለሆነም ጉዳዩ ከመንግስት ነጻ በሆኑ እና ከፍተኛ የሙያ ብቃት ባላቸው ሰዎች ሊጣራ ይገባል። ቀደም ሲል የጋንቤላውን እልቂት እና ከዛም በኋላ የምርጫ 97ቱን ግጭት ተከትሎ የተቀሰቀሱትን ግጭቶች እና የደረሰውን የጉዳት መጠን የሚያጣሩ ኮሚሽኖች መሰየማቸው ይታወሳል። በተለይም የምርጫ 97ቱን ግጭት ያጣራው እና በዳኛ ፍሬህይወት ይመራ የነበረው አጣሪ ኮሚሽን የእነ መለስ ዜናዊን ጫና እና ማስፈራሪያ ተቋቁሞ ያከናወነው ምርመራ ታሪክ ሁሌም የሚያነሳው ነው።››1

የዶክተር አብይ መንግሥት የመከላከያ ሠራዊት፣ የፖሊስ ኃይል፣ የጸጥታና የህዝብ ደህንነት እንዲሁም የመገናኛ ብዙሃን ማለትም የገዝው ፓርቲ ኦዴፓ/ ብልፅግና ፓርቲ ሹማምንቶችና ካድሬዎች ህግ ሳያስከብሩ፣ እያዩ እንዳላዩ በመሆን፣ ድርጊቱ ሲፈፀም ዝም ብሎ በማየት አብረው ተጠያቂ በመሆናቸው የተነሳ በመላ ሃገሪቱ የተፈጸሙትን ዘር ተኮር ጭፍጨፋና የንብረት ውድመት የሚያጣራ ገለልተኛ አጣሪ ኮሚሽን ማቆቆም ግድ ይላል፡፡  የዶክተር አብይ መንግሥት የምርጫ 97ቱን ግጭት ያጣራውን የዳኛ ፍሬህይወትና ዳኛ ወልደሚካኤል አጣሪ ኮሚሽን ሪፖርት ለፓርላማ ለማቅረብ ጠይቀው ፍቃድ አላገኙም ዋናው ምክንያት በዛን ጊዜ ወንጀል የፈፀሙ ሹማምንቶች የፖሊስ ኮሚሽነር የነበሩት ወርቅነህ ገበየሁ፣ ጌታቸው አሰፋ፣ ብርሃኑ ፀጋዬ ወዘተ የመሳሰሉ ባለሥልጣኖች ተጠያቂ እንዳይሆኑ ለማድረግ ነው ይባላል፡፡

የዶክተር አብይ መንግሥት መንግሥታዊና የግል የመገናኛ ብዙኃን ዘርፍ የሚዲያ ህግ የማስከበር ቸልተኝነት የተነሳ  ኦ ኤም ኤን፣ ድምጺ ወያኔ፣ የትግራይ ቲቪና ሌሎችም ሚድያዎች ሌት ተቀን ልዩነትን፣ የእልቂት ቅስቀሳንና  ስምሪትን ሲሰብኩ ዝም በማለታቸው ተጠያቂነትና ክስ ሊቀርብባቸው ይገባል እንላለን፡፡ እነዚህ ሚዲያዎች የእልቂት ቅስቀሳንና ስምሪትን የሰበከበትን ቀንና ሰዐት ከነ አውዲዮ/ቪዲዮ ጋር ለማስረጃነት በማቅረብና  ሁሉም ብሮድካስት በፌስቡክ ላይ አጠናቅሮ በማቅረብ ክስ ሊመሰረትባቸው ይገባል እንላለን፡፡ ለዚህ ነው ነፃና ገለልተኛ አጣሪ ኮሚሽን ማቆቆም አስፈላጊ የሚሆነው፡፡

በሌላ ዜና ‹‹የድምፃዊ ሃጫሉ ሁንዴሳ ግድያን ተከትሎ በተከሰተው አለመረጋጋት የሞቱ ሰዎች ቁጥር 239 መድረሱን ፖሊስ አስታወቀ። ኤኤፍፒ የዜና ወኪል የኦሮሚያ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን ተጠባባቂ ኮሚሽነር ሙስጠፋ ከድር ለአገሪቱ ቴሌቪዥን ጣቢያ የሰጡት መግለጫ ጠቅሶ እንደዘገበው የሟቾች ቁጥር ጨምሯል። ተጠባባቂ ኮሚሽነሩ እንዳሉት “በክልሉ በተከሰተው አለመረጋጋት 11 የፀጥታ ኃይሎችና 215 ሰላማዊ ሰዎች ሞተዋል” በ…›› 2

ይህ በእንዲህ እንዳለ የሞች ቁጥር ከ239 ወርዶ አንዴ 187 ቀጥሎም 158 እየተባለ በዛው መገናኛ ብዙሃን መረጃው መቅረቡና ከ3 የፀጥታ ኃይሎች  ወደ 11 ሞትና 57 ፖሊሶች ጉዳት ደርሶባቸዋል የሚል የተምታታ መረጃ በመውጣት ላይ ናቸው፡፡

‹‹በተለይ በግፍ የታሰሩ አመራሮችና አባላቶቻችን ላይ ፍ/ቤት ከመቅረባቸው በፊት በአገዛዙ መሪዎች በተለያዩ ጊዜ ውንጀላ እየተካሄደባቸው ይገኛል፡፡ ፓርቲያችንም በሕጋዊ መንገድ የተመዘገበ መሆኑን በመካድ ጠ/ሚኒስትሩ ከከፍተኛ የስራ ኃላፊዎቻቸው ጋር ባደረጉት ስብሰባ “ባልደራስ ብሎ ራሱን ያደራጀ” በሚል ፓርቲው በሕግ የተቋቋመ ሳይሆን ሕቡዕ ድርጅት አስመስለው በማቅረብ “ራስ ከሳሽ ራስ ፈራጅ” ሆነው ይገኛሉ፡፡›› 4 ይላል የባልደራስ መግለጫ  ጠ/ሚኒስትሩና ጠቅላይ አቃቢ ህግ አዳነች አቤቤ በቃለ-ምልልሳቸው ባልደራስን ወንጀለኛ ድርጅት አድርገው መፈረጃቸውን በመቃወም፡፡ ባልደራስ በመቀጠልም ‹‹በአንድ ወቅት ጠ/ሚኒስትሩ “ግልጽ ጦርነት ነው የምንገጥመው” ብለው ያሉትን እያስታወስን የሰሞኑ ውንጀላ ቀደም ሲል የታሰበና የታቀደ መሆኑን ልብ ይሏል፡፡ ህዝብ ማን ምን እንደሆነ ያውቃል፡፡ እየተሻሻለ ነው በሚባልበት የፍትህ ስርዓት ውስጥ ልክ እንደ ህወሓት/ኢህአዴግ/ ዘመን ከተሟላ የፍርድ ሂደት በፊት በፖለቲካ ውሳኔ የዳኝነት ነፃነት እየተገፈፈ ነው፡፡›› 4

‹‹አሁንም መንግስት ጊዜ ሳይወስድ እና መረጃዎች ተዳፍነው ሳይጠፉ በፊት በኦሮሚያ ክልል፣ በአዲስ አበባ እና በሌሎች የአገሪቷ ክፍሎች የተፈጸሙትን ዘር ተኮር ጭፍጨፋ እና ስለደረሰው የንብረት ውድመት የሚያጣራ ገለልተኛ አጣሪ ኮሚሽን እንዲያቋቁም ማሳሰብ እፈልጋለሁ። ይህን ሃሳብ የምትጋሩ ፍትህ ፈላጊ ወገኖች ሁሉ በሁሉም መድረክ ይህን ሃሳብ እንድታንጸባርቁ እና መንግስት በአፋጣኝ ገለልተኛ አጣሪ ኮሚሽን እንዲያቋቁም ጫና እንድትፈጥሩ በአክብሮት እጠይቃለሁ። በዘር ላይ ያነጣጠሩ ጥቃቶች እና ጭፍጨፋዎች ልዩ ትኩረት ተሰጥቷቸው፣ በቂ ምርመራ ተደርጎባቸው በድርጊቱ ላይ ተሳታፊ የሆኑ ሁሉ በአፋጣኝ ለፍርድ ካልቀረቡ አገሪቱን ወደከፋ አደጋ ይከታታል።››1በማጠቃለያ፤- ሻለቃ ዳዊት ወ/ጊዮርጊስ በኢትዮጵያ ውስጥ የተደረገውን ጀኖሳይድ (Ethiopia Genocide) ለአለም ለማሳወቅ እየሰሩ ይገኛሉ፣ ነፃና ገለልተኛ አጣሪ ኮሚሽን በማቆቆም በርዋንዳ ጀኖሳይድ የሠሩት ሻለቃ ዳዊት ወ/ጊዮርጊስና ያቆብ ኃለማርያም  ቢሳተፉበት መልካም ነው እንላለን፡፡

ፍትህ በማንነታቸው የጥቃት ሰለባ ለሆኑ ሁሉ!

ምንጭ

Filed in: Amharic